top of page
Search
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 24
  • 3 min read
ree

አንዱ ፍላጎታችን መሉ በኩልሄ መልስ ማግኘት ነው። የትኛውንም ጉዳይ ብንችል በአንድ ሳጥን ውስጥ መክተት እና መረዳት እንፈልጋለን። የምናቃቸውን ሰዎች በምድብ ከፍለን ጥሩ እና መጥፎ ብቻ ወይም ወዳጅ እና ጠላት እንዲሆኑልን እንፈልጋለን። ስለሕይወትም ያለን አረዳድ ሕይወት ትግል ወይም ሕይወት ከባድ እንደሆነ ብቻ ነው። ስለ መንግስትም ሥርዓቶች ያለን ግንዛቤ ጨቋኝ፣ በዝባዣ፣ ፋሺስት ወይም ከኛ የሆነ እና ስህተቱ ይቅርታ የሚባልለት ወይም ነጻ እና ተራማጅ የሆነ ጥቅል ሳጥኖች ናቸው። በመንፈሳዊ ዓለምም የሚድን እና የማይድን፣ ሲዖል ወይም ገነት የሚገባ ብቻ ነው ያለን።


አሁን ላይ በጣም እየተረዳውት የመጣውት ነገር ለሰው ልጅ አዕምሮ ሪያሊትን መረዳት በጣም ከባድ ነገር እንደሆነ ነው። ይሄ ዓለም ከአዕምሮአችን የመረዳት አቅም በላይ በጣም እና እጅግ ውስብስብ ነው። ለምሳሌ ከሰዎች ጋር ስንኖር ግንኙነታችን እከሌ የሚባለው ሰው ሁልጊዜ ጥሩ ስለሆነ አይደለም ወዳጃችን የሚሆነው። ይልቁንስ እኛ የምህረት አቅም ለእርሱ ስላለን ጭምር ነው ወዳጅነት የሚጸናው። ወዳጅ ያልነው ሰው ስለእኛ የሆነ ጊዜ ክፉ ያስባል። እኛም ከዛ ክፋት ነጻ አንሆንም። ከቅናት ወይም ከሌሎች ያልተገናዘቡ ስሜቶች ተነስተን ያን ሰው የሚያሳዝን ባህሪ ወይም ንግግር ልናሳይ፣ ልናወጣ እንችላለን። ለዚህ ነው የምህረት እና የይቅር ባይነት አቅም ያላቸው ሰዎች ብቻ ዘላቂ የሆነ ወዳጅነት የሚገነቡት። እራሱ ውስጥ ያሉትን የክፋት ባህሪዎች እና ሀሳቦች ማስተዋል ያልቻለ ሰው ከሌሎች ጋር ጤናማ ግንኙነት ሊኖረው አይችልም።


ዴቭ ሻፔል ስለ ቢል ኮዝቢ አንድ ያለው ነገር ነበር። ከገደለው ይልቅ ያዳነው ይበልጣል። ከሰዎች ጋር ስንኖር ይሄ ይመስለኛል ውሃ ልኩ። ከሚገለው ይልቅ የሚያድነው ይበልጥ እንደሆነ መጠየቅ። ለብዙ ነገሮች ውሃ ልኩን ማግኘት ነው ወሳኝ። በሕይወት ውስጥም ብዙ ሰዎች የተዛባ ሕይወት የሚኖራቸው ውሃ ልክ ሳይኖራቸው ሲቀር ነው። ወይ አብልጠው ከብዙ ነገር ይልቅ ገንዘብ ይወዳሉ። ወይ ፍጹም አባካኝ ይሆናሉ። ፍጹም የሥራ ፍቅር ይይዛቸው እና ሁሉን ችላ ይላሉ ወይም ሰነፍ ሆነው የሰው ጥገኛ ይሆናሉ። ወይም ፍጹም ሰውን ያምኑና ሲታለሉ ይኖራሉ ወይም ሁሉን ተጠራጣሪ ሆነው ለደስተኛ ሕይወት መሠረት የሆነውን ሰውን ማመን ይሳናቸዋል። በእንግሊዘኛ ይሄ Adjusted ያልሆነ ሕይወት ይባላል።



አጀስት ያልሆነም እውቀት አለ። ሁሉን ነገር በኛ የፕሮፌሽን ዓይን የማየት ብቻ እውቀት። ወይም ጥቂት መጽሐፍ ብቻ በሕይወት ያነበበ ሰው ዓለምን በእነዛ መርሕሆች ብቻ ለመዳኘት እንደሚሞክረው ማለት ነው። በቅርብ የሠላሳ ዓመት ሴት ልጅ ያላት አንድ የሰባ ስድስት ዓመት ነጭ ጋር እያወራን፤ ሴት ልጇ የእርሷን ምክር ለመስማት ምንም ፈቃደኛ አለመሆኗ ገርሟት ታወራኛለች። የስነ ልቦና ባለሙያ ስለነበረች የሴት ልጇ ችግርን ከነ መፍትሔው ታውቀዋለች። ግን መች ለመስማት ፈቅዳ። ሕይወትን ተዋግታ ሕይወትን የኖረች ሴትዮ ፊት ለፊቷ እያለች ሴት ልጇ የርሷ የዓለም ዕይታ የተሻለ ጥራት እንዳለው ታስባለች። አስባ ስኬታማ ብትሆን አንድ ነገር ነው። ግን በሕይወት ከውድቀት ወደ ውድቀት ነው እየሄደች ያለችው።



