top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 2 days ago
  • 3 min read
ree

አሸናፊው ስብዕና ነው ደግነት። በዚህ ምድር ላይ ሰውን ወደ ሕይወታችሁ ለማስጠጋት አንድ መለኪያ፣ አንድ ሜቲሪክ፣ አንድ ሚዛን ብቻ ቢኖራችሁ። ያ ደግነት መሆን አለበት። ጥሩ ነገሩ ብዙ መለኪያዎች አሉን። ግን ደግነት የጎደለው ሰው ሁሉ ነገር ቢኖረው እንኳ በፍጹም ወደ ሕይወታችን መግባት የለበትም። ደግነት የሰው ልጅ የመልካምነቱ ውሃ ልክ ነው። ምንም እውቀት ቢኖረው ሰው ደግ ካልሆነ በዚህ ዓለም ላይ እዳ እንጂ ትሩፋት አይደለም። ምንም ገንዘብ እና ጠቃሚ ምግባሮች ቢኖሩት ደግነት የሌለው ሰው ይሄን ዓለም የመረዳት አቅም የለውም።

 

ደግነት ሕጻን ሲያይ ይራራል። ደግነት ሰው ሲያይ ያ ሰው ምስኪን እናት እንዳለችው፣ እህት ና ወንድም እንዳሉት፣ ልጆች ሊኖሩት እንደሚችሉ ያስባል። ደግነት የሰው ልጅን የዓለም መጋረጃ ከፍቶ በዛ ሰው ውስጥ ያለውን ውጣ ውረድ ለመመልከት ይችላል። ደግነት የሰውን የውጣ ውረድ ታሪክ ሲሰማ እንባውን ያፈሳል። ሕይወት በሞት አላዝር ፊት እንባውን እንዳፈሰሰ።

 

ሁላችሁን እስቲ ወደ ጋዛ ልውሰዳችሁ። የዋህ እና ደግ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእነዛ ሕጻናት መካከል በእግሩ ቢራመድ ምን የሚል ይመስላችዋል? እናንተ ሙስሊሞች፣ እናንተ የነገ ሀማሶች፣ እናንተ የእፉኝት ልጆች የሚል ወይስ እነዛ ያለ አባት፣ እናት፣ ወንድም እና ቤት ከቀሩ ልጆች ጋር የሚያነባ ይመስላችዋል? ደግነት የሚያደርገው ያቺን ሳምራዊት ሴት ያሳያትን ደግነት ነው ለእነዚህ የጋዛ ሕጻናት የሚያሳየው። አብሮ ቁጭ ብሎ ያነባል። አብሮ መከራቸውን ይጋራል።

 

ደግነት ፍርሃቱ እንዲያሸንፈው አይፈቅድም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሥጋ ፍርሃት ራሱን አሳልፎ የሰጠ ቢሆን ምን ሊሆን እንደሚችል አስቡት። በቀራጩ ቤት ምሳ አይበላም። በዛች በዘማዊት ሽቱ ለመዳሰስ እና ለመታጠብ አይፈቅድም ነበር። ምክንያቱም ሰው ምን ይለኛል፣ ባህሉ እና የተዘረጋው መዋቅር ምን ይፈርድብኛል ብሎ ከፈሪሳውያን ጋር ይቆም ነበር።

 

ደግነት ግን ድንጋይ በእጃቸው ጨብጠው አንዲት ምስኪን ሴትን ለመውገር በተሰበሰቡ ሰዎች ፊት አጎነበሰ። ያቺን ሴት ሊያድን መሬቱን ፋቀ። ደግነት ድንጋይ (መሳሪያ) ከያዙ ሰዎች ጋር አይተባበረም። ደግነት የክፋትን ሠራዊት ይበትናል እንጂ። ዘማዊቷን ለማዳን ደግነት ምንም አይሸማቀቅም። የሌሎች ክፋት ለእነርሱ በችግራቸው ጊዜ ለመድረስ የእርሱን ርህራሔ አያጎድለውም። ልቤ ሆይ ደግነትን በየቀኑ ተማር።

 

