top of page
Search
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew


ስለአድዋ አከባበር ሳስብ፣ በዚህ አከባበር የሚበሽቅ ሰው ወይም የሚናደዱ ስብስቦች ባይኖሩ እንዴት ነበር የሚከበረው ብዬ አስባለሁ? ወይም በዓሉ የይገባኛል ክርክር ባይኖርበት እንዴት ነበር ስለበዓሉ የሚኖረኝ እይታ የሚቀየረው?


ሰዎች ስንባል ስነልቦናችን ድል የሚያሰባስበን፣ ከዛ ደግሞ አሸናፊነትን ለኛ ለማድረግ የምንሮጥ ነን። ማንም ሽንፈትን ወይም ተሸናፊነትን ከራሱ ጋር ማያያዝ አይፈልግም። የሆነ ሰው ሀብታም ወይም ታዋቂ ሲሆን ዘመዴ ነው፣ ጓደኛዬ ነው፣ አውቀዋለሁ ብሎ ለመናገር እና ራሳችንን ከዛ ሰው ጋር ለማያያዝ የምንጥር ነን። አሸናፊው ደግሞ ድልን በራሱ ጥረት ብቻ እንዳገኘ፣ ጉብዝናው እና ብልሃቱ ለዛ እንዳደረሰው በመናገር ከሌሎች እሱ ልዩ የሆነበትን ነገር ለማሳየት ይጥራል። እነዚህ ወደ ማህበረሰብ ሲወርዱ ትርክት ይፈጥራሉ። ሰው ደግሞ በትርክት (story) የሚያስብ ፍጥረት ነው። ይሄ ትርክት ማንነትን ይፈጥራል። ከዚያ በዚህ ማንነት ዙሪያ እነሰባሰባለን። እንጋጫለን። ለዚህ ማንነት ብዙ ዘፈኖች፣ ወረቦች፣ ዲስኩሮች በማውረድ ፥ ከዚህ ማንነት ጋር ሁለመናችንን እናሳስራለን። አድዋ አንዱ የማንነት መገንቢያ፣ የመሰባሰቢያ እና እርስ በእርስ የመጋጫ ትርክት ነው። የድል አድራጊነት ታሪክ ስለሆነ ማንነትን በዚህ ላይ መገንባት የሰው ልጅ ዝንባሌ ነው።


ሽንፈትን ቤትውስጥ እንዳለ ቆሻሻ ከእይታ እንሰውረዋለን፣ የህሊና ሰላምም ስለሌለው ወደማይታይበት መዛግብት እንከተዋለን። ምንም እንኳን ሽንፈት የሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ከድል በላይ በዝቶ የሚገኝ ክስተት ቢሆንም ለማንነት ግንባታ ትርክት ግን አይመችም። ከድል በላይ እውነት (reality) ሽንፈት ነው። ሽንፈት ሰዎች መሸሽ የሚፈልጉትን እና የሚሸሹትን ሕመም እንዲጋፈጡ የሚያደርግ ነው። ድል ብዙ ውሸትን በውስጡ አዝሏል። ድል ከእውነት በላይ ፍላጎት ነው፤ ሽንፈት ግን የፍላጎት መነጽር የጎደለው ለእውነት የቀረበ ነው።



በየዕለት ሕይወታችን ብዙ ማንነት አለን። ከአርሴናል ደጋፊዎች ጋር መድፈኞች ነን፣ ከኦሮቶዶክስ ክርስቲያኖች ጋር ኦርቶዶክሳዊ ነን፣ እንደ ኢኮኖሚ መደባችን የመንግስት ሠራተኞች ወይም ባለሀብቶች ወይም ዲያስፖሮች ነን፣ ከገዢዎች ጋር የገዢው ደጋፊ ነን፣ ከአማጺ ኃይሎች ጋር አማጺያን ነን፣ ቀነኒሳ ወይም የዲባባ ልጆች ሲሮጡ ኢትዮጵያዊ ነን፣ ከሌላው ዓለም ጋር በሚደረግ ትግል አፍሪካዊ ነን፣ በጥቁሮች ላይ በሚደርሰው በደል ጥቁር ከሆነው ሁሉም ሕዝብ ጋር እንቆማለን፣ በምዕራባውያን ሀገር ስንኖር ደግሞ ከኮኬዥያን ውጪ ካለው ጋር የቀለም (color) ሰዎች ብለን ራሳችንን እንመድባለን፣ ስለሰው ልጆች ውድቀት ስናወራ ደግሞ ራሳችንን ከሰው ዘር ጋር ሁሉ መድበን መላዕክት እንዳልሆንን እና መሳሳት የኛ ባህሪ መሆኑን እንናገራለን። ይሄ ሁሉ ማንነት ግን በሆኑ አጋጣሚዎች ወደ ደቃቅ ማንነቶች ወርደው የትግል እና እርስ በእርስ የመገዳደል ምክንያት ይሆናል። አንድ ሰው በአንድ ጊዜ የብዙ ማንነቶች ባለቤት ቢሆንም፣ ግጭት ውስጥ የሚያወርደው ግን የብዙ ማንነቶች ባለቤት መሆኑ እና በጠላትነት ከፈረጀው ጋር ካለው ልዩነት ይልቅ አንድ የሚያደርገው እንደሚበዛ መርሳቱ እና ያን ማሰብ አለመፍቀዱ ነው።