አንድ ጥሩ የሚያነብ በአስራዎቹ መጨረሻ ያለ የዘመድ ልጅ አለ። ከእኔ ጋር ሲያወራ የእርሱ ፍላጎት የእርሱ የዓለም ምልከታ ትክክል እንደሆነ ለማሳየት ነው ጥረቱ። አንዳንዴ እገረማለሁ። የምገረመው በወጣቶች አዕምሮ ነው። ሁላችንም ያለፍንበት ዓለም ነው። የእኔም የዛ የሃያ ዓመቶቼ አዕምሮ ጭምር ነው የሚደንቀኝ። የሆነ መስመር አንበን ወይም ሰምተን ሁሉን ነገር በዛ የመመዘን ፍጥነታችን እና ከኛ ተለቅ ያሉ ሰዎች የሚያሳዩንን የሕይወት ዝግታ እንደ ሞኝነት የመቁጠራችን ዝንባሌ ማለቴ ነው።



ትልቁ ጥበብ ራስን መግዛት የሆነው ለዚህ ነው። ራስን መግዛት በራሱ እውቀት ሆኖ ሳይሆን ራሱን የገዛ ሰው ብዙ ውሳኔዎችን ማዘግየት ስለሚችል ነው። ያዘገየው ተገዶ ሳይሆን ፈቅዶ ሲሆን ማለቴ ነው። ያን የሚያደርግ ሰው እውነትን ለማግኘት ጥረቱን ስለማያቆም በትግስቱ ውጤቱን ይለውጠዋል።



ሕይወት በነጠላ አትሰራም። እያንዳንዱ ነገር የተያያዘ ነው። አንድ ሰው አንዳች ጥሩ ነገር ሲያደርግ ለኛ በጎ ብቻ አስቦ አይደለም። ለራሱም አስቦ ነው። መጥፎ የሚያደርግም ሰው ለራሱ ብቻ ጥሩ ስላሰበ አይደለም። በዛ ውስጥ የተጎደለ ፍትሕን በራሱ መንገድ ለማሻሻልም በመጣር ነው። በአንድ ጊዜ ብዙ ነገሮች አብረው እንደ ድር ይሰራሉ። ሕይወት ስትሰራ ይሄ ባይሎጂ ነው፣ ይሄ ኬሚስትሪ ነው፣ ይሄ ፊዚክስ ነው፣ ይሄ ቲዎሎጂ እያለች አትንቀሳቀስም። ሕይወት ጭራሽ እነዚህን ክፍፍሎች አታውቅም። ለምሳሌ አንድ መጥፎ ነገር የሚያደርግ ሰው በአንድ ጊዜ የሞራሉ ስንኩልነት፣ የዓየር ጸባዩ መጥፎ መሆን፣ መጥፎ ከማድረጉ በፊት የገጠመው ሕይወት፣ ጥሩ እንቅልፍ አለመተኛቱ በትክክል እንዳያስብ አድርጎት እና ሌሎች ተጨማሪ ጉዳዮች በአንድ ላይ መጥተው ሊሆን ይችላል። ብዙ ጊዜም እውነታው ይሄ ነው። ለዚህ ነው ብዙ ነገሮችን የሚያውቁ ሰዎች በጣም ጥሩ ውሳኔ የመወሰን አቅማቸው ከፍ የሚለው። ምክንያቱም ሪያሊትን በተሻለ የመረዳት አቅም አላቸው እና።


የተገናዘበ ሕይወት ማለት ውጪውን ከመረዳት በላይ ውጪውን የምንረዳበት እና የምናይበትን መንገድ በጥልቀት ማወቅ ነው። በሌሎች ላይ ለመፍረድ እና ለመጨከን የሚሮጥ ሰው ከፈረደባቸው ሰዎች ስብዕና በላይ ስለራሱ ማንነት ይነግረናል። የተገናዘበ ስብዕና ላይ የደረሰ ሰው በውስጡ የሚርመሰመሱ ስሜቶችን ሁሉ ያለ ማፈር እና መሸማቀቅ እውቅና ይሰጣቸዋል። የዚህ ዓለም ዕይታው እና ነገሮችን የመረዳት አቅሙ ከእነዚህ ከውስጡ ከሚመነጩ የስሜት ውጊያዎች ነጻ እንደማይሆን ይረዳል። ዓለሙን የመረዳት አቅሙ ራሱን በተረዳበት መጠን የተወሰነ እንደሆነ ስለሚያውቅ፤ ሪያሊትን የማወቅ ውስንነቱ ገደብ እንዳለበት ያለጥርጥር ይገባዋል። ለዚህ ነው የሕይወት የፍጽማና አቅጣጫ ለሰው ልጅ በባላንስ ብቻ የሚደረስበት የሚሆነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 5 min read

