top of page
ree


እ.ኤ.አ. በጁላይ 2021 የተጻፈ እና በድጋሚ የተለጠፈ



በመንፈሳዊ ሕይወት ያደኩት በሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ነው። በዕድሜም በብዙ ንባብም መጎልመስ ስጀምር፣ በጉዙዎቼ ከብዙ አገራት ሰዎች ጋር ጥልቅ ውይይቶችን ሳደረግ መንፈሳዊ ብዬ ከተቀበልኩት ነገር ብዙ ለውጬያለው። አንዳንድ ከራሴ ጋር ያደረኩዋቸው ውይይቶች ለራሴ እስከሚያስፈሩኝ ድረስ በሀሳብ ተወስጄባቸዋለው። ካርል ዩንግ እና የሱን ፍልስፍና በስፋት ያስፋፋቱ እንደ አላን ዋትዝ እና ያን ፒያት እንደነገሩን በልጅነታችን ያለንን ስሪት በጣም እጅግ በትንሹ ብቻ ነው መለወጥ የምንችለው። አድካሚ “የኢንቴሌክቿል” ጉዞ ከሄድን መድረስ የምንችለው ራሳችንን ማወቅ ላይ ብቻ ይሆናል። ይሄ በልጅነት እንዴት እንደተሰራን ጥቃቅን ነገሮችን ሳይቀር በማስታወስ የሚደረግ አሰጨናቂ ጉዞ ነው።



ካርል ዩንግ ራሱን ለማወቅ በወንዝ ዳር እንደ ሕጻናት ጭቃ እያቦካ በመጫወት ሕጻን እያለ የተሰሙትን ስሜቶች ከ“unconscious” አዕምሮ ፈልቅቆ ለመረዳት በመጣር የሚሰማውን ስሜት ይመዘግብ ነበር።



አንድ ነገር ዘወትር አሰላስላለው። ቅዱስ ገብርኤል በእኔ ባህሪ ላይ ያለው ተጽዕኖ። በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ገብርኤል የጽናት ምሳሌ ነው። “ንቁም በበህላዌነ ፥ ባለንበት ጸንተን እንቁም” ብሎ ዓለም በአምላክ ቃል ከጸናች በኋላ ከፈጣሪ ቀጥሎ ጽናትን ያወጀ መላክ ነው። ከእሱ እና ከሌሎች ቅዱሳን በኃይሉ የገዘፈው የሳጥናኤል ግርማ ሳይረታው አምላኩን እስከሚያይ የጸና ፥ ያጸና መላዕክ ነው። ያዳናቸው ቅዱሳን ሁሉ የሱ ባህሪ አለባቸው። ፊት ለፊታቸው የገጠማቸው ጠላት ታይቶ የማይታወቅ ግዙፍ፣ ብዙዎች የተርበደበዱበት እነሱ ግን የመዳን ተስፋ እንኳ ርቋቸው ለእምነታቸው መከራውን ለመቀበል የተዘጋጁ ሰዎችን ነው በቅዱስ ገብርኤል አመታዊ በዓላት የሚዘከሩት።



በሌላ አነጋገር ከልጅነቴ ጀምሮ እምነት እና አሸናፊነት ተለያይቶ ነው ስሰበክ የነበረው። ለሆነ ነገር ዋጋ የምትከፍለው እንደምታሸነፍ ስለምታምን ሳይሆን ያ ነገር “አንተነትህን” ስለሚወስን ነው። ሠልስቱ ደቂቅም ሆኑ ሕጻን ቂርቆስ እንድናለን ብለው ወደ እሳት እና የሚንተከተክ ውሃ ውስጥ አልገቡም። ለእምነታችን መሞት ነው አሸናፊነት ፥ ብንድንም ፥ ባንድንም ለእኛ ግዳችን አይደለም። ለእኛ ዋናው ነገር “እምነታችን” ነው ያሉ ቅዱሳን ናቸው። ከዓመት ዓመት ያለመስልቸት የምንሰበከው እነዚህ ታሪኮችን ነው። በጽናት ስለቆመው መላዕክ እና ባንድንም ለማናምንበት ነገር አንበረከክም ስላሉ ቅዱሳን። እኔ ያደኩበት ቤተክርስቲያን መምህሩ (ፓስተሩ) አፈር ለአፈር እያንከባለለን አላደግንም። ስለመቆም እና ጥብአት እያስተማረን እንጂ። ውጤቱን አስልቼ (መዝኜ) አይደለም ለመሠረታዊ እሴቶቼ የምቆመው። እምነቴ ውጤቱን ያመጣው ይሆናል እንጂ ውጤቱ እምነቴን አይሸርፈውም። በኦሮቶዶክስ በተለይ በኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን ምሰሶ የሚባለው አትናቲዎስ የሚታወቀው “ዓለሙ ሁሉ ጠልቶሃል” ብሎ ሰይጣን ሲነግርው ፥ “እኔ ቀድሜ ዓለሙን ሁሉ ጠልቼዋለው” ብሎ በተናገረው ንግግሩ ነው። ይሄ እምነትን በውጤት አለመመዘን ቤተክርስቲያኒቷን በተረዱ ሰዎች ላይ የሚታይ ባህሪ ነው።