ፋኖ እና ሸኔ ሆኖ እየተዋጉት ላሉት “ሁለቱም ኢትዮጵያዊ እንደሆኑ ወይም ሁለቱም እልም ያለ ድህነት ያደቀቀው ሀገር አባል መሆናቸው እና ሁለቱም ያለምንም የተረጋጋ ሕይወት ይሄን ዓለም በቅርብ የሚሰናበቱ ሰዎች ስብስብ አባል ናችሁ” ብትሏቸው ከመጣላት ቆም ብለው ማሰብ አይችሉም። ምክንያቱም ማንነትን ማሰብ እና ማሰላሰል ረቶት አያውቅም። (ፋኖን ያስነሳው በደል እና ግፍ ሸኔ ጋር አለ ብዬ አላምንም። ሁለቱ በብዙ ነገር የተለያዩ ናቸው)።



አንድም ብዙዎቻችን በጥቁር እና ነጭ (binary) ነው የምናስበው። ጥሩ እና መጥፎ ሰዎች አሉ፣ ደግ እና የዋህ የሆኑ እንዲሁም አረመኔ እና ርህራሄ አልባ የሆኑ ሰዎች አሉ ብለን እንጂ ማሰብ የምንፈልገው፤ በጎ ነገር ለመስራት የሚጥሩ ግን ደግሞ ፍላጎታቸው እያስቸገራቸው መጥፎ ሥራም የሚሰሩ ግራጫ ሰዎች ብቻ ናቸው ያሉት ብሎ ለመቀበል ይቸግረናል። ሁልጊዜ ወጥነት ያለን (consistent) ሰዎች እንድንሆን ስለምንፈልግ ሌሎችንም የምንረዳው እንደዛው ነው። ፍላጎት ደግሞ እውነት ሆኖ አያውቅም።



በቅርብ አንድ ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የተሰደደ እና የሕግ አገልግሎት ለማግኘት ወደ ቢሮአችን የመጣ ኢትዮጵያዊ ሶማሌ፣ ዘሬን ጠየቀኝ። “ቅይጥ ነኝ” አልኩት። “አታጭበርብር፣ ዋናው አባትህ ነው። አባትህ የምን ዘር ነው? አለኝ። ይሄን ሲሰማ የነበረ እዚህ የተወለደ እና ያደገ ሌላ ባለሙያ ደንቆት፣ “ቆይ የእናቱ አይቆጠረም ማለት ነው?” አለው። “አዎ! ዋናው አባት ነው” አለው። ይሄን ሰው እንደምሳሌ አቀረብኩት እንጂ በየቀን ውሎአችን ሰውን በሳጥን ውስጥ ከተን ለመረዳት የምናደርገው ጥረት ሁሉ አንዱን ጥሎ ሌላውን ማንሳት ነው። የሰው ልጅ እንዴት ያለ ውስብስብ የሆነ ፍጥረት እንደሆነ ለመገንዘብ አንፈቅድም። አሌክሳንደር ሶልዦቪስኪ እንዳለው “በጽድቅ በተሞላው የጻዲቁ ልብ ውስጥ የክፋት ጥግ አለ። በክፋት በተሞላው የአረመኔው ሰው ልብ ውስጥ የጽድቅ ድልድይ አለ።” ያን መቀበል ግን ለኛ ፈራጆቹ ከባድ ነው።



