top of page
ree


ባብዛኛው የአሜሪካ ክፍል ከፍተኛ ብርድ እና በረዶ የሚያስተናግድበት ወቅት ነው። ማህበረሰቡም ወቅቱን ለመምሰል ይጥራል። ከአለባበሱ እስከ የአኗኗር ዘዬው። በተለይ በመካከለኛው ምዕራባዊ ክፍል ያሉት ግዛቶች ከፍተኛ በረዶ እየጣለባቸው ነው። መንገዱ ጭር ያለ፣ ሰው በጊዜ ወደ ቤቱ የሚገባበት እና የሚሰበሰብበት ወቅት ነው። ከቀኑ አራት ሰዓት (ማለትም በኢትዮጵያ አስር ሰዓት) ጀምሮ ቀኑ መጨለም ይጀምራል። ትላንት በረዶ ከጣለ በኋላ የዚህ ሀገር ተወላጅ የሆነችውን የሥራ ባልደረባዬ ከውጪ ስትገባ አይቻት፣ “በዚህ በረዶ ውጪ ላይ እየተራመድሽ (walk) ነበር? የሚገርመው ግን አንቺ ምንም የመሰለሽ አይመስልም?” ስላት፤ “እኔ እንኳ መጥፎ አለባበስ እንጂ መጥፎ የዓየር ፀባይ የለም ቡዬ ነው ማመን የምፈልገው!” በማለት በዚህ አካባቢ የሚታወቀውን አባባል ተናገረች። “እኔ ግን መጥፎ የዓየር ፀባይ አለ ብዬ አምናለሁ፣ እሱንም አሁን እያየውት ነው” ብያት ተሳስቀን ተለያየን።



ይሄ አባባል ግን ብዙ ልንማርበት እንችላለን። ስንኖር ከኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ፤ ግን እነዚህን ሁኔታዎች የምናልፍባቸው ጥበቦችም እኛ ሰዎች አሉን። መሠረታዊ ሕይወታችን ሳይጓደል እና ሳይስተጓገል አስቸጋሪ ቀናትን ማለፍ እንችላለን። የመጀመሪያው ጥበብ የሚመስለኝ መቀየር የምንችለውን እና መቀየር የማንችለውን ነገር በፍጥነት ማወቅ ነው። ከዛ ሁለተኛ ጥበብ አለ። የሚከተል። አሜሪካኖች አንድ ድንቅ ጸሎት አላቸው ፥ እነዚህን ሁለቱንም ጥበቦች በአንድ ላይ ያዘለ።


“ጌታ ሆይ መቀየር የምችለውን ነገር ታግዬ እንድቀይር ጀግንነትን ስጠኝ ፥ መቀየር የማልችለውን ነገር ደግሞ እንድቀበለው መረጋጋትን አድለኝ። ሁለቱን መለየት የሚያስችልን (መቀየር የሚቻል እና መቀየር የማይቻልን) ጥበብን ለግሰኝ።” የሚል።



የሰው ልጅ ብዙ ዕድሜውን የሚጨርሰው መቀየር የማይችለውን ነገር ለመቀበል ተቸግሮ ሲታገለው፤ መቀየር የሚችለውን ነገር ደግሞ ለመታገል በስንፍና እና በፍርሃት ጊዜ ሲፈጅ ነው። በርግጥ በጣም ከባዱ ነገር የትኛው ነገር ይቀየራል ፥ የትኛው አይቀየርም የሚለውን ማወቁም ላይ ነው። ምክንያቱም ብዙ አይቻልም፣ ይሄ የሰው ልጅ ሊያደርገው ፈጽሞ አይሆንም የተባሉ ነገሮች ተደርገው እና ተለውጠው ታይቷል። ለዚህ ነው ያንን ለመለየት አሜሪካኖች ጥበብን የጠየቁት። ኔልሰን ማንዴላ “it is impossible until it is possible ፥ የማይቻል ነበር እስከሚቻል ድረስ” የሚል አባባል አለው።



ብዙ አንባገነነ መንግስታት በሕዝባቸው ላይ መጫን የሚፈልጉት ስነልቦና እነሱን መቀየር የማይቻል መሆኑን ማሳየት ነው። ለዚህ ደግሞ ራሳቸውን ሥዩመ እግዚአብሔር ከማለት እስከ ፈጣሪ ነን ወደሚል ፕሮፖጋንዳ ይነዛሉ። ብዙሁን ሕዝብም ለብዙ ዘመን የስነልቦና ሽባ ያደርጉታል። አንድ ቀን ያ ደፋር ልጅ “ንጉሱ ራቆቱን ነው” እስከሚል እና የሕዝቡን ዓይነ ጥላ እስከሚገልጥ ድረስ።



