- Mulualem Getachew

- 15 hours ago
- 3 min read

“መልካም ስም ከብዙ ባለጠግነት ይሻላል፥ መልካምም ሞገስ ከብርና ከወርቅ ይበልጣል።” ምሳሌ 22፥1
ማህበራዊ ሚዲያ ላይ መንግስትን ደግፋችሁም ይሁን ተቃውማችሁ ወይም የሆነ ግለሰብ ወይም ተቋም ላይ የሀሳብ ልዩነት ስታነሱ መጥተው በነውረኛ ስድብ የሚያጥለቀልቋችሁ ሰዎች ተፈጥረዋል። የሚገርመው ደግሞ የእነዚህ ሰዎችን የፕሮፋይል ፎቶ ስታዩ የክርስቶስ፣ ወይም የማርያም ስዕል ወይም ደግሞ የሃይማኖት ተቋም ምልክት ወይም አላህን ወይም ፈጣሪን የሚጠራ ጥቅስ ያዘለ ሆነው ታገኛላችሁ፣ ሁሉም ባይሆኑም እንኳ አብዛኞቹ እንደዛ ናቸው።
የቅዱሳን ወይም የፈጣሪ ወዳጅ ነን ብለው ፕሮፋይል ፎቶ ቀይረዋል ግን የስድብ አፍ አላቸው። ሰዎችን ከማዋረድ፣ ከመስደብ፣ ከመዝለፍ ውጪ ምንም ጨዋነት የተሞላው ክርክር እና ውይይት አያደርጉም። በሀሳብ ለመሞገት አይችሉም። ግን ጸያፍ የስድብ አፍ አላቸው። በዮሐንስ ራዕይ ላይ “ለአውሬው የስድብ አፍ ተሰጠው” ይላል። መቼስ የሚሳደብ አውሬ እስካሁን አላየንም። አውሬው ልንባል የምንችለው ተሳዳቢዎቹ እኛው ነን።
እኔ በወገኔቼ ላይ የማየው ይሄ አስነዋሪ ምግባር የምር ያሳስበኛል። በመጀመሪያ ከፈጣሪ ጋር ያጣላል እግዚአብሔር እርስ በእርሳችን እንድንከባበር አዞናልና በተጨማሪም ልዩነት ማለትም የሀሳብ ልዩነት የብዙ መልካም ነገሮች ውጤት ነው። የተሰበሰው ህዝብ ሁሉ ንጉሱ ራቁቱን ሆኖ እያየው ከፍርሃት የተነሳ ያልለበሰውን ልብስ “ዋው! እንዴት ያምራል!” ሲል ፥ አንድ ልጅ ናት “ንጉሱኮ ራቆቱን ነው!” ያለችው። ይሄ ምሳሌ የሚነግረን ሀሳብን ማፈን የማህበረሰብን ውድቀት እንደሚያፋጥን ነው።
ስንት ድንቅ እውቀት እና ሀሳብ ያላቸው ሰዎች የአውሬዎችን የስድብ አፍ ተፀይፈው ከሀሳብ መለዋወጫ መድረክ ራቁ?! ይሄ ደግሞ ዋልጌዎች ልጆቻችን ላይ ተጽዕኖ እንዲያሳድሩ ፥ እውቀት አልባ ሰዎች መድረኩን እንዲይዙ ዕድል ይፈጥራል።
ዛሬ አንድ ከምደነቅበት የአዲስ ኪዳን ታሪክ ላጋራቹ። በሉቃስ ወንጌል 16:19 ጀምሮ ያለ ብዙ ትምህርት ያለው ታሪክ ነው። እኔ ግን ከጨዋነት አንጻር ብቻ ለትምህርት ይሆነን ዘንድ ልጥቀስ።
ታሪኩ ስለ አንድ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ደስተኛ ስለነበረ ባለጸጋ እና አልአዛር ስለተባለ ድሃ ነው። ድሃው አልአዛር ሲሞት ወደ አብርሃም እቅፍ በመላእክት ተወሰደ። ሃብታሙ ግን ወደ ሲዖል። ከሲዖል ሆኖ ወደ አብርሃም እየተመለከተ “አብርሃም አባት ሆይ ማረኝ፥” እያለ ምህረት እና ውሃ ለመነ። ለእኔ አስደናቂው የአብርሃም መልስ ነበር። ይሄ በሃጢአቱ ምክንያት ወደ ሲዖል የወረደ፣ ለደሃው አልአዛር ፍርፋሪ ለመስጠት እንቢ ያለ ንፉግ ባለጸጋ አሁን በድፍረት ምህረት እና ውሃ ሲለምን፤ አብርሃም ብዙ ማለት በቻለ ነበር። አብርሐም በደሉን አስታውሶ ሊያሳፍረው ወይም ሊሰድበው አልወደደም ይልቁንስ “ልጄ ሆይ” ብሎ መለሰለት እንጂ። ይሄን የተፈረደበት ኃጢአተኛ ልጄ ለማለት አብርሐም አልተጠየፈም።