ከሶማሌ ክልል የመጣሁ ይሄው የሀገሬ ልጅ፣ ቀጥሎ እንዲህ ብዬ ጠየኩት። “ዘመድ አለህ እዚህ፣ ማነው እየረዳህ ያለው?” መለሰ። “እኛ ሶማሌዎች የኛ ጎሳ ካለ ይበቃናል፣ በጎሳ እንረዳዳለን። እናንተ ሀበሾች ግን የተቸገረ ሰው ስታዩ ከንፈራችሁን በመምጠት፣ እጃችሁን ጭንቅላታችሁ ላይ በማድረግ ምስኪን፣ ሲያሳዝን ብላችሁ አልፋችሁ ትሄዳላችሁ” አለኝ። ነገሩ እንደቀልድም እንደ ጥሩ እይታም ቢያስቀኝም፣ ይሄ በእርስ በእርስ ጦርነት ለ30 ዓመታት እርስ በእርስ ሲገዳደሉ ከኖሩ ማንነቶች ጋር ራሱን በጎሳ የሚያዛምድ ሰው ነው የመሀል ሀገሩን ሰው፣ በሱ አጠራር ሀበሾች የሚላቸውን በአስመሳይነት የከሰሰው። እውነት ነው የሶማሌ ማህበረሰብ እርስ በእርስ የመረዳዳት ባህል አለው። እርስ በእርስ የመገዳደልም ሰዋዊ ባህል ግን አለው። ያን የክፋት ጥግ ግን ሁልጊዜ እንደቆሻሻ ጠርገን ከሰው እይታ እንሰውረዋለን፣ ከህሊና ግንዛቤ እናርቀዋለን። ምክንያቱም ለማንነት ግንባታ አይመችም።



ከመቶ ዓመት በፊት አድዋ ላይ ድል ያደረጉ የአርበኞች ልጆች ነን። ነገር ግን መቶ ዓመት ሙሉ በረሀብ የምናልቅ፣ በስደት የምንረግፍ፣ በሕግ የሚመራ ሀገር መመስረት ያልቻልል፣ ሀገራችን ድረስ መጥተው ሊገዙን ወደ መጡት ነጮች ሀገር መሄድ እና መኖር ከልጅነት ጀምሮ ህልማችን የሆንን ዜጎች እና በክላሺንኮቭ መሳሪያ ወንድም ወንድሙን እየጣለ የሚኖርባት ሀገርም ፈጣሪዎች ነን። የመጀመሪያው ለዘፈን ይመቻል፣ ሁለተኛው ግን የየቀን ሕይወታችን እውነት ነው።

 
 
 
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew




ስትራቴጂ ጽንሰ ሀሳቡ የመጣው ከውትድርና ወይም ጦርነት ነው። ለዚህ ነው ስለስትራቴጂ ሲነሳ ሁልጊዜ በተቀናቃኝ ላይ ብልጫ ከመያዝ አንጻር የሚሆነው። ምክንያቱም በመሠረቱ ስትራቴጂ ማለት በተቀናቃኝ ላይ የመጨረሻውን የድል ብልጫ መውሰድ ማለት ነው። ነገር ግን ስለስትራቴጂ ማውራት እና ስትራቴጂ ቀርጾ በተግባር ላይ ማዋል ለየቅል ናቸው።



በዚህ ጹሁፍ ስለ ስትራቴጂ ዓምስት ጉዳዮችን እዳስሳለሁ፤



፩) ስትራቴጂ ለዘላቂ አሸናፊነት የግድ ያስፈልጋል፤



፪) ስትራቴጂ መሪነትን ይፈልጋል፤



፫) ስትራቴጂ እና ተጽዕኖ መፍጠር የማይነጣጠሉ ናቸው፤



፬) ታላላቅ ስትራቴጂዎች ግባቸውን እንዲመቱ የተከታዮች እና የመሪዎች ጽናት ምሰሶ ነው፤



፭) ስትራቴጂ በየጊዜው ራሱን ከሁኔታዎች ጋር ማስማማት መቻል አለበት፤



፩) ስትራቴጂ ለዘላቂ አሸናፊነት ወሳኝ ነው፤



በውትድርና መጥፎ ስትራቴጂ ወይም ስንኩል ስትራቴጂ ሲኖርህ ግልጽ ላልሆነ ፖለቲካዊ ግብ ትዋጋለህ፣ የአቅርቦት እና የሪሶርስ እጥረት በየጊዜው ያጋጥምሃል፣ ያለአቅምህ ትለጠጣለህ ከዛም “utopia” የሆነ ፈጽሞ የማይሳኩ ግቦች ይኖሩሃል። ይሄ የመጥፎ ስትራቴጂ ወይም የስንኩል ስትራቴጂ ውጤቶች ናቸው። በቢዝነስ ተቋሞችም ውስጥ ተመሳሳይ ነው። የቢዝነሱ ግብ እና አቅም እና ችሎታ ያላቸው ሠራተኞች የሚያጠፉት ጊዜ የተራራቀ ነው። ቢዝነሱ ያለአቅሙ ይለጠጣል፣ በሁሉ ነገር ይነከራል፣ ሁሉን ነገር ለማግበስበስ ይጥራል።



