top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 4 hours ago
  • 4 min read


በሥጋ ማርያም ተገልጦ፥ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በአይሁድ ምድር ሲመላለስ አምላካቸውን ያዩት ሰዎች እንዴት ታድለዋል የሚል ነገር አንዳንዴ ውል ይልብኛል (ይሄ ዘወትር የምንደነቅበት ነበር መሆን ያለበት)።


ተመልከቱ ቅዱስ ሉቃስ “እንደልማዱ በሰንበት ወደ ሙኩራብ ገባ” ይለናል። (ሉቃ 4፥26)። በዕለተ ሰንበት ስትሄዱ መጽሐፉን ገልጦ የሚያነበው ዓለምን በቃሉ የፈጠረው ፥ በእጆቹ የፈጠረን አምላክ ነው።


ግን እኔስ በዛ ዘመን ብኖር ከአይሁድ የተለየ ለጌታዬ ቦታ እሰጠው ነበር? ለዛውም ዘወትር በሰንበት ወደ መቅደሱ የማልሄድ ከሆነ ፈጽሞ አላየውም።


በቤተሳይዳ የጸበሉ ስፍራ ስትሄዱ 38 ዓመት አልጋ ታቅፎ የኖረን ሰው አንድ በሠላሳዎቹ መጀመሪያ ያለ ወጣት እያናገረው ነው፤ ከዛ በሚደንቅ ተአምር አልጋህን ይዘ ተነስ ሲለው ታያላችሁ፤ ያያችሁትን ማመን ቢከብዳችሁም ያን ሰው ግን፣ ያ አጃቢ ያላስከተለውን፣ የወየበ ልብስ የለበሰን ሰው፣ ያ በለሰለሰ ድምጽ የሚናገርን ሰው እንዴት አምላክ ብላችሁ ትወስዱታላችሁ? በዛ ላይ በኑሮ ወጥመድ ተወጥራችሁ፣ እከሌ ዓየን ዓላየን፣ ማን ነው መጀመሪያ ጸበል ውስጥ ዘሎ የገባው የሚለው ወሬ አካባቢውን ወጥሮት እንዴት ይሄን ሰው ዓይኖቻችን ይየው?


ስለአምላክ ያላችሁ፣ ስለሚመጣው መሲህ የሰማችሁት ትንታኔ እና የተወሩ ወሬዎች ሁሉ ዓይናችን ሥር ሆኖ ምስኪኑን መጻጉ የሚያናግረውን አምላክ የሚያገል ነበር።



ያ ዘመን ዛሬ ቢሆን እኔ ከአገለሉት፣ ሲገደል ከተደሰቱት ወይም ግድ ካልሰጣቸው ሰዎች ተርታ የምመደብ እንደምሆን እራሴን እጠረጥራለሁ።



እስቲ በዚሁ ወደ ሰማርያ እንለፍ። ወደ ዩሐንስ ወንጌል ምዕራፍ አራት። “ወደ ሰማርያ ሊያልፍ ግድ ሆነበት” ይለናል ዩሐንስ። ብዙም ሳይዘገይ “በውሃ ጉድጓድ አጠገብ ተቀመጠ” ይለናል። ለምን በሰማርያ ሊያልፍ ግድ እንደሆነበት ሲነግረን።


ከዛ አንዲት በኃጢአት የደከመች፣ በሃይማኖቷ ግን “ክርስቶስ የሚባል መሲሕ ይመጣል የዛኔ እሱ ሁሉን ይነግረኛል” ብላ በልቧ የምትጠብቅ ምስኪን ሴት የውሃ እንስራዋን አዝላ ከነመቅጃዋ መጣች።