በተመሳሳይ የዛሬ ሶስት እና አራት መቶ ዓመታት በዓየር ላይ መብረር ለአዋፋት እና ለመላዕክት ብቻ የተተው ጉዳይ ነበር። የራይት ልጆች ተነስተው ያን እስከሚለውጡት ድረስ። የሰው ልጅ ዛሬ ላይ ያሉት የቴክኖሎጂ ውጤቶች አብዛኞቹ ከመቶ እና ከሀምሳ ዓመታት በፊት በሕልም እንኳ የማይታሰቡ ጉዳዮች ነበሩ። ጥበቡ ያላቸው ሰዎች ግን የማይቻል የመሰለውን ነገር እንደሚቻል አሳዩን። ለዚህ ነው በአሁን ጊዜ፣ አሁን ባለን አቅም መለወጥ የምንችለው ነገሮች ምን እንደሆኑ ከስንፍና እና ከፍርሃት ተላቀን ማሰብ ያለብን።



ያሄ ማለት ግን አሁን ላይ የምንቀበላቸው ውስንነቶች የሉም እያልኩኝ አይደለም። ምንም እንኳ ከመቶ ዓመት በኋላ ሰው እስከ ሁለት መቶ ዓመት መኖር የሚያስችለው የሕክምና ጥበብ ሊመጣ ቢችልም፣ ዛሬ ላይ ግን ሞት ለብዙዎቻችን ከሰማንያ እና ዘጠና ላይ እንደሚሆን መቀበል ያስፈልጋል። በተጨማሪም ትላንትን መመለስ አንችልም። ትላንት ዛሬ ያለን እውቀት ቢኖረን የማንሰራቸው ብዙ ጉዳዮች፣ ጥፋቶች ነበሩ። ስለዚህ ትላንትን መቀበል ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ የተረጋጋ አዕምሮ ያስፈልጋል። የተረጋጋ አዕምሮ ከትላንቱ ጋር ይታረቃል። ትላንቱን ይማርበታል፣ ነገም በሆነ ደረጃ ተገማች እንዳልሆነ ይረዳል። ለምሳሌ ነገ ዋጋው ይወርዳል ብሎ ዛሬ የሸጠው ንብረት ፥ ነገ የበለጠ ዋጋው ከፍ ሊል ይችላል። ስለዚህ ቢረጋጋ እና ቢጠብቅ ሊያተርፍ በሚችለው ሳይሆን የተረጋጋ አዕምሮ የሚጨነቀው፤ ትላንት ለመሸጥ ሲያስብ ለምን እንዳሰበ፣ ለምን እንደዛ ዓይነት ውሳኔ እንደወሰነ፣ ለውሳኔ የተጠቀማቸውን ማስረጃ እና መረጃ እንጂ የሚመረምረው ፥ ትላንትን ዛሬ ላይ ባገኘው እውቀት ቆሞ አይገመግምም። የተረጋጋ አዕምሮ ለወቀሳ አይደለም የሚቸኩለው። ለመማር እና ከተቻለ ዛሬን እና ነገን የተሻለ ለማድረግ ነው።



የተረጋጋ አዕምሮ ጀግንነትን ለማግኘት ይጥራል። ምክንያቱም መለወጥ የሚችሉ ነገሮችን ለመታገል ጀግና መሆን ያሻል። ብዙ ሰዎች ስኬታችንን እስከሚያዩ ድረስ ከጎናችን ለመቆም ይቸገራሉ። ሲሳካልን ነው ሊተባበሩን የሚፈልጉት። ይሄ የሰው ባህሪ ነው። የእኔም የእናንተም ባህሪ ነው። ስኬት ወዳጇ ብዙ ነው። የከሰረን እና የተረሳን ሰው “እሱኮ ምርጥ ወዳጄ ነው” ብሎ በኩራት የሚገልጽ የለም። ስኬታማን ሰው ግን ሁሉም ወዳጁ ለማድረግ ይጥራል። ሁሉም ከእርሱ ጋር ፎቶ ለመነሳት እና የእርሱ ወዳጅ ለመሆን ይጥራል። ይሄ በየትኛውም ዘመን ያለ እና የሚቀጥል ነው። ቢያሳዝንም ጀግና ሰው ግን ይሄን ይቀበላል። ስለዚህ ለመለወጥ የሚታገለውን ነገር ለመቀየር ለጥቂት ጊዜ የብቻ ትግል እንደሚሆን ያውቀዋል። ኖሕ መርከቡን ገንብቶ እስከሚጨርስ ድረስ በፀሐይ እና ዝናብ በሌለበት መርከብ የሚገነባ ሞኝ ነበር። ዝናቡ ሲመጣ እና በርግጥም የመጣው ጎርፍ የተለየ እንደሆነ ሲታይ ብቻ ነው ኖሕ ጠቢበኛ የተባለው። ለብዙ ዘመን ግን ሞኝ ተብሎ ለመቆጠር መፍቀድ ነበረበት። ለጥቂት ጊዜ ብቻችንን ለመቆም ካልፈቀድን መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮችን ሳንቀይር ሕይወታችን ያልቃል።