የስትራቴጂክ ስህተት እና የኦፕሬሽን ስህተቶች ውጤታቸው የተለያየ ነው። ስትራቴጂው ጥሩ ሆኖ ኦፕሬሽኑ ላይ ስህተት ቢሰራ ማረም በጣም ቀላል ነው። የተሳሳተ ስትራቴጂ ኖሮ ግን ኦፕሬሽኖችህ ቢሳኩ እንኳ እምብዛም ጥቅም የለውም። ስለዚህ ሳስብ ዘወትር እንደምሳሌ የሚመጣልኝ ጌታችን በስሙ አጋንንት ያወጡትን ሰዎች ያላቸው ነው። “ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ በስምህ ትንቢት አልተናገርንምን ፥ በስምህስ አጋንንትን አላወጣንምን ፥ በስምህስ ብዙ ተአምራትን አላደረግንምን? ይሉኛል። የዚያን ጊዜም። ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች፥ ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ።” እነዚህ ሰባኪያን ኦፕሬሽን ሌቨል (level) ላይ የተሳካ ሥራ የሠሩ ነበሩ፣ ብዙዎች ማሳካት ያልቻሉትን ነገር የፈጸሙ ነበሩ። ነገር ግን ያ ሁሉ በተሳሳተ ዓላማ ላይ የቆመ ስለነበረ አላውቃችሁም ተባሉ።



እኔ ይሄን ለስትራቴጂ ጥሩ ምሳሌ አድርጌ የምወስደው በሕይወት ብዙዎቻችን እንደዛ ስለሆንን ነው። ገንዘብ ማግኘትን ስትራቴጂክ ግባቸው ያደርጉና በመጨረሻ ግን ቤተሰብ አልባ እና ጤና አልባ የሚሆኑ ሰዎች የስትራቴጂ ስንኩልነት የገጠማቸው ናቸው። በሀገር ደረጃ ደግሞ የትግራይ ጦርነት ትልቁ የስትራቴጂ ውድቀት የታየበት ነበር። መቀሌ መግባት ኦፕሬሽን ማሳካት እንጂ ስትራቴጂ አልነበረም፣ በዚህም ምክንያት ያ ጦርነት ሀገሪቷን ያደማ፣ ቤተክርስቲያንን የከፈለ፣ ማንም ያላተረፈበት ሆነ። መንግስት በአማራ ክልል የተከተለው የትጥቅ አስፈታለው ኦፕሬሽንን ተመልከቱ፦ ምን ነበር ስትራቴጂው? ከዛ ምን አስከተለ? ምን ላሳካ ብሎ ትጥቅ ካልፈታችሁ አለ? አሁን የተከሰተውን እና ማጠፊያ ያጣውን መዓት ተመልከቱ። ወደ ቤተክርስቲያን ስንመጣ ደግሞ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ወጥቶ እና ከፍተኛ ጊዜ እና ገንዘብ ተርከፍክፎባቸው የሚደገሱ የመዝመሩ፣ የጉባኤ ድግሶች የስትራቴጂ አለመኖር ወይም የመጥፎ ስትራቴጂ ውጤቶች መሆናቸውን ለማወቅ ብዙ ራሱ ሳንቆይ ከዛ በኋላ የሚከሰቱ ልዩነቶችን ማየት ብቻ ይበቃል። ምንድነው ያስገኙት ውጤት? የወጣባቸው ልፋት እና የተለወጠው ነገር ይመጣጠናል? ምንድነው የምር ያሳካነው? በመጨረሻ እነዚህን ሁሉ ከምን አንጻር መዝነናቸው ስትራቴጂው ልክ ነበር ወይም አይደለም እንበል? የማይመዘን፣ የማይገመገም እና የመመዘኛ እና የመገምገሚያ መስፈረት ያላስቀመጠ ስትራቴጂ ገና ከመነሻው ችግር ያለበት ነው።



መጥፎ ስትራቴጂ ኖሮን በኦፕሬሽ ጉዳዮች ላይ መከራከር ጊዜ ማጥፋት ነው። እኔ ብዙ ጊዜ ራሴን ከእንደዚህ ዓይነት ጉዳዮች ማራቅን ነው የምመርጠው ፥ ትልቁን ስዕል ለማየት ፍቃደኛ የሆነ አዕምሮአዊ ክህሎትን ማሽተት ካልቻልኩ። ምክንያቱም የተሳሳተ ስትራቴጂ ኖሮ ስለኦፕሬሽን ማውራት ፥ መኪና እንደሚያባርር ውሻ መሆን ነው። መኪናውን ቢደርስበትም ውሻው ምንም አያደርገውም። ነክሶ አያደማው፣ ቦጭቆ አይበላው።