ውሃ ስጪኝ አላት ያ የማይጠማው ከሷ ኃጢአት የተነሳ ግን ደክሞት የተጠማው ሰው። የተሰመረን መስመር መሲሒው መጥቶ ምክንያቱን እስኪነግራት የምታከብረው ያቺ ሴት ግን አይሁዳዊ ሲሆን ከሳምራዊት ሴት ውሃ ስጪኝ ማለቱን አልወደደችም። እሱ ግን አላት “የሚጠይቅሽን ብታውቂ አንቺ ነበር ውሃ የምትጠይቂው።” ግራ ገባት። በአንድ በኩል የሚቀልድ መሰላት፣ ስለዚህም በምክንያት እና በማሾፍ ሞገተችው “የታለ መቅጃኸ?” አለችው፣ በሌላ በኩል ይሄ ሰው ሥርዓት አለው፣ እንደሌሎች የምታውቃቸው አይሁድ አልመስላት አላት፣ አይሁድ ሆኖ ሳለ ከሳምራዊት ሴት ጋር ማውራቱ ሳያንስ አነጋገሩ በሥልጣን ነበር። ቸል ብለው የማያልፉት ነበር። ይሄም ከቃሉ የተነሳ ብቻ አልነበረም። ከሁኔታው፣ ከመልኩ፣ ከሞገሱ፣ ዓይን ብቻ የሚገባው ቃላት የማይገልጸው የእውነት ውበት በማየቷ ጭምር እንጂ፣





ይሄ ግን አካላዊ ውበት እንዳይመስላችሁ፤ ከኃጢአት ድካም ማረፍን የናፈቀች ነፍስ ብቻ የምታውቀው፣ ስታየው ግን የማታልፈው ልዩ ውበት እንጂ። ። በመኃልየ መኃልይ ጠቢበኛው ሰሎሞን የገለጻት ነፍስ ስታየው የምታውቀው ፥ ውዷን ከመፈለጓ የተነሳ የደከመችው ያቺ ሴት ስታየው የምታውቀው ውበት ያለው ነበር እንጂ። ለዚህ ነው “ነቢይ እንደ ሆንህ አያለሁ” ያለችው። ንግግሩ ብቻ ስላልሆነ ነው “አያለው” ያለችው።



አምስት ባሎች የነበሯት አሁን አብራው ካለችው ጋር ባልተቀደሰ ጥምረት የተሳሰረችው ያቺ ሴት ግን ክርስቶስን ግድ ያስባለ የሃይማኖት ውበት ነበራት። ያም ተስፋ ነበር። “አንተ ከአባቶቻችን ትበልጣለህ፣ አንተ ከያዕቆብ ትበልጣለህ፣ ደግሞ ይመጣል ያ መሲሒ፣ ይመጣል ክርስቶስ ሊነግረን ሁሉን” ትለው ነበር ለራሱ ለክርስቶስ።


በኃጢአት ብዛት ቀጥና በአባቶቿ እምነት ተስፋ ግን ሳትሰበር ያለችው ያቺ ጌታን ግድ ያሰኘች ነፍስ።



ሲ ኤስ ሉዊስ እንዲህ ይላል “በዚህ ምድር ላይ ተራ ሰዎች የሉም። ከሟች ሰው ጋር በሕይወታችሁ አውርታችሁ አታውቁም።” ተፈጥሮ፣ ሀገራት፣ ባህሎች፣ ጥበቦች፣ ስልጣኔዎች እነዚህ ናቸው ሟቾች። እነዚህ ናቸው አርጀተው የሚጠፉት። የእነዚህ ሕይወት ነው ለእኛ ጥቅም፣ ለእኛ እንደ ትንኝ መሆን ያለባቸው። የምናወራው፣ የምንቀልደው፣ የምንሰራው፣ የምንጋባው፣ የምንበዘብዘው፣ የምናሰቃየው፣ የምንጨቁነው ግን ዘላለማዊን ነው። ከዘላለማዊው ጋር ነው የምንጋፋው። የምንተቃቀፈው።