በዚህ ባለጸጋ የተበደለው ህያው ምስክር ሆኖ በአብርሃም እቅፍ መኖሩ ፥ ለአብርሃም ያልተገባ ንግግር ለመናገር ምክንያትም ሆነ ሰበብ ሊሆን አልቻለም ፥ ይልቁንስ ለሚጠይቀው ጥያቄ ሁሉ ሳይሰለች በአክብሮት መለሰለት እንጂ። ድሃውን አልአዛርን ለማየት ያልፈቀደ ይሄ ባለጸጋ ፥ የአብርሃምን የክብር መልስ ግን አገኘ። በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር ቢፈረድበት እንኳ አብርሃም ግን ልጄ ብሎ በክብር ጠርቶት ምህረት እንደማይደረግለት ነገረው።
ክፉ ዜና ለመንገር እንኳ አንደበቱን ማቆሸሽ አላስፈለገውም። ያንን በክብር ነገረው እንጂ። የመልካምነት ማማ አብርሃም ፥ ከሲዖል ለሚያናግሩት እንደዚህ ካለ ፥ እኛ ገና በዚህ ምድር የመጨረሻ ፍርድ ሳይቀበሉ ላሉት የምናሳየው ርህራሔ ምንኛ መተለቅ ነበረበት።
የአብርሃምን አሉታዊ የሆነ መልስ የሰማው ባለጸጋውም ፥ ከዚህ በኋላ ምን ሊቀርብኝ ብሎ አንደበቱን አላጎደፈም። እስከመጨረሻው “አባት ሆይ” እያለ ነበር አብርሃምን ያናገረው። ወደ ገነት የመግባት ምንም ተስፋ እንደሌለው ቢነገረውም አሁን ግን ከሞት በኋላ ባየው ነገር ይሁን ወይም ያለፈው ዘመኑ ሕይወት ከንቱነት ገብቶት ተስፋ የለህም ሲባል እንኳ አንደበቱ ጨዋነት አልተለየውም ነበር።
ወገኖቼ ቅዱስ ጳውሎስ የሚለን ነገር አለው። “እግዚአብሔር አይዘበትበትም። ሰው ሁሉ የዘራውን ያጭዳል።” ስድብን የሚዘራ ነውርን ያጭዳል። ጨዋነትን የሚዘራ ክብርን ያጭዳል።
መልካም ስም፣ መልካም አንደበት ከምንም ሃብት በላይ ነው። ብዙ እውቀት የማያስከፍተውን በሮች መልካም ምግባር ያስከፍታል። አንደበታችንን፣ አዕምሮአችንን መግራት ያስፈልጋል። ለሰዎች በክብር ለመመለስ እንጣር። እኛ መከበርን እንደምንፈልግ ሁሉ ሌሎችን እናክብር።
ስድቡን ኪቦርድ ላይ ስንፅፈው ሄዶ የሚያርፈው ሰው ልብ ላይ መሆኑን እናስታውስ፥ ተጎጂዎቹና ጉዳቱ ሩቅ ሆኖ ካልታየን እኛ ላይ ሲደርስ ያለውን ህመም እናስታውስ:: ማዋረድ የሰይጣን ባህሪ ነው፥ ዳይብሎስ ነው አዋራጅ:: እኛ ግን በክብር ጌታ ምሳሌ የተፈጠርን ነን እና ለምንናገረው እንጠንቀቅ።
አንደበታችንን መግራት የማንፈልግ ተናዳጅ እና ቁጡ፣ ተሳዳቢ ለመሆን ከወሰንን ደግሞ ቢያንስ የፈጣሪን፣ የቅዱሳንን ስዕል እና ጥቅስ ከፕሮፋይል ፎቶ እንቀይር። ይሄ ሌላ በደል ይሆንብናልና።