ደግነት ፊት ለፊቱ ላለው የሰው ልጅ የውጣ ውረድ ሕይወት ቦታ ይሰጣል። ከፍርሃት ጋር አይቆምም። ቡዙዎቻችን በሚገባ ፍቅር እና የሰው ልጅ ደግነት መካከል ያደግን አይደለንም። ዛሬም በሕግ ማስከበር ሰበብ ከሀገራችን ኢትዮጵያ እስከ አለንበት የስደት ቦታ ድረስ የምናየው የክፋትን ጥግ ነው።


በቤተመንግስት ውስጥ ሆኖ ስለ አትክልቱ እና በእግሩ ስለሚራመድበት የውበት ኮሊደር የሚጨነቅ መሪ እንጂ በእርሱ ወታደሮች እና ድሮኖች ስለሚናጋው የቤተሰብ ሕይወት እምብዛም የማይገደው የጭካኔ መሪን ነው የምናየው። ግን ይሄው መሪ ጩጬ ምስኪን ወንድ ልጅ አለው። ወንድ ልጁን ይወዳል። ሌሎችም እንደርሱ የሚወዱት ልጆቻቸው እየተገደሉባቸው እንደሆነ ግን ማሰብ አይፈቅድም። ልቡን ለደግነት አልከፈተውም። ነጻ አውጪ ነን ያሉትም ነጻ እናወጣዋለን ያሉትን ሕዝብ በግፍ ቀንበር ይገርፉታል።

 

ተሰደን በመጣንበትም ሀገር ማስክ ያጠለቁ ሰዎች የጭካኔ እና የዘረኝነት ክፋታቸውን በኢሚግሬሽን ሰበብ በምስኪን ሰዎች ላይ ያዘንቡበታል።



ዛሬ ያለን የነገ አፈሮች ነን። ነገ በታሪክ መጻፍ ውስጥ እንኳ የማንገባ ኢምንቶች ነን። ይሄ እድሜያችን በሚገርም ፍጥነት ይበራል። ከዛም ያልቃል። በሞት ወደ ምንምነት እንቀየራለን። እንግዲህ ለዚህ ሕይወት ነው ሰው ጎድተን፣ በሌሎች ላይ ጥቅም ይዘን፣ ተቆሳስለን የምናልፈው። ከልጅነት ጀምሮ በጭቆና ያደግንበትን በሌሎች ላይ ድጋሚ ያን ክፋት እና ጭቆና አንጸባርቀን እናልፋለን። የተጎዳ እና ያልታከመ ልብ ፥ ሌሎችንም ጎድቶ እና አቁስሎ ያልፋል።

 

ደግነት የሌለው ሰው ሌላው ሁልጊዜ ያስፈራዋል። ደግነት የጎደለው ሕይወት ሌላው ጥቅም እንደሚይዝበት፣ የእርሱ. የሆነውን ነገር ሊነጥቀው እንደሚፈልግ ነው ሁልጊዜ የሚያስበው። ደግነት አልቦ ሰው በቁስ ማጠራቀም ሕይወቱን ያፍናታል። ከሰው ጋር ነጻ ሆኖ መደሰት አይችልም። በትንንሽ ነገሮች መሳቅ አይችልም። ነጻ ያልሆነ፣ ያልተላቀቀ፣ የሚከብድ ስብዕና ነው ያለው። ሁልጊዜ ያስመስላል። ከፍ ያለ ቦታ ላይ ሲሆን ደግሞ ይጨቁናል። እድሉን ሲያገኝ ያሰቃያል።

 

በየቀኑ በጉዞአችን፣ በየቀኑ በሥራችን፣ በየቀኑ በመንገዳችን የተጎዱ ሰዎች ይገጥሙናል። ደግነትን ሆን ብለን ካልተለማመድን ፍርሃት ነው ባህሪያችንን የሚቆጣጠረው። ያን ጊዜ እነዚህን ሰዎች መልሰን እንጎዳለን። ለዚህ ነው የበራችን መቀነት ላይ፣ የየቀን መንገዳንች ላይ “ልቤ ሆይ ደግ ሁን!!!” ማለት ያለብን። ቢያንስ ባንደበታችን ሰው ላለመጉዳት መጠንቀቅ ይኖርብናል። ክፉ ከመናገር እና ሰውን ከማቁሰል ራሳችንን መገደብ ይኖርብናል። “ልቤ ሆይ ደግ ሁን” ልንለው ይገባል። ለሰዎች ብለን ብቻ እንዳይመስላችሁ። ደግነት የራሳችንን የልጅነት እና የአዋቂነት የመንፈስ ትሮማ (ስቃይ) እና የውስጥ ቁስል መፈወሻ ብቸኛው መድኃኒት ስለሆነም ጭምር እንጂ። የደግነት እንባ የውስጥ ቁስል ፈዋሽ ፋፋቴ ነው። ከመፍረድ ያዘገያል ደግነት። የማናውቀውን የሰው ልጅ ሕይወት መጋረጃ ከፍቶ ያሳየናል።


