top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 15 hours ago
  • 3 min read
ree


ምንም ነገር ስትጀምሩ ከማይቀረው እና የግድ ከሚሆነው መጀመር በብዙ የሚጠቅም ሆኖ አይቼዋለሁ። ይሄም ማለት ከመጨረሻው ወደ መጀመሪያ ወይም አሁን ወዳላችሁበት መጥቶ ማሰብ እጅግ ጠቃሚ ነው። ማናችንም ጋር የማይቀር አንድ ክስተት አለ። ሞታችን። አሁን በዚህ ሰዓት ጨምሮ በጥቂት ቀናት እና ዓመታት ውስጥ የምንሞት አለን። መቼ እንደ ሆነ አናውቅም እንጂ ሁላችንም የዚህ ፍጻሜ ደራሽ ነን።



ጥሎ የሚመጣው ጥያቄ “ቀሪው ሕይወታችሁን እንዴት ነው ማሳለፍ የምትፈልጉት? የሚል ነው። ብዙ ምርጫዎች አሉን። በሁለት ምሰሶዎች ግን ልንከፍላቸው እንችላለን። አንዱ ሁሉ እንደሚሆነው ሆኖ መሞት። ሌላኛው ደግሞ የታሰበበት ሕይወት መኖር።


የመጀመሪያው ቀላል ነው። ብዙ የአዕምሮ ሥራ አያስፈልገውም። ማመዛዘን አያሻውም። ብዙኋኑን መከተል ነው። ስሜት እና ሙዳችንን እያደመጡ ብቻ መንጎድ ነው።



ሁለተኛው ግን መቆም ያስፈልጋል። መጠየቅ፣ መመርመር፣ ግራ ቀኙን ማድመጥ እንዲህም ሆኖ መሳሳት እንዳለ ማመን እና ዘወትር አስተሳሰባችንን እየመዘኑ ለመጓዝ መወሰን ይጠይቃል።



ትላንት “ኦርዌል 2+2=5” የተባለ ግሩም ፊልም እያየው ነበር። ከግማሽ ክፍለ ዘመን በፊት የኖረ ግለሰብ የዛሬን የሰው ሁኔታ በደንብ ገልጾ መጻፉ አስደናቂ ነበር። ግን ተንብዮ እንዳይመስላችሁ። ከሱ በፊት እና በሱ ዘመን እየሆነ ያለውን በማየት እና በማስተዋል ነበር የጻፈው። እንደ ዘወትር የመጣልኝ ሀሳብ “የሰው ልጅ መቼም አይቀየርም” የሚል ነበር። ልክ እንዳልሆንኩኝ የገባኝ ዛሬ ያለንበት ዓለም ከመቶ እና ከዛ በላይ በፊት ከነበረው ዓለም በነጻነትም ሆነ በመብት መከበር እጅግ የተሻለ እንደሆነ ካስተዋልኩኝ በኋላ ነበር። የኦርዌልን ፊልም ሳየው ተስፋ ነበር ያስቆረጠኝ። ይሄ ዓለም በማፍያ ፖለቲከኞች እና በስግብግብ ሀብታሞች ብቻ የሚበዘበዝ እና 99 ፐርሰንቱ ማህበረሰብ ተጠቂ እንደሆነ ብቻ እንዲሁም ጎስቋል መሆኑ የማያቆም እና መቆሚያ የሌለው አድርጌ ነበር የሳልኩት። ያ ግን ፈጽሞ ልክ አይደለም።



አዎ ጨለማ ዙሪያችንን ከቦ ሊሆን ይችላል። መጥፎ ሰዎች ሲያብቡ እና እንዳበቡም ሲሞቱ እያየን ይሆናል። ክፉ እና አስመሳይ ሰዎች በደጋጎች ላይ ሲነግሱ ተመልክተን ይሆናል። እንደ ኢዮብ በንጽህናቸው የሚቀጡ እና ጉስቁልናቸው ማለቂያ የሌለውን ግለሰቦች እና ማህበረሰቦች እያየን ይሆናል።