የሰንበት ዕይታ - 16

ree

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አከራካሪ ከሆኑ ነገሮች አንዱ እና የተለያዩ ሊቃውንትም ግራ ከሚጋቡበት ነገሮች ውስጥ ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው እንስሳት ለምግበ እስራኤል መለየታቸው ነው። በተለይ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ ላይ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ መልካም መሆናቸው በይፋ ተገልጾልን፣ ፍጥረቱን እንደሚወድ እና እንደሚመግባቸው በብዙ የመጽሐፍ ክፍል ተነግሮን ሳለ፣ እንደገና ንጹሁ የሆኑ እና ንጹሁ ያልሆኑ ተብለው መለየታቸው እስራኤሎችን ሳይቀር ግራ የሚያጋባ ነው።



ከክርስቶስ ልደት በፊት በግብጽ አሌክሳንደሪያ ብዙ ግብጾች ይኖሩ ነበር፤ በአይሁድ የአመጋገብ ምርጫ የሚደነቁ ሄለናዊያን እና ግሪኮች እነዚህን አይሁዶች ለምን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆነ ምግቦች በማለት አንዳንድ እንስሳትን እንደማይበሉ ጠይቀዋቸው ነበር። ፋይሎ የሚባል ሊቅ በሰዓቱ ለዚህ ምክንያት ነው ያላቸውን ዘርዝሮ ጽፎ ነበር። የአርስጣጢለስ ደብዳቤ ለአሌክሳንደርም ይሄን ጉዳይ ያብራራል። እውነታው ግን በርግጠኝነት ማናቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁት ነው የሚያሳየው።


ይሄ በዘሌዋውያን ምዕራፍ 11 እስራኤል እንዲበሉት ተብለው የተጠቀሱት እንስሶች አንዳንዶቹ በእንደዚህ ባህሪያት ተለይተዋል፤


፩) የተሰነጠቀ ሰኮና ያለውንና የሚያመሰኳውን እንስሳ ሁሉ ብሉ።

፪) በባሕሮችና በወንዞች ውስጥ ክንፍና ቅርፊት የሌላቸው ሁሉ በእናንተ ዘንድ የተጸየፉ ናቸው።

፫) በአራት እግሮቹ ከሚሄድ እንስሳ ሁሉ በመዳፎቹ ላይ የሚሄድ በእናንተ ዘንድ ርኩስ ነው፤

፬) በሆዱ የሚሳብ፥ በአራትም እግሮች የሚሳብ፥ ብዙ እግሮችም ያሉት፥ በምድርም ላይ የሚንቀሳቀሱ ተንቀሳቃሾች ሁሉ የተጸየፉ ናቸውና አትብሉአቸው።


ስለሚበሩ ወፎች የተነገረ መለያ ሕግ ባይኖርም፤ የማይበሉት እንደ ቁራ፣ ዳክዬ፣ ጥንብ አንሳ ተዘርዝረዋል።


በብሉይ ሕግ ስለንጽህና በምግብ ብቻ ሳይሆን በአልባሳትም ተጠቅሷል። ለምሳሌ ሁለት ዓይነት ቀለማት ያሉት ልብስ መልበስ ንጹሁ አይደለም። የሞተ እንስሳ መንካትም እንዲሁ ከንጽህና ያሶጣል። እነዚህን ነገሮች ማድረግ ኃጢአት ነው ሳይሆን፣ ወደ ተቀደሰው ቤት እና ወደ መቅደሱ ለመግባት ግን የመንጻት ሥርዓትን መፈጸም ያስፈልጋል።


አንዱ የሊቃውንት መከራከሪያ እነዚህ ንጹሁ አይደሉም የተባሉ እንስሶች በጣዖት በሚያመልኩ ሕዝቦች ዘንድ የአማልክቶቻቸው ወካይ ናቸው ተብሎ መጠቀሱ ነው ይላሉ። ለምሳሌ በዮሐንስ ራዕይ ሰይጣን በእንቁራሪት ተመስሏል፣ እንቁራሪት ደግሞ ንጹሁ አይደሉም ስለዚህ አትብሏቸው ከተባሉት ነው ወገኑ። ሌላኛው መከራከሪያ ደግሞ ንጹሁ የተባሉ እንስሳት የወገኖቻቸው ወካይ ናቸው፤ ለምሳሌ በውሃ ውስጥ የሚኖር እንስሳ ክንፍና ቅርፊት ከሌለው የአሣን መስፈረት አያሟላም ፥ ስለዚህ ያን ዘር (የአሣን) አጉዳይ ስለሆነ ንጹሁ እንዳልሆነ ይቆጠራል የሚል ነው።



በስፋት በሀገራችን ሊቃውንት ሳይቀር የምንሰማው መከራከሪያ ደግሞ ዝምድና ነው። ለምሳሌ አሳማ ሁሉን የሚበላ፣ የሚከረፋ፣ ሆዳም ስለሆነ ያንን እንደ ኃጢአተኛ እና ከክብሩ እንደተዋረደ ማንነት አድርጎ በምሳሌ በማቅረብ፤ ለመብላት ንጹሁ ያልተባለው ለዛ ነው የሚል ነው። ጥንብ አንሳም ከዚህ ምሳሌ የሚካተት ነው።