ጌታችን ያን ሁሉ ሰዓት በውሃ ጉድጓድ ዳር ተቀምጦ የጠበቃት፣ በእኛ ዓይን ብትሆን ባል የማይበረክትላት ተብላ የተገፋች፣ በማንኛውም ሰው ዓይን መሙላት የማትችለው ያቺ ዘላለማዊ ነፍስ ያላት አንዲት ሳምራዊት ነበረች። አንዲት ሳምራዊት። የምታየውን ወንድምህን ካልወደድክ እግዚአብሔርን ወዳለው ማለት ውሸት ነው ይለናል ሐዋርያው ዩሐንስ በመልዕክቱ፣ ምክንያቱም እግዚአብሔርን አላየኸውምና። (1ዮሐ 4፥20)።


ይሄ ማለት አጠገብኽ ያለው ዘላለማዊው ወንድምኽ ነው ያላየኸው አምላክ መገለጫ። እሱን ውደደው፣ ግድ በለው፣ ለምነው ውሃ ላጠጣ ብለህ፣ የሚያስፈልገውን ለምኖ አይደለም ለምነኽ ስጠው እያለን ነው። ዘላለማዊውን ወንድማችንን ስንረዳ ዘላለማዊው ውሃ፣ የፍቅር ውሃ፣ የዚህን ዓለም ውሃ የማያስጠማው ውሃ ፥ የሕይወት ምንጭ መፍለቅ ይጀምራል ከውስጣችን። ክርስቶስ ግድ የተሰኘባትን ነፍስ ያልናቅን ለታ፣ ያን ጊዜ ነው ጌታችንን መውደድ የምንጀምረው። ያቺ ነፍስ በኃጢአት የደከመች ቢሆን እንኳ፣ ያቺ ነፍስ እኛን የሚያበሳጭ እና የሚያናድ ነገር ከመሥራት የማትቦዝን ቢሆን እንኳ፣ ያቺ ነፍስ ቀን በቀን ብታቆስለን እንኳ ከጌታችን ሥጋና ደም ቀጥሎ በዚህ ምድር ላይ ያቺን ነፍስ ነው ልናከብረው የሚገባው። ይሄ ነው የክርስቶስ ፍቅር።


የሱ ፍቅር ያለ ቅድመ ሁኔታ አይደለም። ምክንያቱም “የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል ወደ እርሱም እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን” (ዮሐ 14፥23) ብሎናልና።


የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቅ፣ እወድኸለው ስላልከኝ ብቻ አልመጣም እያለን ነው፣ ቃሌን የሚጠብቅ ግን ይወደኛል፣ እኔም አባቴም እንመጣለን። እንመጣለን በሱ ውስጥ መኖሪያ ልናደርግ። በቁመተ ሥጋ ተወስኖ በአይሁድ ምድር ሲመላለስ በእጆቹ የመዳሰስ፣ ቀሚሱን የመንካት፣ እንደ ዮሐንስ ደረቱ ላይ የመተኛት ዕድሉን ላላገኘን ሁሉ በእውነት ግን ይሄን ዕድል ለምንመኝ፣ በእናንተ ውስጥ ከአባቴ ጋር መኖሪያዬን ላደርግ እመጣለሁ አለን። ቃሌን ከጠበቃችሁ።



ለሰማሪያዊቷ ሴት እንዳላት የዘላለም የውሃ ምንጭ በውስጣችን ሊያፈልቅ ይመጣል። ያ የውሃ ምንጭ በውስጡ የፈለቀለት ቅዱስ ጳውሎስ ይሄን አለን “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ... ሞት ቢሆን፥ ሕይወትም ቢሆን፥ መላእክትም ቢሆኑ፥ ግዛትም ቢሆን፥ ያለውም ቢሆን፥ የሚመጣውም ቢሆን፥ ኃይላትም ቢሆኑ፥ ... ከጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ።” (ሮሜ 8፥ 35-39)።