ወደ ንባብ ዓለም ስገባ የአምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ “I stand alone” መጽሐፍ እጅግ ይማርከኝ ነበር። አንድም የኃይለሥላሴ ባለስልጣን ደፍሮ ንጉሱ እና ሥርዓታቸው የገቡበትን ንቅዘት ለመናገር ባልፈቀዱ ሰዓት በእንጦጦ ቤተ-ክርስቲያን ያደገው ብርሃኑ ድንቄ ግን አላስቻለውም። ኋላም ጥገኝነት መራራ በሆነበት የነጭ አሜሪካ ተሰዶ ስለእምነቱ ፍጹሙ ስቃይን የተቀበለ ሰው ነው። ደርግም ሲመጣ አሁንም የእምነት ጉዳይ ነውና ደርግን አወገዘ። ኋላ ይሄ እምነቱ በጤናው ጨምሮ በሁሉም ነገር ዋጋ አስከፈለው። እሱ ግን ለእምነቱ የከፈለው ዋጋ ሳይጸጽተው አለፈ። ለእኛም “ብቻዬን ቆምኩኝ” የሚለውን መጽሐፉን አበረከተልን።



የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሲዖል እንደሚገቡ የተነገረላቸው ቅዱሳን ያላት እና "ሲዖል እንኳ ብንገባ የምናመልከው ገነት ወይም ሲዖል ያስገባናል ብለን አይደለም” ያሉ ቅዱሳን የነበራት ናት። ይሄ ነው ትምህርቷ። በዚህ ትምህርት የሚፈጠር የሰው ስነ-ልቦናን አስቡ።



ምንድነው ግቡ ሲዖል እና ገነት ካልሆነ ታዲያ ብሎ ለሚጠይቅ ፥ “ፍቅር” ትላለች ቤተክርስቲያን። መውደድ! በምታገኘው ነገር ሳይሆን በእምነትህ ፥ ለእምነትህ ባለህ ፍቅር ተደሰት። አንተነትህ ሸቀጥ አይደለም። ጸጋዬ ገብረመድህን “ይህችን ነው ኢትዮጵያ የሚላት።”



የቅዱስ ገብርኤል በዓል ተራ ንግስ እና ቅዱስ መላዕክ ማክበር ብቻ የሚመስለው ወይም ለቁስ ስኬት ስዕለት ለማስገባት ሰዎች የሚሯሯጡበት የሚመስለው ይኖራል። ይሄን የሚያደርጉም በዓሉን እና መላዕኩን እየሰደቡ ያሉ ይመስለኛል። በዚህ የቤተክርስቲያን ጥልቅ ፍልስፍና ላይ ቆሞ የሚንጎራደደው መድረክ መሪ የውጤት ተኮር ስዕለቶችን ዝርዝር ሲተርክ ይውላል።



እውነት ለመናገር በዚህ ዘመን ያለችው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን እና የብልጽግና የፕሮቴስታንት ቸርቾች ጋር ያለው የፍልስፍና ልዩነት ግራ ይገባኛል። የብልጽግና ፕሮቴስታንት የኢንዱስትሪያል አውሮፓ ፍጥረት ነው። ፍልፍስናው ሁሉ ኢንዱስትሪ ነው። የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ግን የቁሱ ዓለም ተቃራኒ ናት። ቄሳርን የለየች ነበረች። ዛሬ ያ የለም። እየተፈጠረ ያለው ትውልድም በሽንፈት የሚርድ ፥ በአሸናፊነት ያለ ልክ የሚወጠር ነው። ጦር ሜዳ የሚወስደው እምነቱ እና ክብሩ ሳይሆን ማሸነፍ መቻሉን እርግጠኛ ሲሆን ነው። ምንአልባት የብልጽግና ሃይማኖት ስኬት እየታየ ይሆናል።