ይሄ ሁኔታ ከዚህ በፊትም የነበረ እና ያለ እንዲሁም የሚኖር ነው። ግን የዚህ ዓለም ጨለማ ድሮ ከነበረው በብዙ እጥፍ ቀንሷል። ይሄ ዓለም ከሺዎች ዓመት በፊት የፈሪሳውያንን ሕግ አላከበርክም ብላ አንድ ፍጹም እና ንጹሁ የሆነን ሰው የሰቀለች ነበረች። የእርሱ ተከታይ ናችሁ ብላ ሌሎችን ደግሞ ቆዳ እስከመግፈፍ የደረሰች ነበረች። ይሄ ዓለም ለጆሮ ዘግናኝ የሆኑ ግፎችን ያስተናገደች ናት። አሁን ያ በጥቂት ቦታዎች እናይ ይሆናል እንጂ በብዙ ቀንሷል። ለብዙዎቻችን ዛሬ ከመቶ ዓመት በፊት ከነበረው በብዙ የተሻለ ነው።



ለዚህም ዋነኛው የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዓይነት ግለሰቦች ነበሩ። “ጨለማን ከማውገዝ ሻማ ማብራት የተሻለ ነው” ያሉ ሰዎች ናቸው ይሄን ዓለም ወደ ተሻለ መንገድ የመሩት። እዚህ ያደረሱት። አንዲት ቅድስት በዘመኗ ክፋት በዝቶ ሰዎች ተስፋ ሊያስቆርጧት ሲመጡ፤ ያለችው “የኔ ተልዕኮ ክፋትን ማሸነፍ አይደለም። የእኔ ድርሻ ክፋትን መዋጋት ነው” ነበር።



ኢትዮጵያውያን እኔም የምጋብዛቹ ይሄን ነው። በዚህ ዘመን እንደኔው ብዙ ግራ ገብቷቹ ሊሆን ይችላል። አዋቂው ሕጻን የሆነበት ዘመን ላይ እንዳላችሁ ሊሰማችሁ ይችላል። መላ ቅጡ የጠፋበት እና አዋቂነት ያሽቆለቆለበት ዘመን ላይ ልንሆን እንችላለን። ግድ የላችሁም። ይሄን ጨለማ በማውገዝ ጊዜ አታጥፉ። እናንተ ጋር ያለው መልካምነት እና በጎ መንፈስ ግን እንዳይጨልም አደራ። መልካም እና ደግ ከመሆን አትገደቡ። ምንም ቢጨልም የእናንተ ሻማ የሚገፈው ጨለማ እንዳለ እመኑ።


ዮሐንስ አፈወርቅ ብቻውን የቆመ ቢመስለውም የእርሱን የእምነት ሻማ ግን ለማጥፋት አልፈቀደም ነበር። ኢትዮጵያኖች በዚህ የተርዕዮ ዘመን፣ ሰዎች ዋጋቸውን ከሰዎች በሚገኝ ሙገሳ እና አድናቆት ለማግኘት በሚሮጡበት ዘመን፣ የመልካምነትን ደረጃ (ስታንዳርድ) ዝቅ ላለማድረግ እንጠንቀቅ። በጥቃቅን ነገሮች ሳይቀር ክብርን መጠበቅ፣ የምግባራችንን ደረጃ ከፍ ማድረግ፣ “የእኔ የስነምግባር ማማ ይሄ ነው" ማለት አናቁም። ሁሉም በሰከሩበት ሰዓት ላይ ብንኖር እንኳ የባህሪ ማማ ላይ ለመቆም እንቁረጥ።


ጨለማን በማውገዝ ያሸነፈ የትም የለም። አይኖርምም። በብርሃን፣ በሻማቸው ያሳወሩት ግን አሉ። እኛ ጨለማን በብርሃኑ ብዛት ካሳወረው ነን። ምንም ከባድ ቢሆን ፥ ለማሸነፍ ብቻ አይደለም እዚህ ያለነው። ምክንያቱም ማሸነፍ ብንፈልግ እንኳን ሞት አንድ ቀን ይረታናል። ማንም በመሸነፋችን አይታዘበንም። ሳንዋጋ እጅ በመስጠታችን እንጂ። በማይቀረው ሞታችን መኃል የሆኑ ሰዎችን ሕይወት፣ የሆኑ ግለሰቦችን ሕመም ፈውሰን፣ ጨለማ የነበረውን ሕይወታቸውን አብረተን ካለፍን ፥ የዛኔ ሞት የማይረታው ትንሣኤ በሌሎች ሕይወት ውስጥ ጥለን እንሄዳለን። ሻማ፣ አዎ ሻማ እናብራ በዚህ ጨለማ መኃል።