“መቅጃ የለህም” በማለት እንስራ እና መቅጃ ስላላት ውሃ መጠጣት፣ በመጠጣትም መርካት የምትችል የመሰላት ያቺ ምስኪን ሴት፣ አሁን መቅጃዋን አይደለም እንስራዋን ሳይቀር ትታ ወደ ከተማ ሄደች።


ሌሎች ለዘላለም መንግስቱ እንዲሆኑ “ኑ ፥ ያን አንዲት ምስኪን ሴትን ለማዳን የደከመውን እዩ” ብላ ከከተማው ሰዎችን ጠራች። አገኘውት እያለች በንዳድ ፀሐይ የደከመች ዋላ ውሃ ስታገኝ እንደምትዘለው እየዘለለች ወደ ከተማ ገባች። አገኘውት ውዴን እያለች። ኑ እዩት ውዴ እንደ በረዶ ንጹሁ ነው ፥ ኑ እዩት ውዴ ስለእኛ በደም ተለውሶ ቀይ ነው። ኑ እዩት አፉ እጅግ ጣፋጭ ነው ይነግራችኋል ከሁሉ የተሰወረውን ታሪካችሁን፣ መልኩም ለነፍሴ ያማረ ነው። ኑ ሳምራውያን ሆይ ፥ ውዴ ይህ ነው ፥ ይመጣል ያልነው ክርስቶስ ይህ ነው ፥ ባልንጀራዬም ይህ ነው። (መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 5፥ 10-16)።



በዚህ ምድር ላይ የሚገጥመን ሰው ሁሉ ጌታችን በመስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰለት ነው። ያለእሱ ፈቃድ በዚህ ምድር ሊመላለስ ይቅርና ከጸጉሩ አንድ እንኳ ያለአምላካችን ፈቃድ አትነቀልም። ያ ሰው ክርስቲያን ሲሆን ደግሞ ክብሩ ልዩ ነው። በዚህ ምድር ላይ ባልጀራችን ነው አምላካችንን የመውደዳችን መገለጫ። ለእኛ በጣም ቅርቡ እርሱ ነው።


በሰማርያ ለአንዲት ኃጢአተኛ ያን ሁሉ የደከመ ጌታችን፣ በጎልጎቷ የመስቀልን መራራ ሞት የተጎነጨላትን ያቺን ነፍስ እናክብራት።


ስልጣኔ እንጂ ሟች ፥ የሰው ልጅ አይደለም።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 4 hours ago
  • 1 min read

እውነተኛ ርጋታ እና ጠንካራ መሠረት ሲኖርህ ትችት የበለጠ ይጠቅምሃል።


መቶ ፐርሰንት ልክ ብትሆን እንኳን ወደ አስር ፐርሰንት የሚሆን ሰው ከአንተ ተቃራኒ ይቆማል። ወደ አምስት ፐርሰንት የሚሆን ሰው ደግሞ ሊጠላክ ይችላል። በምክንያትም ያለምክንያትም።

ተረድቶ እና አውቆ የሚደግፍህ እንዳለ ሁሉ፤ ምንም ሳይረዳህ እና ሳይገባው የሚወድህ እና የሚደግፍህ አለ።


ዝም ብዬ ሳየው ወደዋለሁ የሚልን ሰው ከተቀበልከው እና በእርሱ ደስ ከተሰኘህ፣ ዝም ብዬ ሳየው ያስጠላኛል የሚልንም ሰው መታገስ እና በእርሱም አለማዘን ይኖርብሃል።


በተለይ የሀገር መሪ፣ የተቋም አመራር ወይም አንዳች ማህበራዊ ኃላፊነት ላይ ስትሆን ፥ ሁሉም ይደግፈኝ የሚል ፍላጎት እብደት ነው።


ከትልቅነት መለኪያዎች አንዱ ትችቶችን፣ ነቀፋዎችን እና ጥላቻዎችን የምናስተናግድበት መንገድ ነው።


ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ስለ ሰቀሉት ሰዎች በንዴት እነዚህን አጥፋቸው ቢል፤ በግራው ከተሰቀለው ወንበዴ ለይተን ላናየው እንችል ነበር። ከሁሉም የማረክን፣ መሞቱ የምርም ለኛ እንደሆነ ያወቅነው ለሰቀሉት ሰዎች ባሳያቸው ምህረት ነው።


ደካማ መንግስት የሚነቅፉትን እና የሚተቹትን ያስራል።


ለምን?