ገጣሚው ሮበርት ፍሮስት እንዳለው በመጨረሻ የሚቆጨን ከሞከርነው ነገር ይልቅ ያልሞከርነው ነው። ብዙ ሰዎች መለያየት ካለባቸው ሰው ጋር በፍርሃት ታስረው አንድ ሕይወታቸውን ያባክናሉ። ማቋረጥ ያለባቸውን ሥራ በፍርሃት አቅፈው ይዘው የፈጠራ አቅማቸውን ያባክናሉ። ብከስርስ በሚል ስጋት አቅማቸውን ይቀብሩታል። ከዛም መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይቀጥላሉ። እያማረሩ ሕይወታቸውን ይጨርሱታል።



በበረዶ ላይ ከወዳጄ ጋር እየተራመድን ነበር። “በዚህ ብርድ ይሄን ሁሉ መንገድ መጓዝ ጥቅሙ ምንድነው?” አልኩት። “ጽናተ ቅስም ታዳብራለህ” አለኝ። ትላንት መጥፎ ያልኩት ዓየር ፀባይ ዛሬ ብሶበት ነበር። ግን ከጥሩ ልብስ ጋር ጭራሽ ለጥቅም አዋልኩት። ስቤን እያቀለጥኩኝ ቅስሜን ደግሞ አጸናውበት።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 30
  • 3 min read
ree

አንዳንድ ጊዜ እውነተኛ ትምህርት በምቾት ውስጥ ካለፉ ወይም ከስቃይ ውስጥ ከወጡ ሰዎች ነው መማር የምንችለው የሚለውን እርግጠኛ መሆን እቸገራለሁ። ምክንያቱም ብዙ በችግር ውስጥ የሚያልፉ ሰዎች አያለሁ፤ ምቾት ግን የሚገላቸው። ቢሆንም "ሁላችንም ይሄን እንዴት አልፈዋለሁ?" ብለን የምንጨነቀው ችግር ሲመጣ ነው። የዛሬ የሰንበት ጹሁፌ በፍጹም መከራ ውስጥ ያለፈውን ቪክተር ፍራንክል ምክሮች ላይ ያተኮረ ነው። ይሄ ድንቅ ሰው ከመጀመሪያው ግልጽ የሚያደርገው ችግር አንጻራዊ እንደሆነ ነው። በአሜሪካ በሶፋው ላይ ቁጭ ብሎ ያለ ሰው እና በሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት መካከል ያለ ሰው እኩል ሊቸገሩ ይችላሉ። ምክንያቱም የመከራ ከባዱ ክፍል ብዙ ጊዜ አካላዊ ሳይሆን ስነ ልቦናዊ ስቃዩ ነው። “መከራ እንደ ጋዝ ነው” ይላል። “አንድ ጠብታ ጋዝ በበርሜል ውስጥ ቢከተትም ሆነ በአንድ ትልቅ ክፍል ውስጥ የሚቆጣጠረው ክፍት ቦታ ተመሳሳይ ነው።” ያ ጠብታ ጋዝ ክፍሉን ሁሉ መቆጣጠር ይችላል። በተመሳሳይ በበርሜል ውስጥም ቢገባ በርሜሉን ሁሉ ይቆጣጠራል። መከራም ትልቅነቱ እና ትንሽነቱ አይደለም። የዛን ሰው አዕምሮ ትንሽም ይሁን ትልቅ በምልአት ነው የሚቆጣጠረው።



ለዚህ ነው ፍራንክል በናዚ ካምፖች ውስጥ ስላለው እና እርሱ ራሱ ስላለፈበት ሕይወት ሲናገር “ማንም አካሉ ጠንካራ ስለነበረ ያን መከራ አላለፈውም። ይልቁንስ ያን መከራ ያለፉት ሰዎች የመኖር ምክንያት (meaning) የነበራቸው ናቸው” ይላል። “ለምን የሚለውን የመለሰ ሰው የትኛውንም እንዴት ያልፈዋል” ይላል። የተረፉ ሰዎች ከዛ ካምፕ የሚወጡበት ምክንያት ነበራቸው። ሕይወታቸው አሁንም ያላለቀ እና የሚያሳኩት ትርጉም እንዳላት ያምናሉ። ከዛም የተነሳ መከራን እንደ ቅጣት ሳይሆን እንደ ፈተና ብቻ ነው የሚያዩት። ፍራንክል ሳይቀር ከኦሽዊትዝ ካምፕ ወጥቶ ይሄን ስቃዩን ሌክቸር ሲያደርግ እና የሕይወትን ትርጉም ሲያስተምር ራሱን ይስለው ነበር።



ይሄን ያለፉ ሰዎች ባብዛኛው “ይሄ ግን በእኔ ላይ ለምን ሆነ?” ሲሉ አይጠይቁም። “ለዚህ መከራ የሚስማማ ስብዕና ምንድነው? ብለው ነው የሚጠይቁት።