 
 
 
ree


ባብዛኛው የአሜሪካ ክፍል ከፍተኛ ብርድ እና በረዶ የሚያስተናግድበት ወቅት ነው። ማህበረሰቡም ወቅቱን ለመምሰል ይጥራል። ከአለባበሱ እስከ የአኗኗር ዘዬው። በተለይ በመካከለኛው ምዕራባዊ ክፍል ያሉት ግዛቶች ከፍተኛ በረዶ እየጣለባቸው ነው። መንገዱ ጭር ያለ፣ ሰው በጊዜ ወደ ቤቱ የሚገባበት እና የሚሰበሰብበት ወቅት ነው። ከቀኑ አራት ሰዓት (ማለትም በኢትዮጵያ አስር ሰዓት) ጀምሮ ቀኑ መጨለም ይጀምራል። ትላንት በረዶ ከጣለ በኋላ የዚህ ሀገር ተወላጅ የሆነችውን የሥራ ባልደረባዬ ከውጪ ስትገባ አይቻት፣ “በዚህ በረዶ ውጪ ላይ እየተራመድሽ (walk) ነበር? የሚገርመው ግን አንቺ ምንም የመሰለሽ አይመስልም?” ስላት፤ “እኔ እንኳ መጥፎ አለባበስ እንጂ መጥፎ የዓየር ፀባይ የለም ቡዬ ነው ማመን የምፈልገው!” በማለት በዚህ አካባቢ የሚታወቀውን አባባል ተናገረች። “እኔ ግን መጥፎ የዓየር ፀባይ አለ ብዬ አምናለሁ፣ እሱንም አሁን እያየውት ነው” ብያት ተሳስቀን ተለያየን።



ይሄ አባባል ግን ብዙ ልንማርበት እንችላለን። ስንኖር ከኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ፤ ግን እነዚህን ሁኔታዎች የምናልፍባቸው ጥበቦችም እኛ ሰዎች አሉን። መሠረታዊ ሕይወታችን ሳይጓደል እና ሳይስተጓገል አስቸጋሪ ቀናትን ማለፍ እንችላለን። የመጀመሪያው ጥበብ የሚመስለኝ መቀየር የምንችለውን እና መቀየር የማንችለውን ነገር በፍጥነት ማወቅ ነው። ከዛ ሁለተኛ ጥበብ አለ። የሚከተል። አሜሪካኖች አንድ ድንቅ ጸሎት አላቸው ፥ እነዚህን ሁለቱንም ጥበቦች በአንድ ላይ ያዘለ።


“ጌታ ሆይ መቀየር የምችለውን ነገር ታግዬ እንድቀይር ጀግንነትን ስጠኝ ፥ መቀየር የማልችለውን ነገር ደግሞ እንድቀበለው መረጋጋትን አድለኝ። ሁለቱን መለየት የሚያስችልን (መቀየር የሚቻል እና መቀየር የማይቻልን) ጥበብን ለግሰኝ።” የሚል።



የሰው ልጅ ብዙ ዕድሜውን የሚጨርሰው መቀየር የማይችለውን ነገር ለመቀበል ተቸግሮ ሲታገለው፤ መቀየር የሚችለውን ነገር ደግሞ ለመታገል በስንፍና እና በፍርሃት ጊዜ ሲፈጅ ነው። በርግጥ በጣም ከባዱ ነገር የትኛው ነገር ይቀየራል ፥ የትኛው አይቀየርም የሚለውን ማወቁም ላይ ነው። ምክንያቱም ብዙ አይቻልም፣ ይሄ የሰው ልጅ ሊያደርገው ፈጽሞ አይሆንም የተባሉ ነገሮች ተደርገው እና ተለውጠው ታይቷል። ለዚህ ነው ያንን ለመለየት አሜሪካኖች ጥበብን የጠየቁት። ኔልሰን ማንዴላ “it is impossible until it is possible ፥ የማይቻል ነበር እስከሚቻል ድረስ” የሚል አባባል አለው።



ብዙ አንባገነነ መንግስታት በሕዝባቸው ላይ መጫን የሚፈልጉት ስነልቦና እነሱን መቀየር የማይቻል መሆኑን ማሳየት ነው። ለዚህ ደግሞ ራሳቸውን ሥዩመ እግዚአብሔር ከማለት እስከ ፈጣሪ ነን ወደሚል ፕሮፖጋንዳ ይነዛሉ። ብዙሁን ሕዝብም ለብዙ ዘመን የስነልቦና ሽባ ያደርጉታል። አንድ ቀን ያ ደፋር ልጅ “ንጉሱ ራቆቱን ነው” እስከሚል እና የሕዝቡን ዓይነ ጥላ እስከሚገልጥ ድረስ።



