- Mulualem Getachew
- 4 days ago
- 3 min read

ባብዛኛው የአሜሪካ ክፍል ከፍተኛ ብርድ እና በረዶ የሚያስተናግድበት ወቅት ነው። ማህበረሰቡም ወቅቱን ለመምሰል ይጥራል። ከአለባበሱ እስከ የአኗኗር ዘዬው። በተለይ በመካከለኛው ምዕራባዊ ክፍል ያሉት ግዛቶች ከፍተኛ በረዶ እየጣለባቸው ነው። መንገዱ ጭር ያለ፣ ሰው በጊዜ ወደ ቤቱ የሚገባበት እና የሚሰበሰብበት ወቅት ነው። ከቀኑ አራት ሰዓት (ማለትም በኢትዮጵያ አስር ሰዓት) ጀምሮ ቀኑ መጨለም ይጀምራል። ትላንት በረዶ ከጣለ በኋላ የዚህ ሀገር ተወላጅ የሆነችውን የሥራ ባልደረባዬ ከውጪ ስትገባ አይቻት፣ “በዚህ በረዶ ውጪ ላይ እየተራመድሽ (walk) ነበር? የሚገርመው ግን አንቺ ምንም የመሰለሽ አይመስልም?” ስላት፤ “እኔ እንኳ መጥፎ አለባበስ እንጂ መጥፎ የዓየር ፀባይ የለም ቡዬ ነው ማመን የምፈልገው!” በማለት በዚህ አካባቢ የሚታወቀውን አባባል ተናገረች። “እኔ ግን መጥፎ የዓየር ፀባይ አለ ብዬ አምናለሁ፣ እሱንም አሁን እያየውት ነው” ብያት ተሳስቀን ተለያየን።
ይሄ አባባል ግን ብዙ ልንማርበት እንችላለን። ስንኖር ከኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ፤ ግን እነዚህን ሁኔታዎች የምናልፍባቸው ጥበቦችም እኛ ሰዎች አሉን። መሠረታዊ ሕይወታችን ሳይጓደል እና ሳይስተጓገል አስቸጋሪ ቀናትን ማለፍ እንችላለን። የመጀመሪያው ጥበብ የሚመስለኝ መቀየር የምንችለውን እና መቀየር የማንችለውን ነገር በፍጥነት ማወቅ ነው። ከዛ ሁለተኛ ጥበብ አለ። የሚከተል። አሜሪካኖች አንድ ድንቅ ጸሎት አላቸው ፥ እነዚህን ሁለቱንም ጥበቦች በአንድ ላይ ያዘለ።
“ጌታ ሆይ መቀየር የምችለውን ነገር ታግዬ እንድቀይር ጀግንነትን ስጠኝ ፥ መቀየር የማልችለውን ነገር ደግሞ እንድቀበለው መረጋጋትን አድለኝ። ሁለቱን መለየት የሚያስችልን (መቀየር የሚቻል እና መቀየር የማይቻልን) ጥበብን ለግሰኝ።” የሚል።
የሰው ልጅ ብዙ ዕድሜውን የሚጨርሰው መቀየር የማይችለውን ነገር ለመቀበል ተቸግሮ ሲታገለው፤ መቀየር የሚችለውን ነገር ደግሞ ለመታገል በስንፍና እና በፍርሃት ጊዜ ሲፈጅ ነው። በርግጥ በጣም ከባዱ ነገር የትኛው ነገር ይቀየራል ፥ የትኛው አይቀየርም የሚለውን ማወቁም ላይ ነው። ምክንያቱም ብዙ አይቻልም፣ ይሄ የሰው ልጅ ሊያደርገው ፈጽሞ አይሆንም የተባሉ ነገሮች ተደርገው እና ተለውጠው ታይቷል። ለዚህ ነው ያንን ለመለየት አሜሪካኖች ጥበብን የጠየቁት። ኔልሰን ማንዴላ “it is impossible until it is possible ፥ የማይቻል ነበር እስከሚቻል ድረስ” የሚል አባባል አለው።
ብዙ አንባገነነ መንግስታት በሕዝባቸው ላይ መጫን የሚፈልጉት ስነልቦና እነሱን መቀየር የማይቻል መሆኑን ማሳየት ነው። ለዚህ ደግሞ ራሳቸውን ሥዩመ እግዚአብሔር ከማለት እስከ ፈጣሪ ነን ወደሚል ፕሮፖጋንዳ ይነዛሉ። ብዙሁን ሕዝብም ለብዙ ዘመን የስነልቦና ሽባ ያደርጉታል። አንድ ቀን ያ ደፋር ልጅ “ንጉሱ ራቆቱን ነው” እስከሚል እና የሕዝቡን ዓይነ ጥላ እስከሚገልጥ ድረስ።
በተመሳሳይ የዛሬ ሶስት እና አራት መቶ ዓመታት በዓየር ላይ መብረር ለአዋፋት እና ለመላዕክት ብቻ የተተው ጉዳይ ነበር። የራይት ልጆች ተነስተው ያን እስከሚለውጡት ድረስ። የሰው ልጅ ዛሬ ላይ ያሉት የቴክኖሎጂ ውጤቶች አብዛኞቹ ከመቶ እና ከሀምሳ ዓመታት በፊት በሕልም እንኳ የማይታሰቡ ጉዳዮች ነበሩ። ጥበቡ ያላቸው ሰዎች ግን የማይቻል የመሰለውን ነገር እንደሚቻል አሳዩን። ለዚህ ነው በአሁን ጊዜ፣ አሁን ባለን አቅም መለወጥ የምንችለው ነገሮች ምን እንደሆኑ ከስንፍና እና ከፍርሃት ተላቀን ማሰብ ያለብን።