ፋራንክል “ብዙ ጊዜ በሕይወት ምርጫ ላይኖረን ይችላል። መቼም የማንነጠቀው ነጻነት ግን አለን? ይላል። ያም አመለካከታችን ላይ ያለን ነጻነት ነው። በሆነ ሁኔታ ውስጥ ስንሆን በዛ ሰዓት ሊኖረን የሚችለውን አመለካከት የመምረጥ ነጻነት ግን አለን።



ተስፋ ከመቁረጥ አዕምሮአችንን መመለስ፣ የውስጥ ሰላምን ለመጠበቅ ራሳችንን ከክፋት ማራቅ፣ እጅ ላለመስጠት መወሰን፣ በሌሎች ላይ ላለመፍረድ መጠንቀቅ እና ክብርን በትንንሽ ነገሮች ሳይቀር መጠበቅ።



“በሚገርም ሁኔታ በናዚ ካምፖች ውስጥ የሰዎችን መልካምነት ብቻ ተመልክቶ ማን ሊተርፍ እንደሚችል መገመት ይቻል ነበር” ላል ፍራንክል። ቁራሽ ዳቦዎቻቸውን ለሌሎች ያጋሩ፣ በራብ ወቅት ሳይቀር ክብራቸውን የጠበቁ፣ ሌሎች እስረኞችን ያልዱ ሰዎች የመትረፍ ዕድላቸው ሰፍቶ እና ከእነዛ ካምፖች በሕይወት ቆይተው ሲወጡ አይቻለሁ። ይላል።



እዚህ ጋር ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በጻፈው መጽሐፍ ላይ ያለ የወሎ ረሀብ ታሪክ ትዝ ይለኛል። የአሜሪካው ሴናተር ኬኔዲ ረሀብተኞቹን ጎብኝቶ ተመልሶ ሆቴሉ መተኛት ያቅተዋል። በተመለከተው የተራቡ ሰዎች ብቻ ግን አይደለም። እነዛ የተራቡ ሰዎች ሰልፍ ጠብቀው፣ ዳቦ አየን ብለው ሳይጋፉ እና ሳይደባደቡ የተሰጣቸውን አመስግነው ተቀብለው መሄዳቸው እና በዛ ሁኔታ ውስጥ እንኳ ክብራቸውን መጠበቃቸው ነበር ያስደነቀው።



ብዙዎቻችን እንደዚህ ሥርዓት መያዝ እና አለመስገብገብ ሕይወትን ለማስቀጠል ትርጉም ያለው ላይመስለን ይችላል። ይሄ ማንነት ግን በመከራ ውስጥ ቅስምን ከመሰበር ይጠብቀዋል። ቅስም ከአጥንት ውስጥ ያለ አጥንት ነው። የተሰበረ ቅስም ያለው ሰው ጠንካራ አጥንት ቢኖረው እንኳ ቆሞ አይሄድም። የቅስም ጽናቱ ደግሞ ሞራል ነው።




ፋራንክል “አዕምሮ እውነትን መቀበል ሲክድ ይሰበራል” ይላል። የአዕምሮ ጥንካሬ አሁን ያለውን እውነት በመቀበል የሚመጣ ነው። ጽናት መሸሽ ለማንችለው መከራ ትርጉም በመስጠት የሚገኝ ነው። መቀበል ማለት እጅ መስጠት አይደለም። አለመካድ እንጂ። የሚታየውን ነገር ኮስሞቲክስ እና ሊፒስቲክ አለመቀባት እንጂ።



ጽናተ ቅስም ያላቸው ሰዎች ፍርሃትን ካልገሩት ፥ ፍርሃትን እንዲሁ ከፈቀዱለት አሳስሮ እንደሚያስቀምጥ ያውቁታል። ተስፋቸው ህልም አይደለም። ማለትም የዛሬ ሦስት ወር ወይም ከዓመት በኋላ ይለወጣል ብለው አይደለም የሚያምኑት። ይሄ እብደት፣ ይሄ ክፋት፣ ይሄ መከራ ግን እንደሚያልፍ ያምናሉ።



የመከራው ፍጻሜ በግልጽ አልታየው ያለው ጻዲቁ ኢዮብ በወዳጆቹ ወቀሳ ፊት እና በተሸከመው የስቃይ ሰውነት መካከል ቆሞ እንዲህ ነበር ያለው “እኔን ግን የሚቤዠኝ ሕያው እንደ ሆነ፥ በመጨረሻም ዘመን በምድር ላይ እንዲቆም፥ ይህ ቁርበቴም ከጠፋ በኋላ፥ በዚያን ጊዜ ከሥጋዬ ተለይቼ እግዚአብሔርን እንዳይ አውቃለሁ።” ኢዮ 19፥25። ቻርሊ መንገር እንዲህ ይላል “የሚደርስበት የፕሬዠር ደረጃ እንጂ የማይሰበር ሰው የለም።” ምን ያህል ግፊት ይፈልጋል ነው እንጂ ሰው ሁሉ ይሰበራል። ለዚህ ነው ብርቱ ኢዮብ ሳይቀር “ጕልበቴ የድንጋይ ጕልበት ነውን? ሥጋዬስ እንደ ናስ ነውን?” ያለው። ኢዮ 6፥12። በመከራቸው ወቅት “ከዚህ መከራ አንድ ቀን ይታለፋል። በዚህ መከራ ውስጥ የሕይወት ትርጉም አገኛለሁ።” ያሉ ሰዎች የገጠማቸውን የመሻገር አቅም ያገኛሉ።