በተመሳሳይ የዛሬ ሶስት እና አራት መቶ ዓመታት በዓየር ላይ መብረር ለአዋፋት እና ለመላዕክት ብቻ የተተው ጉዳይ ነበር። የራይት ልጆች ተነስተው ያን እስከሚለውጡት ድረስ። የሰው ልጅ ዛሬ ላይ ያሉት የቴክኖሎጂ ውጤቶች አብዛኞቹ ከመቶ እና ከሀምሳ ዓመታት በፊት በሕልም እንኳ የማይታሰቡ ጉዳዮች ነበሩ። ጥበቡ ያላቸው ሰዎች ግን የማይቻል የመሰለውን ነገር እንደሚቻል አሳዩን። ለዚህ ነው በአሁን ጊዜ፣ አሁን ባለን አቅም መለወጥ የምንችለው ነገሮች ምን እንደሆኑ ከስንፍና እና ከፍርሃት ተላቀን ማሰብ ያለብን።



ያሄ ማለት ግን አሁን ላይ የምንቀበላቸው ውስንነቶች የሉም እያልኩኝ አይደለም። ምንም እንኳ ከመቶ ዓመት በኋላ ሰው እስከ ሁለት መቶ ዓመት መኖር የሚያስችለው የሕክምና ጥበብ ሊመጣ ቢችልም፣ ዛሬ ላይ ግን ሞት ለብዙዎቻችን ከሰማንያ እና ዘጠና ላይ እንደሚሆን መቀበል ያስፈልጋል። በተጨማሪም ትላንትን መመለስ አንችልም። ትላንት ዛሬ ያለን እውቀት ቢኖረን የማንሰራቸው ብዙ ጉዳዮች፣ ጥፋቶች ነበሩ። ስለዚህ ትላንትን መቀበል ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ የተረጋጋ አዕምሮ ያስፈልጋል። የተረጋጋ አዕምሮ ከትላንቱ ጋር ይታረቃል። ትላንቱን ይማርበታል፣ ነገም በሆነ ደረጃ ተገማች እንዳልሆነ ይረዳል። ለምሳሌ ነገ ዋጋው ይወርዳል ብሎ ዛሬ የሸጠው ንብረት ፥ ነገ የበለጠ ዋጋው ከፍ ሊል ይችላል። ስለዚህ ቢረጋጋ እና ቢጠብቅ ሊያተርፍ በሚችለው ሳይሆን የተረጋጋ አዕምሮ የሚጨነቀው፤ ትላንት ለመሸጥ ሲያስብ ለምን እንዳሰበ፣ ለምን እንደዛ ዓይነት ውሳኔ እንደወሰነ፣ ለውሳኔ የተጠቀማቸውን ማስረጃ እና መረጃ እንጂ የሚመረምረው ፥ ትላንትን ዛሬ ላይ ባገኘው እውቀት ቆሞ አይገመግምም። የተረጋጋ አዕምሮ ለወቀሳ አይደለም የሚቸኩለው። ለመማር እና ከተቻለ ዛሬን እና ነገን የተሻለ ለማድረግ ነው።



የተረጋጋ አዕምሮ ጀግንነትን ለማግኘት ይጥራል። ምክንያቱም መለወጥ የሚችሉ ነገሮችን ለመታገል ጀግና መሆን ያሻል። ብዙ ሰዎች ስኬታችንን እስከሚያዩ ድረስ ከጎናችን ለመቆም ይቸገራሉ። ሲሳካልን ነው ሊተባበሩን የሚፈልጉት። ይሄ የሰው ባህሪ ነው። የእኔም የእናንተም ባህሪ ነው። ስኬት ወዳጇ ብዙ ነው። የከሰረን እና የተረሳን ሰው “እሱኮ ምርጥ ወዳጄ ነው” ብሎ በኩራት የሚገልጽ የለም። ስኬታማን ሰው ግን ሁሉም ወዳጁ ለማድረግ ይጥራል። ሁሉም ከእርሱ ጋር ፎቶ ለመነሳት እና የእርሱ ወዳጅ ለመሆን ይጥራል። ይሄ በየትኛውም ዘመን ያለ እና የሚቀጥል ነው። ቢያሳዝንም ጀግና ሰው ግን ይሄን ይቀበላል። ስለዚህ ለመለወጥ የሚታገለውን ነገር ለመቀየር ለጥቂት ጊዜ የብቻ ትግል እንደሚሆን ያውቀዋል። ኖሕ መርከቡን ገንብቶ እስከሚጨርስ ድረስ በፀሐይ እና ዝናብ በሌለበት መርከብ የሚገነባ ሞኝ ነበር። ዝናቡ ሲመጣ እና በርግጥም የመጣው ጎርፍ የተለየ እንደሆነ ሲታይ ብቻ ነው ኖሕ ጠቢበኛ የተባለው። ለብዙ ዘመን ግን ሞኝ ተብሎ ለመቆጠር መፍቀድ ነበረበት። ለጥቂት ጊዜ ብቻችንን ለመቆም ካልፈቀድን መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮችን ሳንቀይር ሕይወታችን ያልቃል።