ምክንያቱም የሚደብቀው፣ የሚሸሽገው ብዙ ክፋቶች አሉት።


ጥፋቱ እንዲታረም፣ እንከኑ እንዲሻሻል የሚፈልግ ማንም ግን ትክክል ቢሆን እንኳ ለትችቶች ክፍት ነው። በሚነቅፉት አይረበሽም። ጠቢብ ነቀፋን ይወዳል እንደሚል መጽሐፍ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Apr 26
  • 2 min read


አመጽ አንድን ነገር የማሳኪያው አጭሩ መንገድ ሊመስለን ይችላል። በሕይወት ውስጥ ወለፈንዲ (paradox) ከሆኑ ነገሮች ውስጥ አንዱ ስኬትን በአጭር ማግኘት እና በረጅሙ እና እውነተኛው መንገድ ማግኘት ነው። በየቀን ሕይወታችን ውስጥ በጣም ትልቁ ግፊት የምንፈልገው ነገር ጋር በአጭር ጊዜ ውስጥ መድረስ የሚለው ስሜት ነው። ሕይወት አጭር ናት ግን ከተሳሳትን ደግሞ የዛ ስህተትን ፍሬ የማጨዲያው ወራት ከሕይወት ርዝማኔ በላይ ረዥም ነው የሚሆንብን። ሁላችንም በሃያዎቹ መጀመሪያ ይሄ አብዮታዊ የመሆን ፍላጎታችን እና ለውጥን በቶሎ የማምጣት መሻታችን ጅል የሆኑ ስህተቶችን አሰርቶናል። ማምጣት የምንፈልገው ለውጥ የግድ ሀገራዊ ብቻ ላይሆን ይችላል። በሕይወታችንም ሊሆን ይችላል።



ለብዙ ዘመን ስለመታገስ ሰምቻለሁ። ግን ትግስት ሲባል ቃሉን እንደመጥራት ቀላል አይደለም። መታገስ ምንአልባትም ከትህትና ቀጥሎ በጣም ከባዱ ባህሪ ሊሆን ይችላል። መታገስ የምንፈልገውን ነገር መርሳት እና በመጣ ጊዜ ይምጣ ማለት አይደለም። መታገስ የምንፈልገው ነገር እንዲሆን በመስራት ግን ያንን ነገር ሕጋዊ ባልሆነ ሁኔታ እና ብዙዎችን በሚጎዳ መልኩ ላለማግኘት መስራት ነው። መታገስ የምንፈልገውን ነገር ባለመርሳት ፥ መሻታችን በራሱ ብቻ የመጠበቅ ጊዜውን እንዳያሳጥረው መጠንቀቅ ነው።