ጥሩ ስትራቴጂ ዓላማን ከተግባር ጋር የሚያዋህድ ነው። ሁለቱን ማጋባት ሲችል ስትራቴጂው ጥሩ ነው ይባላል። ይሄ ማለት ካለን አቅም፣ የሰው ኃይል፣ ሪሶርስ እና ሁኔታ ጋር የተዛመደ ተግባሮችን ማሳካት ከምንፈልገው ዓላማ ጋር ስንቀርጽ ጥሩ ስትራቴጂ ይባላል።



በመነሻዬ እንዳልኩት ስትራቴጂ ተቀናቃኝ ባለበት ሁኔታ የሚቀረጽ እና መነሻውም ከጦርነት ነው።



ስለዚህ ስለስትራቴጂ ስናስብ የግድ ከግንዛቤ መውሰድ ያሉብን ሦስት ነጥቦች አሉ፤



1) የኛን መጎዳት ወይም መክሰር የሚፈልግ ጠላት ወይም ተቀናቃኝ እንዳለን ማመን ያስፈልጋል።


በዚህ ዓለም ላይ ጦርነት ፈጽሞ ሊቆም እንደማይችል ማመን ከሞኝነት የመላቀቂያ የመጀመሪያው ደረጃ ነው። በተመሳሳይ ዓላማ አንግበን፣ አንዳች ነገር ለማሳካት ስንነሳ በሁሉም አቅጣጫ ጠላቶች እንደሚነሱብን መቀብል የተግባራዊ አስተሳሰብ ጅማሮ ነው። የእኛ መነሳት ወደድንም ጠላንም የሚጎዳው አካል ይኖራል። ያ አካል በቻለው መጠን ይዋጋናል። የእርሱ የበታች አድርጎን ለማቆየት ወይም ለማጥፋት ይሰራል። ስለዚህ ስትራቴጂ ይሄን ሁልጊዜ ከግንዛቤ መውሰድ አለበት።



2) ስትራቴጂ የሚጸናባቸው ግምቶች ለጥሩ ስትራቴጂ እጅግ ወሳኝ ናቸው። ማንኛውም ስትራቴጂ ሲቀረጽ ስለራስም ሆነ ስለተቀናቃኝ ወይም ከኛ ውጪ ስላሉ ነገሮች ጠንቅቀን አናውቅም። ስለዚህ ስትራቴጂያችን ከሞላ ጎደል በግምቶች (assumptions) ላይ የተመሰረተ ነው። ስለዚህ የስትራቴጂያችን ጥራት በግምቶቻችን ጥራት ላይ ይመረኮዛል። በውትድርና ውስጥ እነዚህን ግምቶች በስለላ ተቋሞች በኩል ሲገኝ፣ በግለሰብ ሕይወትም ሆነ በተቋሞቻችን ስለተቀናቃኞቻችን ያለንን እውቀቶች የምንሞላበት መንገዶች ሊኖሩን ይገባል። አለበለዚያ የሚኖረን ስትራቴጂ ሳይሆን ህልም እና ርዕይ ነው።



3) ጥሩ ስትራቴጂ በአንድ ሀሳብ፣ መሳሪያ ወይም ግለሰብ ብቃት ወይም አቅም ላይ የተንጠለጠለ ፈጽሞ መሆን የለበትም። የትኛውም ጥሩ የውትድርና ስትራቴጂ ባሉት ጥቂት መሳሪያዎች (ከጠላት በሚሻሉ) ላይ ተንጠልጥሎ ተሳክቶ አያውቅም። ወይም በአንድ ግለሰብ ላይ ተመርኩዞም ዘላቂ አሸናፊነት አይገኝም። ከታዋቂ ጄኔራሎች እና የጦር መሪዎች ጀርባ ቀላል የማይባሉ ስትራቴጂክ አሳቢዎች እና የኦፕሬሽን አስፈጻሚዎች አሉ። ዓለም ልብወለድ እና ድራማ ስለሚወድ አንድ ናፖሊዮ፣ አንድ አሌክሳንደር፣ አንድ ምንሊክን ማድነቅ ይወዳል እንጂ ከእነዚህ ምርጥ የጦር ጄኔራሎች ጀርባ ከእነሱ የማይተናነሱ ሌሎች ምርጦች ነበሩ። በተመሳሳይ የሁለተኛው የዓለም ጦርነትም ሆነ ቀዝቃዛው ጦርነት አሜሪካ ከጀርመን ወይም ከራሺያ የሚልቁ ምርጥ መሳሪያዎች ስላሏት አይደለም ያሸነፈችው። ይልቁስ ብዙ ነገርን ታሳቢ ባደረገ እና ውህደት (synergy) በፈጠረ፣ በየጊዜው ራሱን እያሻሻለ እና እየተማረ በሚሄድ ስትራቴጂ እና መሪዎች ምክንያት ነው ያሸነፈችው። ተቀናቋኇቿ ደግሞ ይሄ አልነበራቸውም።