ለጊዜያዊው ለዚህ ሕይወት ውበቱ እና ክብሩ ደግነት ነው። ደግ የሆነ ሰው ትንሿን ዘመኑን ያከብራታል።


በሞቱ አልጋ ላይ የመጨረሻ ዓይኖቹን ሲጨፍን ለዚህ ነበር ብሎ አይዘጋውም። ይሄ ሕይወት አጭር እንደነበረ ገና ድሮ እንደገባው ግን ደግሞ የሌሎችን ቁስል ፈውሶበት ያሳለፈው መሆኑን በማየት እየሳቀ ዓይኖቹን ይጨፍናል።

 

ልቤ ሆይ ደግ ሁን።

 
 
 
ree


አላን ዋትስ ስለ ካርል ዩንግ በጻፈው መጣጥፍ ላይ ከራሱ ጋር የታረቀ ሰው በዚህ ዓለም ላይ ካርል ዩንግ ነበረ ይላል። ዩንግ ራሱ ላይ ያሉትን ሕጸጾች እና ድካሞች በይሁንታ ያለማፈር የተቀበለ ሰው ነበር። በተለይ በ1950ዎቹ ሲዊዘርላንድ ላይ ለቀሳውስት ያደረገው ንግግሩ ዩንግ የሰውን ተፈጥሮ በጥልቀት መረዳቱን የሚያሳይ ነበር።



ሰዎች ለራሳቸው ጥቅም እንደሆነ እስካወቁ ድረስ ምንም ክፋትን በሰዎች ላይ የማድረግ አቅም አላቸው። የሰው ልጆች በጎ ላደረገላቸው እና መልካሙን ነገር ለሰጣቸው ሳይቀር የእነሱ ሕይወት የሚሰምር ከመሰላቸው ወይም በጣም የሚፈልጉት ነገር እንዲሆንላቸው የወደዱ እንደሆነ ክፋትን ለማድረግ ፈቃደኛ ናቸው። ለዚህ ነው ለክርስቲያኖች የክርስቶስ ሕይወት አስገራሚ የሆነው። ምክንያቱም በበርባን ምትክ ንጹሁ ክርስቶስ ለመሞት ፈቅዷልና። በቅርብ አንድ ወዳጄ ስለ ልጁ ነገረኝ። ልጁ ገና አራት እና አምስት ዓመቷ ነው። በቤቱ ውስጥ እርሷ ነበረች እንደ እንቁ የምትታየው። ነገር ግን አዲስ ልጅ ሲወለድ የቤተሰቡ ትኩረት ሁሉ ወደ ሕጻኑ ሆነ። ከዛ ይህች ሕጻን ልጅ አዲስ የተወለደውን ልጅ ጠላችው። መምታት ጭምር ፈለገች። እኔን በጣም የገረመኝ የአንዲት ነፍስ ያላወቀች ልጅ ሪያክሽን ራሱ ከፍቅር ይልቅ ቅናት መሆኑ ነው። በዚህ ዓለም ላይ ገና ክፍትን ያልተማረች ሕጻን ልጅ ተፈጥሮዋ የነገራት አዲስ የመጣው ልጅ ትኩረቱን ስለወሰደ ጠላትሽ ነው የሚል ነው። ይሄ የሚነግረን የሰው ልጅ ጠባዩ እንስሳዊነት ሲሆን፤ ተፈጥሮውም እስካልተገራ ድረስ ከበጎነት ይልቅ ለክፋት የተመቸ መሆኑን ነው።