አድዋ ላይ የጊዮርጊስን ታቦት ይዞ የዘመተው ሕዝብ እዛ ድረስ የወሰደው ሰውነት ስለሚባል ክብር ነው። ሰማዕት ጴጥሮስ በመድፍ ፊት ሃሳቡን ያለወጠው እና ጣልያንን እያወገዘ የጥይት አረር የተቀበለው ውጤት ተኮር ሃይማኖት ስላነበረው ነው። እንዴት የሰው ልጅ ማንነት በምንአልባት በሚወሰን የወደፊት ውጤት ይሰፈራል። ቅዱስ ገብርኤል የገባቸው አባቶቻችን ኢትዮጵያን የወደዷት ከዚህ እምነት በመነሳት ነበር። ኢትዮጵያ “ባያድነን እንኳ (ባይደላኝ፣ ብራብብሽ፣ ብሰቃይብሽ፣ ወዝ እና አቅም ባይኖርሽ) ፥ ለጠላቶቻችችን ውርደት አንገዛም” የሚለው እምነት ሃውልት ነበረች። ይሄን እምነት ነው አባቶቻችን ኢትዮጵያ የሚሉት።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Dec 21
  • 3 min read
ree


ምንም ነገር ስትጀምሩ ከማይቀረው እና የግድ ከሚሆነው መጀመር በብዙ የሚጠቅም ሆኖ አይቼዋለሁ። ይሄም ማለት ከመጨረሻው ወደ መጀመሪያ ወይም አሁን ወዳላችሁበት መጥቶ ማሰብ እጅግ ጠቃሚ ነው። ማናችንም ጋር የማይቀር አንድ ክስተት አለ። ሞታችን። አሁን በዚህ ሰዓት ጨምሮ በጥቂት ቀናት እና ዓመታት ውስጥ የምንሞት አለን። መቼ እንደ ሆነ አናውቅም እንጂ ሁላችንም የዚህ ፍጻሜ ደራሽ ነን።



ጥሎ የሚመጣው ጥያቄ “ቀሪው ሕይወታችሁን እንዴት ነው ማሳለፍ የምትፈልጉት? የሚል ነው። ብዙ ምርጫዎች አሉን። በሁለት ምሰሶዎች ግን ልንከፍላቸው እንችላለን። አንዱ ሁሉ እንደሚሆነው ሆኖ መሞት። ሌላኛው ደግሞ የታሰበበት ሕይወት መኖር።


የመጀመሪያው ቀላል ነው። ብዙ የአዕምሮ ሥራ አያስፈልገውም። ማመዛዘን አያሻውም። ብዙኋኑን መከተል ነው። ስሜት እና ሙዳችንን እያደመጡ ብቻ መንጎድ ነው።



ሁለተኛው ግን መቆም ያስፈልጋል። መጠየቅ፣ መመርመር፣ ግራ ቀኙን ማድመጥ እንዲህም ሆኖ መሳሳት እንዳለ ማመን እና ዘወትር አስተሳሰባችንን እየመዘኑ ለመጓዝ መወሰን ይጠይቃል።



ትላንት “ኦርዌል 2+2=5” የተባለ ግሩም ፊልም እያየው ነበር። ከግማሽ ክፍለ ዘመን በፊት የኖረ ግለሰብ የዛሬን የሰው ሁኔታ በደንብ ገልጾ መጻፉ አስደናቂ ነበር። ግን ተንብዮ እንዳይመስላችሁ። ከሱ በፊት እና በሱ ዘመን እየሆነ ያለውን በማየት እና በማስተዋል ነበር የጻፈው። እንደ ዘወትር የመጣልኝ ሀሳብ “የሰው ልጅ መቼም አይቀየርም” የሚል ነበር። ልክ እንዳልሆንኩኝ የገባኝ ዛሬ ያለንበት ዓለም ከመቶ እና ከዛ በላይ በፊት ከነበረው ዓለም በነጻነትም ሆነ በመብት መከበር እጅግ የተሻለ እንደሆነ ካስተዋልኩኝ በኋላ ነበር። የኦርዌልን ፊልም ሳየው ተስፋ ነበር ያስቆረጠኝ። ይሄ ዓለም በማፍያ ፖለቲከኞች እና በስግብግብ ሀብታሞች ብቻ የሚበዘበዝ እና 99 ፐርሰንቱ ማህበረሰብ ተጠቂ እንደሆነ ብቻ እንዲሁም ጎስቋል መሆኑ የማያቆም እና መቆሚያ የሌለው አድርጌ ነበር የሳልኩት። ያ ግን ፈጽሞ ልክ አይደለም።