በግል ሕይወትም ከችግር ለመውጣት ገንዘብ የሚጠይቅ ሰው እምብዛም ከችግር እንደማይላቀቅ አምናለሁ። ለእንደዚህ ዓይነት ሰውም ሆነ ተቋሞች የሚሰጥ ገንዘብ ከብክነት ብዙ ለይቼ አላየውም። ምንም ጥርጥር የለውም ገንዘብ በኦፕሬሽን ላይ የሚያስፈልግ ትልቅ ሪሶርስ ነው። ነገር ግን ገንዝብ ስትራቴጂ ሆኖ አያውቅም። በጎስቋላ ሕይወት ውስጥ ያለ ግለሰብም ሆነ እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ያሉ ተቋሞች የገንዘብ ችግር አይደለም ያለባቸው። እንደውም ገንዘቡ የችግሩ አካል ሆኖ እንጂ የምንመለከተው። እንደ ኮዳክ ካሜሬ እና ኖኪያ ስልክ የመሰሉ ኩባንያዎች መሪዎቻቸው እያለቀሱ ከገበያ የወጡት የገንዘብ እጥረት ስለነበረባቸው አልነበረም። ስለዚህ ስለጥሩ ስትራቴጂ ስናስብ ገንዘብ ስላለን፣ ወይም አንድ ምርጥ ሰው በመካከላችን ስላለ፣ ወይም ጥሩ መሳሪያዎች ስላሉን ስትራቴጂያችን ይሳካል ብለን ማሰብ የለብንም።




 
 
 
Writer's picture: Mulualem GetachewMulualem Getachew



በእኔ ዓይነት ሥራ ወይም የሰዎችን መከራ እና ስቃይ መስማት የየዕለት ሥራችሁ ሲሆን ፥ ሰውን የሚያሳዝን እና የሚያስለቅስ ታሪክ ልክ የፀሐይ በምስራቅ የመውጣት ያህል ኖርማል ይሆንባችዋል። በሂደት፣ ብዙ ሰዎች እንደሆኑት፣ ትደነድናላችሁ። በተለይ ይሄ ሥራዬ ነው ብላችሁ ከወሰዳችሁት ፥ ራሳችሁን እንዲረበሽ አትፈቅዱለትም። በዚህም ሰዎች ለእናንተ ቴክኒካል ችግር ይሆኑባችዋል። ልክ እንደ ማሽን መጠገን ከቻላችሁ የምትጠግኗቸው፣ አለበለዚያ ግን የምትተዎቸው።



በቅርብ ከአንድ የሕግ ትምህርት ቤት ፕሮፌሰሬ ጋር ምሳ ነበረን። በመኃል በቅርብ የመኪና አደጋ ደርሶባት ሆስፒታል ገብታ ስለነበረችው ሚስቱ በትካዜ ያወራኝ ጀመር። ስለሕክምናው ሲነግረኝ፤ ለዶክተሮቹ ሚስቴ ቴክኒካል ችግር (techinical problem) ነበረች። ለነርሶቹ ግን ሚስት፣ እናት፣ ሴት እና የእነሱን ርዳታ ፈልጋ በእጃቸው ላይ የወደቀች ተረጂ ነፍስ ነበረች። ዶክተሮቹ እንደ ማሽን ለመጠገን ዓይተዋት ሲወጡ ፥ ነርሶቹ ግን አጽናንተዋትም ጭምር ነበር የሚለዩን አለኝ።