መከራን ማለፍ የሚችሉ ሰዎች በመከራቸው ሰዓት ሳይቀር ትንንሽ ደስታዎችን ይፈልጋሉ። በሚያዩት የተፈጥሮ ውበት ይደሰታሉ። በዛ መከራ መካከል ከከዷቸው እና ከተዎቸው ሰዎች ላይ ዓይናቸውን አንስተው ባልጠበቁት ሰዓት የደረሱላቸውን ሰዎች ደግነት እያዩ ያመሰግናሉ። በዛ መከራ ውስጥ ሳይቀር በቀልዶች እና በራሳቸው ባህሪ ይስቃሉ። ይሄ ሕይወት ከዚ ውጪ መሆን አይችልም። በዚህ መካከል ማለፍ ነው ስብዕና።




ሕይወት ትርጉም የሚኖራት በመከራ ውስጥ ማለፍ ለፈቀዱ ነው። በዚህ ውስጥ እንኳ እያለፉ ራስ ወዳድነት ሳያሸንፋቸው በመስጠት ሲያምኑ፣ ለእነሱ በቂ ያልነበረውን ለመጋራት ሲፈቅዱ፣ ነውር ሳይነካቸው ወደ መታረጃው ቦታ ሲገቡ ግን ደግሞ ትንሣኤ እንዳለ ፥ ክፋት በመጨረሻ እንደሚሸነፍ ሲያምኑ ፥ የዛኔ የእነርሱ ታሪክ ለማስተማሪያነት እንደሚውል ሲያውቁ ፥ ቅስማቸው እንደ ጸና ፥ አንገታቸው እንደ ቀና ይሻገራሉ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 23
  • 5 min read
ree


በቅርብ እህቴን ስለ አዶናይ ጠየቀኳት። ተደንቃ “አንተ ደግሞ ምን ስትሰራ አወቅከው?” አለችኝ፤ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ እንዳየውት ነግሬያት፤ አሁንም ምን ታስቤያልሽ ስላት ፥ “እኔ ምን አገባኝ፤ አንተስ ደግሞ ስለዚህ ሰው ምን ይጨንቀሃል” ብላኝ በዚህ ዘጋነው።



አዶናይ ግን የዚህ አሁን ያለንበት ዘመን መገለጫ ይመስለኛል። አዶናይ ዝም ብሎ የሚተው ሰው አይመስለኝም። ስለዚህ የሰንበት ዕይታዬን በእርሱ ዙሪያ ላደርግ ነው።



ትላንት አስተሳሰቡን የምወድለት ፈላስፋውን አላን ዶ ቦቶን ስሰማ እንዲህ አለ በመኃል፤ “የጨዋ እና ጥሩ ቤተሰብ አንዱ መገለጫ ልጆቻቸው ምንም የታዋቂነት ፍላጎት ሳይኖራቸው ሲቀር ነው።” አለ። ሲያብራራ “በልጅነቱ ለቤተሰቡ ዓለማቸው እና ሁሉመናቸው እንደሆነ ተሰምቶት ያደገ ልጅ፤ ሲያድግ በማያውቃቸው ሰዎች መወደድን አይናፍቅም። የማያውቃቸው ሰዎች አወቁት፣ አላወቁት፣ ወደዱት ጠሉት ለእርሱ ምኑም አይደለም። በልጅነቱ መታየት፣ መወደድ ያልቻለ ሰው ነው ካደገ በኋላ ይሄን ከሌሎች ለማግኘት የሚጥረው። ልክ የዘጠና ፐርሰን ኮሜዲያንን የልጅነት አስተዳደግ ታሪክ ስታጠኑ፤ በልጅነታቸው ሁሉም የሰዎችን ትኩረት ለማግኘት የሚቸገሩ ነበሩ። ለዚህ ነው ሌሎችን ለማሳቅ ተምረው እና አጥንተው ወደ ዛ ፕሮፌሽን የተሳቡት።”



ይሄን በማህበራዊ ሚዲያ አጋርቼው፤ አንድ ወዳጄ ኮሜንት እስከሚሰጥበት ድረስ እውነት ለመናገር ከአዶናይ ጋር የሚገናኝ አልመሰለኝም ነበር። በኋላ ግን ሰግጥ፤ ፈምስ ትዝ አለኝ።