አዎ ጨለማ ዙሪያችንን ከቦ ሊሆን ይችላል። መጥፎ ሰዎች ሲያብቡ እና እንዳበቡም ሲሞቱ እያየን ይሆናል። ክፉ እና አስመሳይ ሰዎች በደጋጎች ላይ ሲነግሱ ተመልክተን ይሆናል። እንደ ኢዮብ በንጽህናቸው የሚቀጡ እና ጉስቁልናቸው ማለቂያ የሌለውን ግለሰቦች እና ማህበረሰቦች እያየን ይሆናል።



ይሄ ሁኔታ ከዚህ በፊትም የነበረ እና ያለ እንዲሁም የሚኖር ነው። ግን የዚህ ዓለም ጨለማ ድሮ ከነበረው በብዙ እጥፍ ቀንሷል። ይሄ ዓለም ከሺዎች ዓመት በፊት የፈሪሳውያንን ሕግ አላከበርክም ብላ አንድ ፍጹም እና ንጹሁ የሆነን ሰው የሰቀለች ነበረች። የእርሱ ተከታይ ናችሁ ብላ ሌሎችን ደግሞ ቆዳ እስከመግፈፍ የደረሰች ነበረች። ይሄ ዓለም ለጆሮ ዘግናኝ የሆኑ ግፎችን ያስተናገደች ናት። አሁን ያ በጥቂት ቦታዎች እናይ ይሆናል እንጂ በብዙ ቀንሷል። ለብዙዎቻችን ዛሬ ከመቶ ዓመት በፊት ከነበረው በብዙ የተሻለ ነው።



ለዚህም ዋነኛው የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዓይነት ግለሰቦች ነበሩ። “ጨለማን ከማውገዝ ሻማ ማብራት የተሻለ ነው” ያሉ ሰዎች ናቸው ይሄን ዓለም ወደ ተሻለ መንገድ የመሩት። እዚህ ያደረሱት። አንዲት ቅድስት በዘመኗ ክፋት በዝቶ ሰዎች ተስፋ ሊያስቆርጧት ሲመጡ፤ ያለችው “የኔ ተልዕኮ ክፋትን ማሸነፍ አይደለም። የእኔ ድርሻ ክፋትን መዋጋት ነው” ነበር።



ኢትዮጵያውያን እኔም የምጋብዛቹ ይሄን ነው። በዚህ ዘመን እንደኔው ብዙ ግራ ገብቷቹ ሊሆን ይችላል። አዋቂው ሕጻን የሆነበት ዘመን ላይ እንዳላችሁ ሊሰማችሁ ይችላል። መላ ቅጡ የጠፋበት እና አዋቂነት ያሽቆለቆለበት ዘመን ላይ ልንሆን እንችላለን። ግድ የላችሁም። ይሄን ጨለማ በማውገዝ ጊዜ አታጥፉ። እናንተ ጋር ያለው መልካምነት እና በጎ መንፈስ ግን እንዳይጨልም አደራ። መልካም እና ደግ ከመሆን አትገደቡ። ምንም ቢጨልም የእናንተ ሻማ የሚገፈው ጨለማ እንዳለ እመኑ።