ከሰዎች ጋር የሚያገናኝ ሥራ እንሰራ ይሆናል። እንጀራ የሚያመጣ። የሰዎች ችግር የገንዘብ ምንጫችን ሊሆን ይችላል። ግን እነዛ ሰዎች ሰውነታቸው ከተረሳን ፥ በመጨረሻ የራሳችንን ልብ ጭምር እናጣዋለን። ዋረን በፌት ለሼሬ ሆልደሮቹ ዛሬ በጻፈው ዓመታዊ ሪፖርት ፥ “ይሄን ሪፖርት ትላልቅ ኩባንያዎች በየዓመቱ እንደሚያዘጋጁት ዓይነት ሪፖርት ዓይደለም የምንጽፈው እና የምናዘጋጀው። ይልቁንስ እኛ ሼር ሆልደር ብንሆን ምን ዓይነት ሪፖርት ነው ማንበብ የምንፈልገው ብለን በማሰብ ነው የምናዘጋጀው። ገንዘባችሁን እኛን አምናችሁ ፥ በኛ ኩባንያ ላይ ኢንቨስት ካደረጋችሁ ፥ ልክ እኛ በእናንተ ቦታ ብንሆን ማንበብ የምትፈልጉትን በማሰብ ነው የምንጽፈው” ይላል። ለዚህም ነው የበፌት ዓመታዊ ሪፖርት እንደ ልብ አንጠልጣይ ፊልም በጉጉት የሚጠበቀው። የሚነበበው። ለምን? ምክንያቱም ራሱን በሌሎች ጫማ ውስጥ መክተት ችሏል። የሌሎችን ሰውነት የየቀን ዕለታዊ የሆነው ሥራው እንዲያስረሳው አልፈቀደም። ያን ነው ትልቅ ልብ የምለው። ያ ልብ በፈጣሪ የሚያምኑ ሰዎች ሁሉ ለፈጣሪያቸው የሚሰጡት ልብ ነው። ሁላችንም አምላካችንን ትልቅ ነው ብለን እናምናለን። ሺ ዘመናት ተደጋግሞ ቢሰማው ፥ ምንም የሱ ጉልበት ፍጹም ኃያል ቢሆን ፥ ፊት ለፊቱ ተንበርክኮ የሚለምነውን ፍጥረቱን ግን ለመስማት ያዘነብላል ብለን እናምናለን። የኛ ስቃይ ለሱ ትልቅ ወይም አዲስ ስለሆነበት ሳይሆን ፥ ትልቅ ልብ ስላለው እንጂ።



ትልቅ ልብ ያለው መሪ ሲኖረን ፥ ሕጻናት ተጨፍጭፈው የችግኝ ተከላ ድግስ ደግሶ የሰዎችን ለቅሶ ለርሱ የሁልጊዜ ሥራው እንደሆነ አያስመስልም። ብዙዎቻችን ይሄ የሚጠቅመው የኛን ተገልጋይ ብቻ ይመስለናል። በፍጹም። ራሳችንን እንጂ። ሥራችን ሌሎችን እንደ ማሽን አሳይቶ ፥ የሰውነት ልብን ሊነፍገን ካልቻለ ፥ በመጨረሻ ሰዎችን የመረዳት እና የመገንዘብ ታላቅ ልብ ገንዘብ እናደርጋለን። ሰውነትን በምላት የመጎናጸፍ ዕድል እናገኛለን። ከዚህ የሚገኝ ርካታ ደግሞ ወደር የለውም።



ትልቅ ልብ ማለት የኛን ርዳታ ፈልጎ ፊትለፊታችን የቆመው ሰውን እኔ ብሆን እንዴት ነው የሚሰማኝ ብሎ የሱ ቁስል እንዲሰማን የመፍቀድ ልምምድ ነው። ዛሬ አሜሪካ ውስጥ የምታዮቸው መሪዎች ፥ አቅም እና ጉልበት የሌላቸውን ምስኪን ስደተኞች በሰንሰለት አስረው ወደ ማጎሪያ ማዕከል በመጣል መደሰት የቻሉት ፥ “ሕገወጦች” የሚል ስም ስለሰጧቸው ነው። ያ ስደተኞችን ለማሰቃየት እና የእነሱን ታሪክ ለመስማት እንዳይችሉ አቅሙን ሰጣቸው። እኛም የተለየን አንሆንም። ቆም ብለን ፥ የሌላውን ሰው መከራ ወደ ራሳችን ለማስጠጋት ካልወሰንን። እኔ ብሆንስ ካላልን።