ገጣሚው ሮበርት ፍሮስት እንዳለው በመጨረሻ የሚቆጨን ከሞከርነው ነገር ይልቅ ያልሞከርነው ነው። ብዙ ሰዎች መለያየት ካለባቸው ሰው ጋር በፍርሃት ታስረው አንድ ሕይወታቸውን ያባክናሉ። ማቋረጥ ያለባቸውን ሥራ በፍርሃት አቅፈው ይዘው የፈጠራ አቅማቸውን ያባክናሉ። ብከስርስ በሚል ስጋት አቅማቸውን ይቀብሩታል። ከዛም መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይቀጥላሉ። እያማረሩ ሕይወታቸውን ይጨርሱታል።



በበረዶ ላይ ከወዳጄ ጋር እየተራመድን ነበር። “በዚህ ብርድ ይሄን ሁሉ መንገድ መጓዝ ጥቅሙ ምንድነው?” አልኩት። “ጽናተ ቅስም ታዳብራለህ” አለኝ። ትላንት መጥፎ ያልኩት ዓየር ፀባይ ዛሬ ብሶበት ነበር። ግን ከጥሩ ልብስ ጋር ጭራሽ ለጥቅም አዋልኩት። ስቤን እያቀለጥኩኝ ቅስሜን ደግሞ አጸናውበት።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Nov 30
  • 3 min read
ree

አንዳንድ ጊዜ እውነተኛ ትምህርት በምቾት ውስጥ ካለፉ ወይም ከስቃይ ውስጥ ከወጡ ሰዎች ነው መማር የምንችለው የሚለውን እርግጠኛ መሆን እቸገራለሁ። ምክንያቱም ብዙ በችግር ውስጥ የሚያልፉ ሰዎች አያለሁ፤ ምቾት ግን የሚገላቸው። ቢሆንም "ሁላችንም ይሄን እንዴት አልፈዋለሁ?" ብለን የምንጨነቀው ችግር ሲመጣ ነው። የዛሬ የሰንበት ጹሁፌ በፍጹም መከራ ውስጥ ያለፈውን ቪክተር ፍራንክል ምክሮች ላይ ያተኮረ ነው። ይሄ ድንቅ ሰው ከመጀመሪያው ግልጽ የሚያደርገው ችግር አንጻራዊ እንደሆነ ነው። በአሜሪካ በሶፋው ላይ ቁጭ ብሎ ያለ ሰው እና በሱዳን የእርስ በርስ ጦርነት መካከል ያለ ሰው እኩል ሊቸገሩ ይችላሉ። ምክንያቱም የመከራ ከባዱ ክፍል ብዙ ጊዜ አካላዊ ሳይሆን ስነ ልቦናዊ ስቃዩ ነው። “መከራ እንደ ጋዝ ነው” ይላል። “አንድ ጠብታ ጋዝ በበርሜል ውስጥ ቢከተትም ሆነ በአንድ ትልቅ ክፍል ውስጥ የሚቆጣጠረው ክፍት ቦታ ተመሳሳይ ነው።” ያ ጠብታ ጋዝ ክፍሉን ሁሉ መቆጣጠር ይችላል። በተመሳሳይ በበርሜል ውስጥም ቢገባ በርሜሉን ሁሉ ይቆጣጠራል። መከራም ትልቅነቱ እና ትንሽነቱ አይደለም። የዛን ሰው አዕምሮ ትንሽም ይሁን ትልቅ በምልአት ነው የሚቆጣጠረው።