ሌሎች ደግሞ ንጹሁ የተባሉት እንስሳት ለፈጣሪ በመሥዋዕት መልክ የሚቀርቡ በመሆናቸው፤ የፈጣሪ ምግብ ናቸው፣ በዚህም ንጹሁ ተባሉ። በተቃራኒው አሳማ፣ ግመል ደግሞ ለመሥዋዕት ስለማይቀርቡ፣ የሰው ልጆችም መብላት የለባቸውም የሚል ነው።


ሌሎች ደግሞ እንደ ጠንካራ መከራከሪያ አድርገው የሚያነሱት ከጤና አንጻር ነው። እንደ እንቁራሪት፣ አሳማ ያሉ እንስሶች ከውሏቸው እና አመጋገባቸው አንጻር ለጤና አደገኛ ስለሆኑ (ሁሉን የሚያግበሰብሱ በመሆናቸው) ለዛ ነው አትብሉ የተባልነው ይላሉ።


እውነት ለመናገር ከላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎች እምብዛም አሳማኝ አይደሉም። ለምሳሌ ቀላል የማይባሉ ንጹሁ የተባሉ እንስሶች የክፋት ምሳሌዎች፣ የባዕድ አምልኮ ምልክቶች ነበሩ። በንጽህናም ከወሰድን ፍየል እምብዛም ከአሳማ የሚለይ የአመጋገብ ሥርዓት የለውም። ዶሮም ሁሉን የሚመገብ ነው። ከጤናም አንጻር የሚነሳው ክርክር ውሃ የሚቋጥር አይደለም። አሳማ ከምግባር አንጻር በመጥፎ እና በሁሉ አግበስባሽነት ቢመሰልም፣ በምንም ክፋት የማይመሰሉ እንስሶችም ንጹሁ አይደሉም እና አትብሏቸው ተብሏል። ለምሳሌ ዳክዬ፣ ሎብሰተር፣ ፈረስ እና ሌሎችም። ስለዚህ የክፋት ምሳሌ ናቸው መባሉም አሳማኝ መከራከሪያ አይደለም። ለፈጣሪ ምግብነትም (ከመሥዋዕት አንጻር) ተብሎ የሚቀርበው ምክንያት መሻገር የማይችሏቸው ነጥቦች አሉት። ለምሳሌ ለመብላት ንጹሁ ሆነው ለእግዚአብሔር ግን በመሥዋዕትነት ማቅረብ የማይፈቀዱ እንስሶች ነበሩ። አጋዘን አንዱ ነው። ይበላል ግን አይሠዋም።



ከበሽታ እና ከንጽህና አንጻርም እስራኤሎች የተለየ ጤናማ ሕዝቦች አልነበሩም። ንጹሁ የተባሉ እንስሳትን ብቻ በመብላታቸው ያተረፉት የተለየ የጤና ጉዳይ የለም። ሌሎች በሚጠቁበት በሽታ ሁሉ ተጠቅተዋል። ረዥም ዕድሜ በመኖር በአርኬዎሎጂ ጥናት መሠረት ሩቅ ምስራቆች የተሻሉ ናቸው። እነዚህ ደግሞ በአመጋገብ ባህላቸው ከእስራኤሎች የተለዩ ነበሩ።


አንድ መገንዘብ ያለብን ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ንጹሁ እንስሳት እና ንጹሁ ያልሆኑ ብሎ ለመብል ሲከፍላቸው ፈጽሞ ከሰውነት ጤና እና ከረዥም ዕድሜ ጋር እንዳላያያዛቸው ነው።

በዚህ ክርክር ውስጥ እግዚአብሔር ለእስራኤላውን ንጹሁ እና ንጹሁ ያልሆኑ እንስሳት፣ አዕዋፋት እና የባህር እንስሶች ብሎ ሲለይ በምን ምክንያት ነው የሚለውን ከዳሰሱ እና አሳማኝ ሆነው ያገኘውትን ነጥቦች ልዘርዝር፤


1) መገደብን፣ እንቢ ማለትን ማስተማር፤


ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፥ “ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ ሁሉ ግን አይጠቅምም። ሁሉ ተፈቅዶልኛል፥ በእኔ ላይ ግን አንድ ነገር እንኳ አይሠለጥንብኝም።” እግዚአብሔር ሁሉን መልካም አድርጎ ከፈጠረ በኋላ፣ በገነት ውስጥ መታዘዝን፣ የሰውን በፍጥረቱ ውስጥ ያለውን ቦታ እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት የምታሳይ ያለመብላት ሕግ አውጥቶ ነበር። ያ ፍሬ በገነት ውስጥ ከነበሩት ፍሬዎች የተለየ ውበት ወይም ማስቀየም እንዳለው የተነገረን ነገር የለም። ሔዋን ለመብላት ስታስብ ፍሬው ያማረ እንደሆነ ከማየቷ በቀር። ይሄ ግን ሌሎቹ የሚበሉ ፍሬዎች ከዛ ዛፍ ያነሰ ውበት ወይም አስጎምጅነት እንዳላቸው ምንም አልተገለጸም። አንድ ነገር ግን ተነግሮናል፣ ያ ዝፍ የሞት ፍሬ መሆኑ። ምክንያቱም እርሱን መብላት ያለመታዘዝ ምልክት ነው። የአመጽ ምሳሌ ነው። በተመሳሳይ ለእስራኤል ንጹሁ እንስሳት ተብለው የተዘረዘሩትን በመስመር ማስቀመጥ እና ሁሉንም በሆነ መስፈረት ማኖር አይቻልም (arbitrariness አለባቸው)። ይሄ የሚነግረን ጉዳዩ ከመብልነት እጅጉን የተሻገረ እንደሆነ ነው።