ዮሐንስ አፈወርቅ ብቻውን የቆመ ቢመስለውም የእርሱን የእምነት ሻማ ግን ለማጥፋት አልፈቀደም ነበር። ኢትዮጵያኖች በዚህ የተርዕዮ ዘመን፣ ሰዎች ዋጋቸውን ከሰዎች በሚገኝ ሙገሳ እና አድናቆት ለማግኘት በሚሮጡበት ዘመን፣ የመልካምነትን ደረጃ (ስታንዳርድ) ዝቅ ላለማድረግ እንጠንቀቅ። በጥቃቅን ነገሮች ሳይቀር ክብርን መጠበቅ፣ የምግባራችንን ደረጃ ከፍ ማድረግ፣ “የእኔ የስነምግባር ማማ ይሄ ነው" ማለት አናቁም። ሁሉም በሰከሩበት ሰዓት ላይ ብንኖር እንኳ የባህሪ ማማ ላይ ለመቆም እንቁረጥ።


ጨለማን በማውገዝ ያሸነፈ የትም የለም። አይኖርምም። በብርሃን፣ በሻማቸው ያሳወሩት ግን አሉ። እኛ ጨለማን በብርሃኑ ብዛት ካሳወረው ነን። ምንም ከባድ ቢሆን ፥ ለማሸነፍ ብቻ አይደለም እዚህ ያለነው። ምክንያቱም ማሸነፍ ብንፈልግ እንኳን ሞት አንድ ቀን ይረታናል። ማንም በመሸነፋችን አይታዘበንም። ሳንዋጋ እጅ በመስጠታችን እንጂ። በማይቀረው ሞታችን መኃል የሆኑ ሰዎችን ሕይወት፣ የሆኑ ግለሰቦችን ሕመም ፈውሰን፣ ጨለማ የነበረውን ሕይወታቸውን አብረተን ካለፍን ፥ የዛኔ ሞት የማይረታው ትንሣኤ በሌሎች ሕይወት ውስጥ ጥለን እንሄዳለን። ሻማ፣ አዎ ሻማ እናብራ በዚህ ጨለማ መኃል።

 
 
 
ree


ባብዛኛው የአሜሪካ ክፍል ከፍተኛ ብርድ እና በረዶ የሚያስተናግድበት ወቅት ነው። ማህበረሰቡም ወቅቱን ለመምሰል ይጥራል። ከአለባበሱ እስከ የአኗኗር ዘዬው። በተለይ በመካከለኛው ምዕራባዊ ክፍል ያሉት ግዛቶች ከፍተኛ በረዶ እየጣለባቸው ነው። መንገዱ ጭር ያለ፣ ሰው በጊዜ ወደ ቤቱ የሚገባበት እና የሚሰበሰብበት ወቅት ነው። ከቀኑ አራት ሰዓት (ማለትም በኢትዮጵያ አስር ሰዓት) ጀምሮ ቀኑ መጨለም ይጀምራል። ትላንት በረዶ ከጣለ በኋላ የዚህ ሀገር ተወላጅ የሆነችውን የሥራ ባልደረባዬ ከውጪ ስትገባ አይቻት፣ “በዚህ በረዶ ውጪ ላይ እየተራመድሽ (walk) ነበር? የሚገርመው ግን አንቺ ምንም የመሰለሽ አይመስልም?” ስላት፤ “እኔ እንኳ መጥፎ አለባበስ እንጂ መጥፎ የዓየር ፀባይ የለም ቡዬ ነው ማመን የምፈልገው!” በማለት በዚህ አካባቢ የሚታወቀውን አባባል ተናገረች። “እኔ ግን መጥፎ የዓየር ፀባይ አለ ብዬ አምናለሁ፣ እሱንም አሁን እያየውት ነው” ብያት ተሳስቀን ተለያየን።



ይሄ አባባል ግን ብዙ ልንማርበት እንችላለን። ስንኖር ከኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ፤ ግን እነዚህን ሁኔታዎች የምናልፍባቸው ጥበቦችም እኛ ሰዎች አሉን። መሠረታዊ ሕይወታችን ሳይጓደል እና ሳይስተጓገል አስቸጋሪ ቀናትን ማለፍ እንችላለን። የመጀመሪያው ጥበብ የሚመስለኝ መቀየር የምንችለውን እና መቀየር የማንችለውን ነገር በፍጥነት ማወቅ ነው። ከዛ ሁለተኛ ጥበብ አለ። የሚከተል። አሜሪካኖች አንድ ድንቅ ጸሎት አላቸው ፥ እነዚህን ሁለቱንም ጥበቦች በአንድ ላይ ያዘለ።