ለዚህ ነው ሰው የራሱን ጥቅም ከሚያጣ፤ ሰዎችን አሳልፎ መስጠት እና መጉዳት ምርጫው የሚሆነው። ይሄን ለክፋት የተመቸን ማንነታችንን እውቅና ካልሰጠነው እና በፍጹም ሰብአዊ አስተሳሰቦች እና ክርስትናዊ ፍቅር ካልገራነው በቀር ሰው አውሬ ነው። ክርስቶስን የተለየ የሚያደርገውም ይሄ ነው። ተፈጥሮ ለመልካም ነገሮች ያደላ ነው። ፍጹም ስለራሱ ሕመም ብቻ ማሰብ በሚገባው የመስቀል ሰዓት ያሰበው ከራሱ ይልቅ ስለ ሰቀሉት ምህረትን ነበር። ከዛም ለሚወዳት እናቱ ልጅ እና ተንከባካቢን መስጠት ነበር። ከዛም በዛ መራራ ሰዓት አንተም እንደኛው ወንጀለኛ ነህ እያለ በሚከሰው አላዋቂ ከመናደድ እና ከመራገም ይልቅ በሌላኛው ጎኑ ሆኖ አንተ ልዩ ነህ ያለውን ያን ሰው የገነት ቁልፍን መስጠት ነበር ሥራው ያደረገው። ለክፋት ፈጽሞ አልመለሰም። ከክፋት ጋር ድርድር ውስጥ አልገባም። ፍርድን ሊሰጥ ከማይችል ከጲላጦስ ፊት አለፈለፈም። ሦስቴ የከሰሰውን ሰው ከሰስከኝ ብሎ አላወራውም። ይሄ ሁሉ ክፋት ምንም አላስደነቀውም።



የበሰሉ ሰዎች የሚደርሱበት ደረጃ ያ ይመስለኛል። በሰው ክፋት አለመደነቅ። ከሰው ልጆች ሞራል እና ከፍታን አለመጠበቅ። የሰው ልጅ ተፈጥሮ በሆኑ ጉዳዮች ጉድ አለማለት። ያ ብቻ ሳይሆን እነርሱም ለዛ ክፋት ብቁ መሆናቸውን ማወቅ። ለጴጥሮስ መመለስ ትልቁ አስተዋጽኦ ክርስቶስ በርሱ መክዳት አለመደነቁ ነው። የሰው ልጅ የሚድን ከመሰለው ሁሉን ትቶ የተከተለውን መልሶ ይክደዋል።



ተመልከቱ አሜሪካ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን ጉድ። በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ክርስትናን የሚያራምድ ነው። አሜሪካ ውስጥ በባለፉት ሃምሳ ዓመታት ውስጥ እንደዚህ ጊዜ ስደተኞች ባይተዋርነት ተሰምቷቸው አያውቅም። ጥቁር እና ስደተኛ ፍጹም ወደ ሆነ ባይተዋርነት እየተገፉ ያለበት ዘመን ላይ ነን። አንገታቸው ላይ መስቀል ያደረጉ እና የቻርሊ ከርክን መገደ አስመልክቶ ወደ ቤተክርስቲያን እየጎረፈ ያለ የትረምፕ ደጋፊዎች ናቸው ስልጣን ላይ ያሉት። ከክርስትና በላይ ለስደተኞች መጨነቅ ያለበት ሃይማኖት መኖር ያለበት አይመስለኝም። ምክንያቱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰደደ ነበር። ለስደተኞች ፍጹም ርህራሄ እንድናሳይ የተጋበዝንበት ሃይማኖት ነበር። ክርስትና መሠረቱ፣ ምሰሶው፣ ጣሪያው ሁሉ ምስኪኖችን እና መሄጃ የሌላቸውን በመቀበል ላይ የተመሰረተ ነው። ቤተክርስቲያን ለዚህ ነው የስደተኞች ቤት የምትባለው። ተሰደው የመጡ ሰዎች የሚጠለዩት የክርስቶስ ቤት ውስጥ ነው።



አሁን ግን ክርስትና የሰው ክፋትን ሊገራው ይቅርና የመጨቆኛ መሳሪያ ሆኖ መጥቷል። ኃጢያተኞች ቤት እየሄደ በአመንዝራዋ እንባ እግሮቹ የታጠበ፣ በቀራጩ ቤት እራት የበላ፣ ከወንበዴው ጋር ንግግር ያደረገ፣ ባል እየቀያየረ ከኖረች ሴት ጋር ለማውራት በጠራራ ፀሐይ ወንዝ ዳር ቁጭ ብሎ የጠበቀን አምላክ የምናመልክ እና የምንከተል ሰዎች ፈጽሞ ልንሆን አንችልም፤ አሁን የምናደርገውን እያደረግን። ይሄ የክርስትና ተቃራኒ ነው። ይሄ ፖለቲካ እንጂ ክርስትና፣ ሃይማኖት ሊሆን አይችልም። ለባህሪያችን የሚስማማ ነገር እያደረግን ክርስቲያን ተብለን ልንጠራ አንችልም።