እስራኤል እንቢ ማለትን፣ ለእግዚአብሔር ሲል መተውን፣ በዚህም ራስን መግዛትን እንዲማር የወጡ ሕጎች ናቸው። የሥጋ ትልቁ ፍላጎት እና ፈተና የሆነውን መብላት በመገደብ ፥ እንቢ ማለትን እና የፍቃድ ጡንቻን ማጠንከርን ለእስራኤል አስተማረው። እስራኤል እነዚህ የኛ ምግቦች አይደሉም፣ ለኛ አይሆኑም በማለት በሕይወት ራስን መገደብን እና ኃጢአት እንኳ ባይሆን ለእኛ የተፈቀደ አይደለም በማለት እንቢ ማለትን በሕይወት እንዲማሩ የተተከለ የፍቃድ (will power) ጡንቻ ማጎልበቻ ናቸው። ለእግዚአብሔር ስንል ምክንያት እንኳ ባይኖረው እንቢ ማለትን እንዲማሩ አደረጋቸው። በዚህም በሕይወት ነገሮች ስላጓጓቸው እና ስሜታቸው ስላሻው ብቻ እንዳያደርጉ ፥ ለምኞታቸው እንቢ የማለትን ጡንቻ ገና በጊዜ እንዲያዳብሩ አደረጋቸው።


የአይሁድ ቤተሰቦች በዚህ ዘመን ሳይቀር ይሄን የምግብ ባህል በጥንቃቄ ይከተላሉ። ተመልከቱ ይሄ ራስን የመግዛት፣ በዚህም የሕይወት ስኬትን የመቆናጠጥ ማንነት ከአይሁድ ዘር በላይ በዚህ ዓለም ማን ምሳሌ ሊሆን ይችላል። የኖቤል ሽልማትን ብቻ ውሰዱ። እስከዛሬ ከ965 የኖቤል ተሸላሚዎች ውስጥ፣ 214 አይሁዶች ናቸው። በአሜሪካ ውስጥ የአይሁድ ቁጥር 2.4% ነው፤ በአሜሪካ ቢዝነስም ሆነ ፖለቲካ ግን 71% ከሚሆነው የነጩ ማህበረሰብ ምንም ያልተናነሰ ተጽዕኖ የአይሁድ ማህበረሰብ ነው ያለው። በዚህ ዓለም ላይ ከቁጥሩ አንጻር የአይሁዶችን ያህል ስኬት የተጎናጸፈ አንድ ዘር መጥራት የሚችል ይኖራል? የትኛውንም የስኬት ሜትሪክሶችን አምጡ እና የአይሁድን ማህበረሰብ አስቀምጡ፤ ይሄ ማህበረሰብ ካለው ቁጥር አንጻር እጅግ አስገራሚ ስኬት የተጎናጸፈ ሆኖ ታገኙታላችሁ።


ማንንም ጠይቁ ፥ ለጊዜያዊ ፍላጎቱ እንቢ ማለት የቻለ ሰው፣ ራሱን መቆጣጠር እና መግዛት የሚችል ሰው በምንም ዘርፍ በመጨረሻ ያሸንፋል። ይሄን ነበር በምግብ እግዚአብሔር ለእስራኤል ያስተማራቸው። በዚህ ሕግ ሕይወታቸውን ሁሉ አበራላቸው። እንቢ የማለትን ማንነት አጸናላቸው።


2) ሥርዓትን ያስተምራል ፦ መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ላይ “ዓላማ ይዞ እንደ ተሰለፈ ሠራዊት የምታስፈራ ማን ናት?” እንዳለው ጠቢቡ፤ በሕይወት ሥርዓት ያለው ትንሽ ሠራዊት ሥርዓት የሌለውን እልፎች ይረታል። ዛሬም ስለእስራኤላውን ይሄ እውነት ነው። ጎረቤቶቻቸው በቁጥር በስንት እጥፍ እየበለጧቸው፣ ራሳቸውን የለዩ፣ በሥርዓት ማንነታቸውን ያሰለጠኑ በመሆናቸው በእልፍ የሚበልጧቸው በፊታቸው ይርዳሉ። (You develop an ordered soul that says no to certain things).