አዶናይ የዚህ ዘመን ብቻ መገለጫ ሳይሆን፤ የብዙዎቻችንም መገለጫ መሆኑ የገባኝ ለዛ ነው። አብዛኞቻችን በሌሎች መደነቅ፣ መታወቅ እና ምርጥነታችን በሰዎች ሁሉ እንዲመሰከርልን እንፈልጋለን። የኛነታችን Value (ቦታ) ራሱ በተከተሉን እና ባደነቁን ሰዎች ብዛት የሚወሰን ነው። ምክንያቱም ጎስቋላ ልጅነት ነበረን። ልጆችን ደግሞ የሚያሳድገው ቤተሰብ ብቻ ሳይሆን ማህበረሰብም ጭምር ነው።


እኔ እውነት ለመናገር አዶናይን በተለየ መውቀስ አልፈልግም። መጀመሪያ አዶናይ ታናሽ ወንድሜ ቢሆን ኖሮ የምመኝለት እንዲሳካለት ብቻ ነው። ቶልስቶይ ጠላት አድርጋችሁ የምታዩት ሰው የምትወደው እናት፣ የምታዝንለት እህት እንዳለችው ስትመለከቱ፤ ያን ሰው እንደ ሰው ማየት ትችላላችሁ የሚል ዓይነት ፍልስፍና አለው። ለዚህ ነው ወንበዴውን ዶሎኮቭ ስለ እህቱ እና ስለ እናቱ በሞቱ ጫፍ ሰዓት ላይ ሲጨነቅ ያሳየን።ወንበዴውን በወንበዴነት ብቻ ሳይሆን እናቱን እና እህቱን በሞቱ ሰዓት ሳይቀር በሚያስብ አፍቃሪ ወንድምም እንደሆነ እንድናይ ነው የጋበዘን።


የመጀመሪያው አዶናይ ከሌሎቹ በላይ በፍጥነት መታወቅ ቻለ እንጂ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በሁሉም ዓለም የሚታየው ይሄ አይደለምን? በኛ እንኳ ዮኒ ማኛ፣ ሞጣ፣ ጂጂ፣ ዘመድኩን አልነበሩ መድረኩን የያዙት። እነዚህ ሁሉ ሰዎች ጆሮን ጭው የሚያደርግ ነገር የሚናገሩ፣ ታላላቆችን የሚያዋርዱ፣ ለባህል እና ለሞራል ያልተገዙ አልነበሩምን? እነዚህ ሰዎችን ስንቶቻችን በይፋም ሆነ በድብቅ ሰማናቸው?!



በአሜሪካ ውስጥስ ብሔራዊ ጀግና የተባለውን ቻርሊ ከርክን ተመልከቱ። ለኮሚኒቲ ኮሌጅ እንኳ ብቁ ያልሆነ፣ ከየትኛውም ኮሌጅ ያልተመረቀ፣ አንዳች ለማህበረሰብ የሚጠቅም ነገር ያልፈጠረ ግን የሀርቫርድ የሕግ ትምህርት ቤትን ወርቅ የወሰደች የጠቅላይ ፍርድ ቤትን ዳኛ “ጥቁር በመሆኗ ነው እንጂ ለዛ የሚበቃ እውቀት የላትም” ብሎ በድፍረት የተናገረ፣ “ጥቁሮች አይሮፕላን አብራሪ ሆነው ካየው ያ ሰው እውነትም ብቃት አለው ብዬ አስባለው” ያለ፣ ስለ ባርነት በጎ ነገርን የተናገረ ሰው አልነበረም አሜሪካ እንደ ጀግና የቀበረው? ጀግና ያደረገው! ይሄን ልጅ ማህበራዊ ሚዲያ አገነነው እንጂ የትኛው እውቀቱ እና የፈጣራ ችሎታው ነበር እዚህ ያደረሰው? ዛሬ በማህበራዊ ሚዲያ ታዋቂ የሆኑትን ባብዛኛው ተመልከቱ? የትምህርት ደረጃቸውን ተመልከቱ ከዛ ደግሞ ለምን ታዋቂ እንደሆኑ እዩ የምታገኙት ሁሉ እኮ ተመሳሳይ ነው። በትምህርት ደረጃቸው የወረዱ፣ የኮንስፓይረሲ ንደፈ ሀሳብ የሚያራምዱ፣ ትልልቅ የተባሉትን የሚዘረጥጡ እና የሚያዋርዱ ሰዎች ናቸው የተከታይ መዓት ያላቸው።



የእነሱን የተከታይ እና የታዋቂነት መጠን እያዩ ደግሞ ብዙዎች ያን መንገድ እየተከተሉ ነው። ምክንያቱም እብድ የሆነ ነገር ማድረግ፣ ማህበረሰብ ያከበረውን ነገር ለጆሮ ጭው በሚል መልኩ አዋርዶ እና ፈንቅሎ መውጣት ነው የሚያስፈልገው። ከዛ በብዙዎች መታየት፣ የላይክ ብዛት እና የሺዎች እና የሚሊዮኖች ተከታዮች ብዛትን ማሳየት ወይም መሰብሰብ። ፎቶ ትለጥፋላችሁ፣ ጹሁፍ ትለጥፋላችሁ የሚሊዮን ተከታዮች እና ላይኮችን መቁጠር ነው።