“ጌታ ሆይ መቀየር የምችለውን ነገር ታግዬ እንድቀይር ጀግንነትን ስጠኝ ፥ መቀየር የማልችለውን ነገር ደግሞ እንድቀበለው መረጋጋትን አድለኝ። ሁለቱን መለየት የሚያስችልን (መቀየር የሚቻል እና መቀየር የማይቻልን) ጥበብን ለግሰኝ።” የሚል።



የሰው ልጅ ብዙ ዕድሜውን የሚጨርሰው መቀየር የማይችለውን ነገር ለመቀበል ተቸግሮ ሲታገለው፤ መቀየር የሚችለውን ነገር ደግሞ ለመታገል በስንፍና እና በፍርሃት ጊዜ ሲፈጅ ነው። በርግጥ በጣም ከባዱ ነገር የትኛው ነገር ይቀየራል ፥ የትኛው አይቀየርም የሚለውን ማወቁም ላይ ነው። ምክንያቱም ብዙ አይቻልም፣ ይሄ የሰው ልጅ ሊያደርገው ፈጽሞ አይሆንም የተባሉ ነገሮች ተደርገው እና ተለውጠው ታይቷል። ለዚህ ነው ያንን ለመለየት አሜሪካኖች ጥበብን የጠየቁት። ኔልሰን ማንዴላ “it is impossible until it is possible ፥ የማይቻል ነበር እስከሚቻል ድረስ” የሚል አባባል አለው።



ብዙ አንባገነነ መንግስታት በሕዝባቸው ላይ መጫን የሚፈልጉት ስነልቦና እነሱን መቀየር የማይቻል መሆኑን ማሳየት ነው። ለዚህ ደግሞ ራሳቸውን ሥዩመ እግዚአብሔር ከማለት እስከ ፈጣሪ ነን ወደሚል ፕሮፖጋንዳ ይነዛሉ። ብዙሁን ሕዝብም ለብዙ ዘመን የስነልቦና ሽባ ያደርጉታል። አንድ ቀን ያ ደፋር ልጅ “ንጉሱ ራቆቱን ነው” እስከሚል እና የሕዝቡን ዓይነ ጥላ እስከሚገልጥ ድረስ።



በተመሳሳይ የዛሬ ሶስት እና አራት መቶ ዓመታት በዓየር ላይ መብረር ለአዋፋት እና ለመላዕክት ብቻ የተተው ጉዳይ ነበር። የራይት ልጆች ተነስተው ያን እስከሚለውጡት ድረስ። የሰው ልጅ ዛሬ ላይ ያሉት የቴክኖሎጂ ውጤቶች አብዛኞቹ ከመቶ እና ከሀምሳ ዓመታት በፊት በሕልም እንኳ የማይታሰቡ ጉዳዮች ነበሩ። ጥበቡ ያላቸው ሰዎች ግን የማይቻል የመሰለውን ነገር እንደሚቻል አሳዩን። ለዚህ ነው በአሁን ጊዜ፣ አሁን ባለን አቅም መለወጥ የምንችለው ነገሮች ምን እንደሆኑ ከስንፍና እና ከፍርሃት ተላቀን ማሰብ ያለብን።



ያሄ ማለት ግን አሁን ላይ የምንቀበላቸው ውስንነቶች የሉም እያልኩኝ አይደለም። ምንም እንኳ ከመቶ ዓመት በኋላ ሰው እስከ ሁለት መቶ ዓመት መኖር የሚያስችለው የሕክምና ጥበብ ሊመጣ ቢችልም፣ ዛሬ ላይ ግን ሞት ለብዙዎቻችን ከሰማንያ እና ዘጠና ላይ እንደሚሆን መቀበል ያስፈልጋል። በተጨማሪም ትላንትን መመለስ አንችልም። ትላንት ዛሬ ያለን እውቀት ቢኖረን የማንሰራቸው ብዙ ጉዳዮች፣ ጥፋቶች ነበሩ። ስለዚህ ትላንትን መቀበል ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ የተረጋጋ አዕምሮ ያስፈልጋል። የተረጋጋ አዕምሮ ከትላንቱ ጋር ይታረቃል። ትላንቱን ይማርበታል፣ ነገም በሆነ ደረጃ ተገማች እንዳልሆነ ይረዳል። ለምሳሌ ነገ ዋጋው ይወርዳል ብሎ ዛሬ የሸጠው ንብረት ፥ ነገ የበለጠ ዋጋው ከፍ ሊል ይችላል። ስለዚህ ቢረጋጋ እና ቢጠብቅ ሊያተርፍ በሚችለው ሳይሆን የተረጋጋ አዕምሮ የሚጨነቀው፤ ትላንት ለመሸጥ ሲያስብ ለምን እንዳሰበ፣ ለምን እንደዛ ዓይነት ውሳኔ እንደወሰነ፣ ለውሳኔ የተጠቀማቸውን ማስረጃ እና መረጃ እንጂ የሚመረምረው ፥ ትላንትን ዛሬ ላይ ባገኘው እውቀት ቆሞ አይገመግምም። የተረጋጋ አዕምሮ ለወቀሳ አይደለም የሚቸኩለው። ለመማር እና ከተቻለ ዛሬን እና ነገን የተሻለ ለማድረግ ነው።