3) ማንነት ነው ፦ እነዚህን ምግብ እኛ እስራኤላውያን በመሆናችን አንበላም በማለታቸው ፥ ራሳቸውን ሁሉን ከሚበላው ዓለም ለዩ። በዚህም በቁጥር በብዙ እጥፍ ከሚበልጡአቸሁ ጎረቤቶቻቸሁ ማንነታቸውን ጠብቀው ማቆየት ቻሉ።


4) የእግዚአብሔርን ንጽሕ እና ቅድስና የሚያሳይ ነው። ለምሳሌ ሴቶች በወራዊ ልማዳቸው ወቅት ወደ ቅዱሱ ስፍራ ወንዶችም ዘራቸው የፈሰሰ እንደሆነ ወደ እግዚአብሔር መቅደስ እንዳይገቡ በብሉይ ሕግ ተደንግጎ ነበር። ሴቶች ወራዊ ልማዳቸውን ማስቀረት የሚችሉት ነገር አይደለም፤ ስለዚህም ኃጢአት አይደለም። ነገር ግን ወደ ቅድስናው ስፍራ በዚህ ወቅት መቅረብ አይችሉም፤ ለምን? ይሄ የእግዚአብሔርን ቅድስና እና ንጽህና የሚናገር ነው። “እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፤ ሰውነታችሁን ቀድሱ፥ ቅዱሳንም ሁኑ፥ እኔ ቅዱስ ነኝና፤ በምድርም ላይ በሚሳብ ተንቀሳቃሽ ሁሉ ሰውነታችሁን አታርክሱ።” ዘሌዋውያን 11፥44። ኃጢአትን አለመስራት አንድን ሰው ቅዱስ አያደርገውም። ቅድስና የዓላማ ተግባር ነው (affirmative action)። ቅድስና መተግበርን ይሻል፣ መራቅን ብቻ አይደለም። አንድ ሰው ኃጢአት መሥራት እየቻለ፣ ስለእግዚአብሔር ብቻ ሲል ከተወ ያ ቅድስና ነው። ምክንያቱም የዓላማ ተግባር ነውና። ቤቱ ውስጥ ምግብ የሞላለት እና ምንም ያልጎደለበት ሰው ላይሰርቅ ይችላል። አለመስረቁ ቅዱስ አያደርገውም። ከመጸወተ ግን ያ ቅድስና ነው። ሰይጣን ስለኢዮብ ያለው ይሄን ነበር። “እርሱ ስለሞላለት፣ ምንም ስላልጎደለበት፣ ዙሪያውንም ከክፍ ስላጠርክለት እንጂ ምንም ጽድቅ የለውም” ነበር ያለው። ሰይጣን ሳይቀር ከኃጢአት መራቅ በራሱ የጽድቅ ምልክት እንዳልሆነ ያውቃል ማለት ነው። እነዚህ ምግቦች ለእግዚአብሔር ሲባል ብቻ መተውን፣ በዚህም መቀደስን የሚያስተምሩ ምልክቶች ናቸው።


በአዲስ ኪዳን እነዚህ ምግቦች ያላቸው ቦታ ግልጽ ነው። በቤተክርስቲያናችንም እንዴት እንደሚታዩ ብጹዑ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የቤተክርስቲያን ታሪክን በጻፉበት መጽሐፋቸው ዳሰውታል።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Aug 10
  • 4 min read

የሰንበት ዕይታ - 3

ree

ካርል ማርክስ እና ሼክስፒር በዚህ ጉዳይ ይለያያሉ። ካርል ማርክስ ሰዎች የሚጣሉት ስለሚለያዩ ነው ይላል። የተለያዩ ግቦች፣ ፍላጎቶች፣ አይዶሎጂ፣ የተለያየ ቁሶች ስላላቸው ነው የሚጣሉት ይላል። ሼክስፒር ግን በሮሚዮ እና ጁሊየት እና በሌሎችም ሥራዎቹ እንደገለጠው ሰዎች የሚጣሉት ስለሚመሳሰሉ ነው ይላል። እኔ ሼክስፒርን በሙሉ ስቀበል ፥ ካርል ማርክስን ደግሞ በከፊል ልክ ነው እላለው።


ብዙ ጊዜ የምንቀናው ከኛ በሀብት እና በንብረት ወይም በሆነ ነገር የሚመሳሰለንን ሰው እንጂ ከኛ በጣም በራቁ ሰዎች አንቀናም። በቢልጌት ወይም በኤለን መስክ እኛ አንቀናም። የምንቀናው ልንደርስበት በምንችለው ወይም አብሮን ከኛ ጋር በነበረ ሰው ነው። ቃዬል በአዳም አልቀናም በመንታ ወንድሙ አቤል እንጂ። ኤሳው በያዕቆብ ፥ የዮሴፍ ወንድሞች ከኛ እሱ በምን በልጦ ነው ብለው በወንድማቸው ዮሴፍ፣ አሮን እና ማርያም በወንድማቸው በሙሴ ቀኑበት ይላል። ይሄ ሁሉ የሚያሳየን ሰዎች የሚጠላሉት ስለሚመሳሰሉ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥም በጣም በሚቀራረቡ ብሔሮች መካከል ነው ጥላቻ እና ግጭት ያለው። በትግራይ እና በአማራ፣ በትግራይ እና በኤርትራውያን፣ በኦሮሞ እና አማራ (በቁጥር ስለሚቀራረቡ)፣ በወላይታ እና በሲዳማ፣ በአኝዋክ እና ጉምዝ፣ በኑዌር እና ዲንካ እያለ ይቀጥላል። በዓለም ላይም ጥላቻ እና ግጭት በሚቀራረቡ መካከል እንጂ በሚራራቁ መካከል ጠብ የለም።