ለምሳሌ ፕሬዝዳንቱ እንዲቀየር የሚፈልግ ሰው ብዙ ሕጋዊ መንገዶች አሉት። ለዛ መስራት ይችላል። ሕጋዊ መንገዶች ተጓዳኝ ጉዳቶችን ለመቀነስ የተቀመጡ ናቸው። እንደ አሜሪካ ባለ ሀገር ውስጥ ደግሞ ፕሬዝዳንቶች በዓመታት ይቀያየራሉ። ሕዝብ አንድን ፕሬዝዳንት ሲመርጥ እኛ ላንስማማ ብንችል እንኳ የሌሎችን መራጮች መብት ግን ማክበር አንዱ የትግስት መገለጫ ነው። ከዛም በላይ ትህትና ነው። እነሱም በአመክንዮ ሂደት (reasoning process) አስበው እና አውጥተው አውርደው እንዳደረጉት ማመን ያስፈልጋል። ሕጋዊ መንገዶችን የሚከተል ማንም እነዛን የማሳመን ሸከም ስለሚኖርበት ፥ እነሱን ለመረዳት ብዙ ርቀት ይሄዳል። በዚህ መኃል እርስ በእርስ መነጋገር፣ የልዩነትን ክፍተቶች የማጥበብ ሥራዎች ይሰራሉ። ትግስት ባላንስድ (balanced) የሆነ ውጤት እንድናገኝ የሚያደርገን ለዛ ነው። በማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ሕይወት ውስጥ እውነት ማናችንም ጋር ተጠቅልላ የለችም። የምንጠላው ወይም የምንቃወመው ቡድን ጋርም እውነት አለ። ለዚህ ነው በትግስት የሚራመድ ማንም ብዙ እውነቶችን ገንዘብ ማድረግ የሚችለው።



በጣም መጋፋት ካሉብን ፍላጎቶች ትልቁ ለውጥን በፍጥነት የማየት ውሳጣዊ ስሜትን ነው። ስንዴ ዘርታችሁ ይሄ ነገር እየበቀለ ነው እንዴ ብላችሁ ቆፍራችሁ አውጥታችሁ አታዩትም። አፈሩን አለስልሳችሁ፣ ወቅቱን ጠብቃችሁ እስከዘራችሁ ድረስ ያ ዘር አፈሩን ፈልቅቆ ቡቃያ ሆኖ እስኪወጣ መጠበቅ (መታገስ) ይኖርባችዋል። የብዙ ድንቅ ለውጦች ቁልፍ ያለው በመታገስ ላይ ነው።



አመጽ የትግስት እጦት ነው። አመጽ የምንፈልገው ነገር ጋር በአጭር የመድረስ ስሜታዊ ኃይል ነው። ውጤቱም የምንፈልገውን ነገር የበለጠ ማርዘም ነው። ጸጸት አንድን ነገር በአጭሩ የማግኘት ሩጫ ሽልማት ነው።



የምንፈልገው ነገር ላይ ውጤቱ ላይ ብቻ ዓይናችንን ከማድረግ ያን ለማግኘት የምንሄድበት ርቀት፣ ጉዞ ጭምር እንዲያስደስተን እና ያ ሂደት (process) የራሱ የሆነ ደስታ እንዳለው ማሰብ ትግስት እንዲኖረን ይረዳል። አቋራጮችን የሚጠቀም ማንም የሚፈልገው ነገር ጋር ቢደርስ ራሱ ያገኘው ነገር ምን እንደሆነ እና ዋጋው የቱን ያህል እንደሆነ አይገነዘብም። ያገኘውን የማጣት ዕድሉ እንደ መጣበት መንገድ ፈጣን ነው። የጥድፊያ ስሜት ከስንፍና ከሚመጣ የመዘግየት ስሜት በላይ አደገኛ ነው። የዘገየ ሰው ያለውን ላያጣ ይችላል። የሚጣደፍ ግን ያለውንም ያጣል። ትግስት ግን ማንቀላፋትም አይደለም። ትግስት ወደ ምትፈልጉበት ቦታ በየቀኑ መሄድ ማለት ነው። ትግስት የማያቋረጥ ፥ ጨርግዶም እንደማይሄድ ወንዝ ነው። ትግስት የሚፈልገውን ነገር ብቻ ሳይሆን ወደ ሚፈልገው ቦታ የመሄጃው መንገድንም የሚፈልገውን ነገር በመጨረሻ እንዲደሰትበት የማድረግ አቅም እንዳለው ይገነዘባል። የትግስት ዕጦት ውጤቱንም ይቀይረዋል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page