ያሄ ማለት ግን አሁን ላይ የምንቀበላቸው ውስንነቶች የሉም እያልኩኝ አይደለም። ምንም እንኳ ከመቶ ዓመት በኋላ ሰው እስከ ሁለት መቶ ዓመት መኖር የሚያስችለው የሕክምና ጥበብ ሊመጣ ቢችልም፣ ዛሬ ላይ ግን ሞት ለብዙዎቻችን ከሰማንያ እና ዘጠና ላይ እንደሚሆን መቀበል ያስፈልጋል። በተጨማሪም ትላንትን መመለስ አንችልም። ትላንት ዛሬ ያለን እውቀት ቢኖረን የማንሰራቸው ብዙ ጉዳዮች፣ ጥፋቶች ነበሩ። ስለዚህ ትላንትን መቀበል ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ የተረጋጋ አዕምሮ ያስፈልጋል። የተረጋጋ አዕምሮ ከትላንቱ ጋር ይታረቃል። ትላንቱን ይማርበታል፣ ነገም በሆነ ደረጃ ተገማች እንዳልሆነ ይረዳል። ለምሳሌ ነገ ዋጋው ይወርዳል ብሎ ዛሬ የሸጠው ንብረት ፥ ነገ የበለጠ ዋጋው ከፍ ሊል ይችላል። ስለዚህ ቢረጋጋ እና ቢጠብቅ ሊያተርፍ በሚችለው ሳይሆን የተረጋጋ አዕምሮ የሚጨነቀው፤ ትላንት ለመሸጥ ሲያስብ ለምን እንዳሰበ፣ ለምን እንደዛ ዓይነት ውሳኔ እንደወሰነ፣ ለውሳኔ የተጠቀማቸውን ማስረጃ እና መረጃ እንጂ የሚመረምረው ፥ ትላንትን ዛሬ ላይ ባገኘው እውቀት ቆሞ አይገመግምም። የተረጋጋ አዕምሮ ለወቀሳ አይደለም የሚቸኩለው። ለመማር እና ከተቻለ ዛሬን እና ነገን የተሻለ ለማድረግ ነው።
የተረጋጋ አዕምሮ ጀግንነትን ለማግኘት ይጥራል። ምክንያቱም መለወጥ የሚችሉ ነገሮችን ለመታገል ጀግና መሆን ያሻል። ብዙ ሰዎች ስኬታችንን እስከሚያዩ ድረስ ከጎናችን ለመቆም ይቸገራሉ። ሲሳካልን ነው ሊተባበሩን የሚፈልጉት። ይሄ የሰው ባህሪ ነው። የእኔም የእናንተም ባህሪ ነው። ስኬት ወዳጇ ብዙ ነው። የከሰረን እና የተረሳን ሰው “እሱኮ ምርጥ ወዳጄ ነው” ብሎ በኩራት የሚገልጽ የለም። ስኬታማን ሰው ግን ሁሉም ወዳጁ ለማድረግ ይጥራል። ሁሉም ከእርሱ ጋር ፎቶ ለመነሳት እና የእርሱ ወዳጅ ለመሆን ይጥራል። ይሄ በየትኛውም ዘመን ያለ እና የሚቀጥል ነው። ቢያሳዝንም ጀግና ሰው ግን ይሄን ይቀበላል። ስለዚህ ለመለወጥ የሚታገለውን ነገር ለመቀየር ለጥቂት ጊዜ የብቻ ትግል እንደሚሆን ያውቀዋል። ኖሕ መርከቡን ገንብቶ እስከሚጨርስ ድረስ በፀሐይ እና ዝናብ በሌለበት መርከብ የሚገነባ ሞኝ ነበር። ዝናቡ ሲመጣ እና በርግጥም የመጣው ጎርፍ የተለየ እንደሆነ ሲታይ ብቻ ነው ኖሕ ጠቢበኛ የተባለው። ለብዙ ዘመን ግን ሞኝ ተብሎ ለመቆጠር መፍቀድ ነበረበት። ለጥቂት ጊዜ ብቻችንን ለመቆም ካልፈቀድን መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮችን ሳንቀይር ሕይወታችን ያልቃል።
ገጣሚው ሮበርት ፍሮስት እንዳለው በመጨረሻ የሚቆጨን ከሞከርነው ነገር ይልቅ ያልሞከርነው ነው። ብዙ ሰዎች መለያየት ካለባቸው ሰው ጋር በፍርሃት ታስረው አንድ ሕይወታቸውን ያባክናሉ። ማቋረጥ ያለባቸውን ሥራ በፍርሃት አቅፈው ይዘው የፈጠራ አቅማቸውን ያባክናሉ። ብከስርስ በሚል ስጋት አቅማቸውን ይቀብሩታል። ከዛም መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይቀጥላሉ። እያማረሩ ሕይወታቸውን ይጨርሱታል።
በበረዶ ላይ ከወዳጄ ጋር እየተራመድን ነበር። “በዚህ ብርድ ይሄን ሁሉ መንገድ መጓዝ ጥቅሙ ምንድነው?” አልኩት። “ጽናተ ቅስም ታዳብራለህ” አለኝ። ትላንት መጥፎ ያልኩት ዓየር ፀባይ ዛሬ ብሶበት ነበር። ግን ከጥሩ ልብስ ጋር ጭራሽ ለጥቅም አዋልኩት። ስቤን እያቀለጥኩኝ ቅስሜን ደግሞ አጸናውበት።