የሦስተኛው ክፍለዘመን የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቅ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ሙሴን ለመከራ የዳረገው የሚራራቁት የዕብራውይ እና የግብጻዊ ጠብ ሳይሆን በሁለት ወንድማማቾች ዕብራውያን ጠብ ነው ለስደት የተዳረገው ይላል። ይሄንንም ሲገልጽ የሚለያዩ ነገሮች ጠብ ቀላል እና ውጪያዊ ነው ስለዚህም መገላገል ቀላል ነው ይላል። የሚመሳሰሉ ሰዎች ወይም የወንድማማቾች ጠብ ግን የመረረ ነው ፥ ለዚህም መገላገል እጅጉን ከባድ ነው። ይሄንንም ሲያጠቃልል እንዲህ በሚል ዘመን ተሻጋሪ አባባል ነው የዘጋው “ማንም ሰው ተቀናቃኙ በእርሱ ላይ የድል ኃይል እንዳለው ምልክት ካላገኘ በቀር በእርሱ ላይ ሐዘን አይሰማውም። ” ይሄ ማለት ሰው በሕጻን ልጅ ስድብ አይናደድም ፥ አቻው ወይም ወዳጁ ሲሰድበው ነው የሚናደደው። ማናችንም ተቀናቃኝ የምንላቸው አቻዎቻችንን ነው። በሞተ ሰው ወይም ከኛ በብዙ በሚያንሱ እና በብዙ በሚበልጡ ላይ ንዴት የለንም።



ካርል ማርክስ ደግሞ ያስተዋለው ሰዎች ለግጭት የሚሰጡትን ትንታኔ ነው። አዎ ማንም ሰው ግጭት ውስጥ ሲገባ “ስለቀናው ነው፣ እሱ ያለውን ስለተመኘው ነው፣ እሱን ስለተፎካከርኩት ነው፣ እሱ እንዳይደርስብኝ ነው” አይልም። ምክንያቱም ይሄ ግጭቱን ምክንያት ያሳጠዋል ፥ ተከታይ እና ደጋፊን ይነሳል። ለራሳችንም እንደዛ ብለን ማመን አንፈልግም።


የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ምንድነው?


ብዙዎቻችን እንቀናለን ፥ የምንቀናው ደግሞ በጎረቤታችን ወይም በብዙ በሚመስለን ነው።(መጽሐፍም ባልጀራን ውደደው ያለው ፥ ባልንጀራን መውደድ ከባድ ስለሆነ ነው።)ይሄን ለማወቅ ከፈለጋችሁ ዓይናችሁን ጨፍናችሁ ስኬታቸውን ስትሰሙ ወዲያው ደስታ የማይሰማችሁ ሰዎችን አስተውሉ። ወይም በሆነ ነገር ከናንተ ሊያንሱ የሚችሉበትን ነገር ሲያገኛቸው ደስ የሚላችሁ ሰዎች እነማን ናቸው? እነዚህ ሰዎች በብዙዎቻችን ሕይወት ውስጥ አሉ። በእህት እና ወንድም ወይም በእህትማማቾች፣ በጣም በቅርብ ጓደኞች መካከል ነው ባብዛኛው የሚኖረው። ይሄ ስሜት ሲመጣብን ፈጥነን ለማውገዝ አንቸኩል። ይሄ ስሜት ከጥንት ጀምሮ የነበረ ነው። ረጋ ብለን ለምን እንደዛ እንደተሰማን እንጠይቅ፣ እኛ ከቁስ እና ከውድድር በላይ የራሳችን ውበት እንዳለን እናስተውል። ሕይወት ለእያንዳንዳችን የተለየች ናት። ስለዚህ ከዚህ ዓለምም የምናገኘው ነገር እንደዛው የተለያየ ነው። የሌላው ስኬት ሁልጊዜ ለኛ ሊጠቅም ስለሚችልበት ነገር እናስብ። እንድንፎካከራቸው ከሚጋብዙን ሰዎች በብዙ ኬሎሜትር እንራቅ። እንደዛ ስሜት ከሚሰማን ሰዎች ወይም እንዲሰማን ከሚያደርጉን ለጊዜው እንሽሽ ፥ የራሳችን ሕይወት ላይ እናተኩር። ከዛ በተረፈ ግን የምንቀናባቸው ሰዎችን ከኛ መነጠል የማንችል ከሆነ ፥ በተቻለ መጠን በጎ ነገራቸው ላይ ለማተኮር እና ሆን ብለን ለመርዳት እንሞክር። በእነሱ ፊት ላለማስመሰል እንጣር።


የምንቀናባቸው ነገር የምናደንቅላቸው ነገር ስለሆነ እኛ ያ ነገር ቢኖረን እንደምንመኝ እና በዛ ነገራቸው እንደምንቀናባቸው እንንገራቸው። ያ የሚያሳፍር ቢመስለን እንኳ በውስጣችን ያለውን መጥፎ የፉክክር ስሜት ግን ይገለዋል። ስለዚህ ራሳችንን እናድናለን።