ለዚህ ነው ፍራንክል በናዚ ካምፖች ውስጥ ስላለው እና እርሱ ራሱ ስላለፈበት ሕይወት ሲናገር “ማንም አካሉ ጠንካራ ስለነበረ ያን መከራ አላለፈውም። ይልቁንስ ያን መከራ ያለፉት ሰዎች የመኖር ምክንያት (meaning) የነበራቸው ናቸው” ይላል። “ለምን የሚለውን የመለሰ ሰው የትኛውንም እንዴት ያልፈዋል” ይላል። የተረፉ ሰዎች ከዛ ካምፕ የሚወጡበት ምክንያት ነበራቸው። ሕይወታቸው አሁንም ያላለቀ እና የሚያሳኩት ትርጉም እንዳላት ያምናሉ። ከዛም የተነሳ መከራን እንደ ቅጣት ሳይሆን እንደ ፈተና ብቻ ነው የሚያዩት። ፍራንክል ሳይቀር ከኦሽዊትዝ ካምፕ ወጥቶ ይሄን ስቃዩን ሌክቸር ሲያደርግ እና የሕይወትን ትርጉም ሲያስተምር ራሱን ይስለው ነበር።



ይሄን ያለፉ ሰዎች ባብዛኛው “ይሄ ግን በእኔ ላይ ለምን ሆነ?” ሲሉ አይጠይቁም። “ለዚህ መከራ የሚስማማ ስብዕና ምንድነው? ብለው ነው የሚጠይቁት።



ፋራንክል “ብዙ ጊዜ በሕይወት ምርጫ ላይኖረን ይችላል። መቼም የማንነጠቀው ነጻነት ግን አለን? ይላል። ያም አመለካከታችን ላይ ያለን ነጻነት ነው። በሆነ ሁኔታ ውስጥ ስንሆን በዛ ሰዓት ሊኖረን የሚችለውን አመለካከት የመምረጥ ነጻነት ግን አለን።



ተስፋ ከመቁረጥ አዕምሮአችንን መመለስ፣ የውስጥ ሰላምን ለመጠበቅ ራሳችንን ከክፋት ማራቅ፣ እጅ ላለመስጠት መወሰን፣ በሌሎች ላይ ላለመፍረድ መጠንቀቅ እና ክብርን በትንንሽ ነገሮች ሳይቀር መጠበቅ።



“በሚገርም ሁኔታ በናዚ ካምፖች ውስጥ የሰዎችን መልካምነት ብቻ ተመልክቶ ማን ሊተርፍ እንደሚችል መገመት ይቻል ነበር” ላል ፍራንክል። ቁራሽ ዳቦዎቻቸውን ለሌሎች ያጋሩ፣ በራብ ወቅት ሳይቀር ክብራቸውን የጠበቁ፣ ሌሎች እስረኞችን ያልዱ ሰዎች የመትረፍ ዕድላቸው ሰፍቶ እና ከእነዛ ካምፖች በሕይወት ቆይተው ሲወጡ አይቻለሁ። ይላል።



እዚህ ጋር ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በጻፈው መጽሐፍ ላይ ያለ የወሎ ረሀብ ታሪክ ትዝ ይለኛል። የአሜሪካው ሴናተር ኬኔዲ ረሀብተኞቹን ጎብኝቶ ተመልሶ ሆቴሉ መተኛት ያቅተዋል። በተመለከተው የተራቡ ሰዎች ብቻ ግን አይደለም። እነዛ የተራቡ ሰዎች ሰልፍ ጠብቀው፣ ዳቦ አየን ብለው ሳይጋፉ እና ሳይደባደቡ የተሰጣቸውን አመስግነው ተቀብለው መሄዳቸው እና በዛ ሁኔታ ውስጥ እንኳ ክብራቸውን መጠበቃቸው ነበር ያስደነቀው።



ብዙዎቻችን እንደዚህ ሥርዓት መያዝ እና አለመስገብገብ ሕይወትን ለማስቀጠል ትርጉም ያለው ላይመስለን ይችላል። ይሄ ማንነት ግን በመከራ ውስጥ ቅስምን ከመሰበር ይጠብቀዋል። ቅስም ከአጥንት ውስጥ ያለ አጥንት ነው። የተሰበረ ቅስም ያለው ሰው ጠንካራ አጥንት ቢኖረው እንኳ ቆሞ አይሄድም። የቅስም ጽናቱ ደግሞ ሞራል ነው።