የተረጋጋ አዕምሮ ጀግንነትን ለማግኘት ይጥራል። ምክንያቱም መለወጥ የሚችሉ ነገሮችን ለመታገል ጀግና መሆን ያሻል። ብዙ ሰዎች ስኬታችንን እስከሚያዩ ድረስ ከጎናችን ለመቆም ይቸገራሉ። ሲሳካልን ነው ሊተባበሩን የሚፈልጉት። ይሄ የሰው ባህሪ ነው። የእኔም የእናንተም ባህሪ ነው። ስኬት ወዳጇ ብዙ ነው። የከሰረን እና የተረሳን ሰው “እሱኮ ምርጥ ወዳጄ ነው” ብሎ በኩራት የሚገልጽ የለም። ስኬታማን ሰው ግን ሁሉም ወዳጁ ለማድረግ ይጥራል። ሁሉም ከእርሱ ጋር ፎቶ ለመነሳት እና የእርሱ ወዳጅ ለመሆን ይጥራል። ይሄ በየትኛውም ዘመን ያለ እና የሚቀጥል ነው። ቢያሳዝንም ጀግና ሰው ግን ይሄን ይቀበላል። ስለዚህ ለመለወጥ የሚታገለውን ነገር ለመቀየር ለጥቂት ጊዜ የብቻ ትግል እንደሚሆን ያውቀዋል። ኖሕ መርከቡን ገንብቶ እስከሚጨርስ ድረስ በፀሐይ እና ዝናብ በሌለበት መርከብ የሚገነባ ሞኝ ነበር። ዝናቡ ሲመጣ እና በርግጥም የመጣው ጎርፍ የተለየ እንደሆነ ሲታይ ብቻ ነው ኖሕ ጠቢበኛ የተባለው። ለብዙ ዘመን ግን ሞኝ ተብሎ ለመቆጠር መፍቀድ ነበረበት። ለጥቂት ጊዜ ብቻችንን ለመቆም ካልፈቀድን መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮችን ሳንቀይር ሕይወታችን ያልቃል።



ገጣሚው ሮበርት ፍሮስት እንዳለው በመጨረሻ የሚቆጨን ከሞከርነው ነገር ይልቅ ያልሞከርነው ነው። ብዙ ሰዎች መለያየት ካለባቸው ሰው ጋር በፍርሃት ታስረው አንድ ሕይወታቸውን ያባክናሉ። ማቋረጥ ያለባቸውን ሥራ በፍርሃት አቅፈው ይዘው የፈጠራ አቅማቸውን ያባክናሉ። ብከስርስ በሚል ስጋት አቅማቸውን ይቀብሩታል። ከዛም መቀየር የሚቻሉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይቀጥላሉ። እያማረሩ ሕይወታቸውን ይጨርሱታል።



በበረዶ ላይ ከወዳጄ ጋር እየተራመድን ነበር። “በዚህ ብርድ ይሄን ሁሉ መንገድ መጓዝ ጥቅሙ ምንድነው?” አልኩት። “ጽናተ ቅስም ታዳብራለህ” አለኝ። ትላንት መጥፎ ያልኩት ዓየር ፀባይ ዛሬ ብሶበት ነበር። ግን ከጥሩ ልብስ ጋር ጭራሽ ለጥቅም አዋልኩት። ስቤን እያቀለጥኩኝ ቅስሜን ደግሞ አጸናውበት።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page