በተጨማሪም ቅናት ምን ያህል ፍትሐዊ ስሜት እንዳልሆነ እንገምግመው። ምክንያቱም የምንቀናበትን ሰው ሁሉ ነገሩን አንፈልግም። ያ የምንቀናበትን ጥቂት በጎ ነገር እንጂ። ለምሳሌ የስቲቪ ጆብ (የአፕል ስልክ መስራች) ጓደኛ ሆነን በሱ እንቀናለን እንበል። የምንቀናው በሱ ስኬት ብቻ እንጂ፤ ፈጣሪ ስቲቪ ጆብን ላድርጋችሁ ቢለን ማናችንም እንቢ ነው የምንለው ምክንያቱም ከ40ዎቹ ዕድሜው ጀምሮ በካንሰር በሽታ የተሰቃየውን በ56 ዓመቱ የሞተውን ስቲቪ ጆብን ማናችንም መሆን አንፈልግም፤ የፈለግነው ያ ስኬቱን ብቻ ነው። ሕይወት ግን እንደዚያ አየሰራም። ልጅን ወዶ ንፍጡን ተጠይፈን አይሆንም እንደሚባለው፤ ቅናት እንደዛ ነው። ልጁን ያለንፍጡ መፈለግ። ለዚህ ነው ፍትሐዊ ስሜት እንዳልሆነ እና እኛ የምንቀናበት ሰው የሌለው ውበት በኛ ሕይወት ውስጥ እንዳለ ማየት ያለብን። ይሄ ማለት ግን የኛ ሕይወት ከዛ ሰው የበለጠ ነው ማለት አይደለም። የተለየ እና የራሱ ውበት ያለው ነው ለማለት ነው። ቅናት ግን ይሄን ውበት ያጨልመዋል። ለምሳሌ ሙዚቀኛው ሙሉቀን መለሰ በጥላሁን ገሰሰ ይቀናበታል ይባላል። ያ እውነት ነው እንበል። ሙሉቀን ግን የጥላሁን ገሰሰን ሕይወት ይሰጥኽ ቢባል ፍቃደኛ አይሆንም ምክንያቱም የጥላሁን ሕይወት አንገት መታረድ፣ እግር መቆረጥ፣ በጊዜ መሞትም አለበትና። ለዚህ ነው ቅናት የህሊና ፍትህ መታወር ውጤት የሆነው።



ሌላው የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ፥ ወደ ግጭት ስንገባ እንደግለሰብም ሆነ እንደተቋም እና ሀገር ራሳችንን መጠየቅ ያለብን “የሄ ግጭት ከመመሳሰል ከመጣ ቅናት ወይስ ስትራቴጂክ ፍላጎቴን የሚጠቅም ግጭት ነው?” ብለን ነው። ድፍረት አይሆንብኝ እና ከ90% በላይ የሚሆኑት ግጭቶች የቅናት ውጤቶች ናቸው። በዚህም ከመመሳሰል የመጣ፤ የረጅም ዘመን (long-term) ጥቅማችንን ያላማከለ፣ ስሜት የሚነዳው እና በመጨረሻም ሁሉንም ለከፋ ውጤት የሚዳርግ ነው። ምክንያቱም ቅናት ሌላው የሚያጣ ከሆነ በራሱ ማጣት ሀዘን አይሰማውም። ቅናት ሌላው ሁለት ዓይኑን የሚያጣ ከመሰለው የራሱን አንድ ዓይን አሳልፎ ለመስጠት የሚፈቅድ ነው። ቅናት እንደጥንብ አንሳ የሌሎች መቀርናት የሚስበው ፥ መልካም ጠረናቸው የሚገለው ነው። በሚገርም ሁኔታ እንደ ኮሚኒዝም ያሉ የፖለቲካ ፍልስፍናዎች ሳይቀር በቅናት ሞተርነት የተንቀሳቀሱ ድሃውን ከበርቴ ማድረግ ሳይሆን ከበርቴውን ድሃ በማድረግ የተጠናቀቁ ነበሩ። ጥቂቶች በእነዚህ ሥርዓቶች የተደሰቱት ሃብታም ስለሆኑ ሳይሆን ሌሎችን ከእነሱ እኩል ድሃ ስላደረገላቸው ነበር። የሚያስቡ ሰዎች፣ የራሳቸውን ረጅም ጊዜ ጥቅም በጥልቀት ለመመርመር የሚችሉ እና ስሜታቸውን ለመፈተሽ የሚፈቅዱ ግለሰቦችም ሆነ ልሂቃን ግጭቶች በቅናት እንዳይመሩ ወይም እንዳይቀሰቀሱ ለራሳቸው ስሜት መጠበቂያ ያደርጋሉ። ወደ ግጭት ከመግባታቸው በፊት የዛ ሰው፣ ተቋም ወይም ሀገር ስኬት ለእነሱ ምን ማለት እንደሆነ፣ ያ እንዴት ለእነሱ ጥቅም እንደሚውል ያስባሉ። ውድቀቱ የሚያስደስታቸው ከሆነ ያ ግጭት ከቅናት የተነሳ ሊሆን እንደሚችል መጠርጠር ተገቢ ነው።ምክንያቱም ከመመሳሰል የሚነሱ ግጭቶች ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ አጥፊዎች (distractive) ናቸውና።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page