ቶሎስቶይ በ1500 ገጽ በከተበው "ዎር ኤንድ ፒስ" መጽሐፍ ውስጥ አስገራሚ ብቃቱን የገለጸበት ሦስት መስመር ጹሁፉ ይመስለኛል። ዶሎኮቭ የተበላ ቁማርተኛ፣ የሽጉጥ ፍልሚያን የሚያዘወትር፣ ቢጠጣ ቢጠጣ የማይጠረቃ እና ቤተሰብ እንዳላሳደገው የሚኖር ሰው ነበር። የተለያዩ የአውሮፓ አገራትን ትምህርት ቀምሶ ወደ ሩስያ የመጣ እና የአባቱን ግዙፍ ሃብት በመውረስ ሃብታም ከሆነው "ፒየር" ከሚባል ሰው ጋር ዶሎኮቭ ይጣላል። የሽጉጥ ፍልሚያ የጥሉ መቋጫ እንዲሆን ይስማማሉ። ሁሉም ዶሎኮቭ ካለው ፍጹም የልምድ ብልጫ በመነሳት ፒየርን እንደሚገለው ገመቱ። ከፍልሚያው በፊት ዶሎኮቭ ለወዳጁ ሮስቶቭ "ይኸውልህ ወደ እንደዚህ ዓይነት ግጥሚያ ስትሄድ እንደምትሞት አስበክ ኑዛዜ ጽፈክ፣ የመጨረሻ ቃልህን በሚያምር ቃላት ከትበኸ መጓዝ የለብህም። ግን እንደምትገድል ቅንጣቢ ጥርጣሬ ሳይኖርኽ ከገባህበት ሁሉም ነገር ይሰምራል። ልክ እንደ ድብ አዳኝ ፥ ፍርሃቱን ከገለጠ ድቡ ያንን በማሽተት እንደሚያከሽፍበት ሁሉ ፣ ፍርሃት ከተሰማክ ሁሉ ነገር እዛው ያከትማክ።" ሲያቀብጠው እዚህ ጉድ ውስጥ እንደገባ የገባው ፒየር ግን አንዴ ለግጥሚያው እሺ ብያለው እንግዲህ የፈሰሰ ውሃ አይታፈስ በሚል ፍልሚያው ሜዳ ላይ ቆመ። ፒየር ዶሎኮቭን ክፉኛ አቆሰለው። ዶሎኮቭ ፒየርን ሳተው። ሮስቶቭ ጓደኛውን አቃቅፎ ወደ እርዳታ ከነፈ። በመኃል ዶሎኮቭ እያቃሰተ እነዚህን ቃላት ይተፋል "ይሄን ከሰማች ትሞታለች፣ አትተርፍም፣ ለእኔስ ግድ የለኝም እሷ ግን ... እሷ ግን ቆማ መሄዷን እንጃ። ወይኔ ... ይሄን ጉድ ...ማየት የለባትም ... በሕይወት አትኖርም ..." ሮስቶቭ ግራ ገባው! "ስለ ማን ነው የምታወራው?" አለው። "ስለ ... እናቴ! .... ስለ እህቴ!" ከዚህ በኋላ ሮስቶቭ አዕምሮ ውስጥ የተመላለሰው ቃላቶች ናቸው ዘወትር የሚገርመኝ። "ዶሎኮቭ ወንበዴው፣ ዶሎኮቭ ቁማርተኛው፣ ዶሎኮቭ አጭበርባሪው ... አፍቃሪ ልጅ እና ወንድምም ነበር!"



በኢኮኖሚክስ የኖቤል ተሸላሚ የሆነው እና የሆሎኮስት ተራፊ Daniel Kahneman በደች ግዛት ውስጥ ከጀርመን ወታደሮች ቤተሰቦቹ ደብቀውት እያለ ከተደበቀበት ቦታ አፈትልኮ ይወጣል። "መንገዱ ኦና ነበር። ሰው አይታይም" ይላል ጊዜውን ሲያስታውስ። "ዞር ስል አንድ ወታደር ጋር ዓይን ለዓይን ተጋጠምን። ለመሸሽ ሞከርኩ። ጠራኝ። ሮጬ ማምለጥ እንደማልችል ስለገባኝ ወደ ወታደሩ ሄድኩ። የናዚ ጀርመን ወታደር ነበር። በሁለት እጆቹ ወደ ላይ ላጥ አርጎ አነሳኝ። ዓይኖቹ እንባ አቀረሩ። ስንት ዓመትህ ነው አለኝ። ነገርኩት። 'አንተን የሚያህል ልጅ አለኝ። በጣም ናፍቆኛል' ብሎ ሳመኝ እና ወደ መሬት መለሰኝ።" ዳኒ ስለ ሰው ያለው አመለካከት ከዛ ጊዜ ጀምሮ እንደተለወጠ ይናገራል።


ዳንኤል የእውቀት ልህቀቱ እና የሰውን ተፈጥሮ በማወቅ አቻ የማይገኝለት ሰው የነበረ ቢሆንም እስኪሞት ድረስ ግን ሰዎችን ነጭ ወይም ጥቁር ብቻ በሚል ፍረጃ (ማለትም ጥሩ ወይም መጥፎ) ወጥመድ ሳይወድቅ ቀረ። በክፉው እና በደካማው ሰው ውስጥ ሳይቀር የጽድቅን ልምላሜ ፥ የሰውነትን ዘር ማሽተት እንዲችል ሆነ። ትልቅ ልብ ማለት ያ ነው። ትልቅ ሆኖ ለመሞት ፈቀደ። ትልቅ ሰው ሆኖ ይሄን ትንሽ ሕይወት ፈጸመ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page