አላን ዶ ቦቶን ይሄን ነው የጥሩ አስተዳደግ ማሳያው ልጆቻችሁ ታዋቂ መሆንን ሳይፈልጉ ሲቀር ነው ያለው። ወላጅ ታዋቂ ለመሆን በሚጥርበት ዓለም ውስጥ፣ ልጆች አይፓድ እና ስልክ በሚያሳድጋቸው ዓለም ውስጥ ምን ዓይነት ትውልድ ነው የሚፈጠረው? ይሄን እንጠይቅ አላን ዶ ቦቶን የጥሩ አስተዳደግ አለ እንጂ የትኛው ወላጅ ነው ከዚህ ደዌ የተፈወሰው ቀድሞስ?



የአላን ዶ ቦቶንን ንግግር እየሰማው በተመሳሳይ በጣም ቀዝቃዛ በሆነው የሚሲሲፒ ወንዝ ሥር ረጅም የእግር ዋክ (walk) እያደረኩኝ ነበር። ሁለት ነገሮች መጡልኝ። የመጀመሪያው ሰላማዊ እና ጸጥ ያለ ሕይወት ያለውን ደስታ። የምር በዛ ወንዝ ዳር ያለው የዝምታ ውበት ወደር አልነበረውም። በዛ ውስጥ ምንም ዋክ የሚያደርግም ሰው አልነበረም። ያ እራሱ ገረመኝ። ከዚህ ዝምታ በላይ ውበት የት ኖሮ ነው ሰው የጠፋው? ይሄን የመሰለ ኦርዲነሪ (ተራ) ሕይወት። ማንም የማይሻማችሁ ሕይወት። ተራ ሰው ሆኖ የመኖር ውበት። በዚህ ተፈጥሮ ውስጥ፣ በዚህ ዝምታ ውስጥ ፥ ምንም ሆኖ የመኖር ሕይወት። ግን በሕይወት ሚሊዮን ሰዎች ተክትለዋችሁ ፥ የውስጥ ሰላም ከሌላችሁ ምንድነው? ለጉድ ፈምሳችሁ ፥ ውስጣችሁ ግን ርጋታ ከሌላው፣ የቁስ ክምችት እንዲያፍናችሁ አሁንም አሁንም የምትጥሩ ከሆነ ፥ ምንድነው ረቡ? የሆነ ቀን አሁን ያደነቃችሁ ሰው ሁሉ ሟች ነው። የተደነቃችሁት እናንተም ማንም የማያስታውሳችሁ ቀን ይመጣል። ከዛስ? ፥ ለዚህ ነበር? ያ ሁሉ ትግል!



ሁለተኛው ሀሳብ ሃይማኖት ነው። ምንድነው ሰዎች በሃይማኖት ውስጥ የሚያገኙት? በሃይማኖት ውስጥ ሰዎች የሚያገኙት ፍቅርን ነው። አንድ እስከ ሁለመናቸው የሚወዳቸው አምላክ እንዳለ ነው የሚያውቁት። አንድ ምንም ቢሆኑ፣ ምንም በኃጢአት ቢቆሽሹ፣ መልከ ጥፉ ቢሆኑ፣ ወይም ሰዎች ገበናቸውን ቢያውቁ መቀበሪያ የሚያጡ የሚመስላቸው ሰዎች ሳይቀር ፥ “ፈጣሪ ግን ይወደኛል!” ፣ የሚል ስሜትን ነው የሚያገኙት።



ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች የእርሱ መሆናችንን እንዴት እንዲያውቁ እንደፈለገ ሲናገር ሰምታችሁታል? “በመጨረሻም ካሸነፋችሁ የእኔ መሆናችሁ ይታወቃል” አላለም። “የእኔ መሆናችሁ የሚታወቀው በዓለም ዙሪያ ተበትናችሁ፣ የእኔ ወንጌል መቀበር ካልቻለ እና አሸናፊ ከሆነ ነው እውነተኛ መሆናችሁ የሚታወቀው” አላለም። "ለብዙ ዘመናት ወንጌሌ ከቀጠለ የዛኔ እውነተኛ እንደሆነ እወቁም" አላለም። ይሄ የአይሁዱ  ገማልያል ትምህርት እንጂ የክርስቶስ ትምህርት አይደለም። እውነትን ልክ እንደ "ሽል ከሆነ ይገፋል ቦርጭ ከሆነ ይጠፋል" በሚል ንግግር የለካው ገማልያል እንጂ ክርስቶስ አልነበረም። ክርስቶስ እውነትን የለካው በፍቅር ነው።