ፋራንክል “አዕምሮ እውነትን መቀበል ሲክድ ይሰበራል” ይላል። የአዕምሮ ጥንካሬ አሁን ያለውን እውነት በመቀበል የሚመጣ ነው። ጽናት መሸሽ ለማንችለው መከራ ትርጉም በመስጠት የሚገኝ ነው። መቀበል ማለት እጅ መስጠት አይደለም። አለመካድ እንጂ። የሚታየውን ነገር ኮስሞቲክስ እና ሊፒስቲክ አለመቀባት እንጂ።



ጽናተ ቅስም ያላቸው ሰዎች ፍርሃትን ካልገሩት ፥ ፍርሃትን እንዲሁ ከፈቀዱለት አሳስሮ እንደሚያስቀምጥ ያውቁታል። ተስፋቸው ህልም አይደለም። ማለትም የዛሬ ሦስት ወር ወይም ከዓመት በኋላ ይለወጣል ብለው አይደለም የሚያምኑት። ይሄ እብደት፣ ይሄ ክፋት፣ ይሄ መከራ ግን እንደሚያልፍ ያምናሉ።



የመከራው ፍጻሜ በግልጽ አልታየው ያለው ጻዲቁ ኢዮብ በወዳጆቹ ወቀሳ ፊት እና በተሸከመው የስቃይ ሰውነት መካከል ቆሞ እንዲህ ነበር ያለው “እኔን ግን የሚቤዠኝ ሕያው እንደ ሆነ፥ በመጨረሻም ዘመን በምድር ላይ እንዲቆም፥ ይህ ቁርበቴም ከጠፋ በኋላ፥ በዚያን ጊዜ ከሥጋዬ ተለይቼ እግዚአብሔርን እንዳይ አውቃለሁ።” ኢዮ 19፥25። ቻርሊ መንገር እንዲህ ይላል “የሚደርስበት የፕሬዠር ደረጃ እንጂ የማይሰበር ሰው የለም።” ምን ያህል ግፊት ይፈልጋል ነው እንጂ ሰው ሁሉ ይሰበራል። ለዚህ ነው ብርቱ ኢዮብ ሳይቀር “ጕልበቴ የድንጋይ ጕልበት ነውን? ሥጋዬስ እንደ ናስ ነውን?” ያለው። ኢዮ 6፥12። በመከራቸው ወቅት “ከዚህ መከራ አንድ ቀን ይታለፋል። በዚህ መከራ ውስጥ የሕይወት ትርጉም አገኛለሁ።” ያሉ ሰዎች የገጠማቸውን የመሻገር አቅም ያገኛሉ።



መከራን ማለፍ የሚችሉ ሰዎች በመከራቸው ሰዓት ሳይቀር ትንንሽ ደስታዎችን ይፈልጋሉ። በሚያዩት የተፈጥሮ ውበት ይደሰታሉ። በዛ መከራ መካከል ከከዷቸው እና ከተዎቸው ሰዎች ላይ ዓይናቸውን አንስተው ባልጠበቁት ሰዓት የደረሱላቸውን ሰዎች ደግነት እያዩ ያመሰግናሉ። በዛ መከራ ውስጥ ሳይቀር በቀልዶች እና በራሳቸው ባህሪ ይስቃሉ። ይሄ ሕይወት ከዚ ውጪ መሆን አይችልም። በዚህ መካከል ማለፍ ነው ስብዕና።




ሕይወት ትርጉም የሚኖራት በመከራ ውስጥ ማለፍ ለፈቀዱ ነው። በዚህ ውስጥ እንኳ እያለፉ ራስ ወዳድነት ሳያሸንፋቸው በመስጠት ሲያምኑ፣ ለእነሱ በቂ ያልነበረውን ለመጋራት ሲፈቅዱ፣ ነውር ሳይነካቸው ወደ መታረጃው ቦታ ሲገቡ ግን ደግሞ ትንሣኤ እንዳለ ፥ ክፋት በመጨረሻ እንደሚሸነፍ ሲያምኑ ፥ የዛኔ የእነርሱ ታሪክ ለማስተማሪያነት እንደሚውል ሲያውቁ ፥ ቅስማቸው እንደ ጸና ፥ አንገታቸው እንደ ቀና ይሻገራሉ።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page