የክርስቶስ ትምህርት ይሄ ነው “እርስ በእርስ ከተፋቀራችሁ የዛኔ የእኔ መሆናችሁ ይታወቃል።” ይሄ ነው ሃይማኖት የሰጠን። የፈጣሪያችን የፍቅር ዓይን በኛ ላይ እንዳረፈ ማመን። የአላን ዶ ቦቶንን የጥሩ አስተዳደግ መለኪያ የሚያሟላ ወላጅ ማግኘት በጣም ከባድ ነው። በሰው መደነቅ እና የሰው ዓይንን መናፈቅ አዶናያዊ ናፍቆት የሌለበት ሰው ማግኘት ከባድ ነው። ምክንያቱም የእውነተኛ ፍቅር እጦት ስላለብን።



የተርዕዮን ኃይል ያሸነፉ ሰዎች በፈጣሪያቸው የፍቅር ዓይን እንደታዩ የገባቸው ወይም ያንን የዝምታ ውበት ፥ ያን ኦርዲነሪ ሆኖ የመኖርን ፥ የሰው ኳኳታ እና ጋጋታ የሌለበትን የውበት ዓለም የተረዱ ሰዎች ብቻ ናቸው።



ጌታዬን ኢየሱስ ክርስቶስን ሳስብ እኔ ከማንም በላይ የምትመጣብኝ ያቺ ከወንዝ ዳር ውሃ ልትቀዳ የመጣችው የሰማርያዋ ሴት ነች። የዝች ሴት ታሪክ የምር የገባው ፍጹም የፍቅር ሰው የነበረው ዮሐንስ ነበር። ሕዝብ ሊያስተምር ነው የመጣው ብለው ያሰቡት ደቀመዛሙርቱ ይሄ ታሪክ ወዲያው አልገባቸውም። እርሱ ግን የአንዲት ሴት ሕይወት ግድ አለው።


“በሰማርያም ሊያልፍ ግድ ሆነበት።” ይላል ታሪኩ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ አራት ሲጀምር። የአንዲት ሴት ሕይወት ግድ አለው። የአንዲት። በጠራራ ፀሐይ ለሰዓታት ጠበቀ። ለእርሱ፣ ለዚህ ጌታ እርሷ ልጁ ናትና። ዓለሙ ናት። ሁሉመናው ናት። ስለዚህ ግድ አለው። ፍቅሩ።


ከአንዲት በኃጢአት ከደከመች ግን ደግሞ የውስጧን ድክመት ከዓለሙ ሁሉ ከሰወረች ሴት ጋር ንግግር አደረገ። ብቻዋን አገኛት። “እኔ የምሰጥሽ ውሃ” አላት። ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ለላይክ ቆጠራ የማያመላልስ፣ ለሰብስክሪፕሽን ልመና የማያንቆራጥጥ፣ ለወደዱልኝ እና ምን ተባልኩ ስጋት እዚህም እዛም የማያስብል ፥ “እኔ የምሰጥሽ ውሃ" አላት። አልገባትም። ከዚህ ጥማት፣ ከዚህ የመወደድ ፍላጎት ራብ፣ ከዚህ የመታየት ናፍቆት ውጣውረድ የሚገላግላት የሚያናግራት ፥ ውዷ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑ አልገባትም።



“መቅጃ የለህም እኮ አለችው።” የእርሱ ውሃ ዘወትር መቀዳት የሚያስፈልገው መስሏት። ይሄን ውሃ ግን አንዴ እስከምትጠጪው ነው ከዛ በኋላ አይጠማሽም። እንደዚህ ዓለም ውሃ በጠጣሽው መጠን የበለጠ የሚያስመኝሽ አይደለም። ከጠጣሽው በኋላ እስከ ዘላለም የምትረኪበት እንጂ።



 በዛ ወንዝ ብቻዬን እየሄድኩኝ ነበር። ስለ ሰማርያዊቷ ሴት እና ስለ ጌታዋ ሳስብ እና ያ ስሜት የፈጠረብኝ የውስጥ አስገራሚ ንዳድ ከየትም ቦታ ያላገኘውት ረፍት ነበር የሰጠኝ። በዛ ሰዓት ልክ ሐዋርያው ጴጥሮስ “እባክህ ከዚህ ተራራ አንውረድ” እንዳለው ከዚህ የመገለጥ ፍንጣቂ ወደ ፈምስ ጨለማ እንዳልወርድ ተማጸንኩኝ። ግን ባህሪዬ እዛ ለመርጋት የሚያስችለው ልምምድ አልነበረውም።



የምርጥ አስተዳደግ መለኪያ ልጆቻችን ታዋቂ የመሆን ምኞት ሳይኖራቸው ሲቀር ነው። ላይክ የሚናፍቅ እና የእርሱን እና የሰውን (value) በላይክ ብዛት የሚመዝን ልጅ ካሳደግን ፥ አዎ እንደ ሰማራዊቷ ሴት ከዚህ ድካም ፈጣሪያችን እንዲገላግለን እመኛለሁ። ይሄን ውሃ የቀመስን ቀን ቅንጣት ታክል በሰው መወደድ እና መጠላት ለኛ ግድ አይሰጠንም። ይሄን በጥቂት፣ እጅግ በጥቂት ሰዎች ሕይወት አይቸዋለሁ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page