ለዚህ ነው ዩንግ በዚህ ስብከቱ ለእነዛ ቀሳውስት የክርስትና መሠረቱ በራሳችን ውስጥ ያለውን በርባንን፣ ያን ወንበዴ፣ ያን ዘረኛ የሆነውን እና ቡድነኝነት የሚስማማውን ተፈጥሮአችንን መቀበል ነው ያለው። በርሱ ማፈር ሳይሆን መቀበል፣ በውስጣችን እንደሚኖር ማወቅ ነው ያለብን። ምክንያቱም ሰዎች እንደዛ ነን። ያንን በውስጣችን ያለው የክፋት ጥግ ስናውቅ ሌላው ላይ የመፍረድ አቅም አይኖረንም። ሌሎችንም ከፍ ወዳለ ስብዕና እና እርከን ማውጣት እንችላለን። ያኔ ብቻ ራሳችንን ወደ ማወቅ እና ክርስቶሳዊ ፍቅርን ወደ መላበስ ማደግ እንችላለን።


አረመኔያዊ ነገሮች ሊደርሱብን የፈቀድን ካልሆንን የክርስቶስን ፍቅር መሸከም የምንችል አይመስለኝም። ምክንያቱም መልካም ካልሆንን የሰዎች ክፋትን መቋቋም እንችላለን። የሰዎች ክፋትን ስናውቅ ነው ደግሞ እውነተኛ መልካም መሆን የምንችለው። ምክንያቱም በጎ እንደሚሰጠን እያመንን መልካም ካደረግን’ማ ከተፈጥሮአችን ተቃራኒ የሆነን እምነት አልተከተልም። ክፋት እና መከዳት እንደሚጠብቀን አምነን መልካምነትን የመረጥን ከሆንን ብቻ ነው በመርህ እየተጓዝን ያለነው። በሰው ልጆች እንደምንጎዳ አውቀን ነው ፍቅርን የመረጥነው። ባጎረስን እንደምንነከስ በፍጹም ጠብቀን ነው እጃችንን በክፋት አፍ ውስጥ የከተትነው። ለምን? ይሄ ምርጫ ነው። ምርጫችን በጨለማው ዓለም ውስጥ ጨለማ ላለመሆን ነው። በጨለማው ዓለም ውስጥ ላለመታየት የፈለገ ሰው እርሱም ጨለማ ነው መሆን ያለበት። ከጨለማው ጋር የተባበረ በጨለማው አይጎዳም። የጨለማውን ጨለማነት በመልካም ባህሪ እና በፍቅር ለመለወጥ የፈለጉ ሰዎች ብቻ በዚህ ዓለም ክርስቲያን ተብለው ይጠራሉ። ከዓለም እና ከተፈጥሮአችን ግብዣ ውጪ ክፋትን በክፋት ላለመመለስ ወስነዋልና። እንደሚጠቁ እና እንደሚከሰሱ እያወቁ ራሳቸውን ለሚበልጠው የስብዕና ማማ አሳልፈው ሰጥተዋል። ከርሱ የመከዳት የውስጥ ሕመም እና የሀሰት ክስ ስቅላት ቁስል ጋር አሁን ተባብረው ፥ ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ለመተባበር የመርህ ውሳኔ አድርገዋል። በስም ሳይሆን በተግባር ክርስቶስን ለመምሰል መጣር የእነዚህ ራስን እና ሰውን የመረዳት ጉዞ እና ከዛ ተፈጥሮአችን በተቃራኒ የመጓዝ ውሳኔ ነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Sep 28
  • 5 min read

ree


Written on April 7, 2023 and you can find the original post with this link. (https://www.facebook.com/profile/100002335758452/search/?q=ጄኔራል%20አበባው)



እኔ አንተን የትላንት ታሪክህን ጠቅሼ መክሰስ አልፈልግም። ስለኢትዮጵያም ያለህን እምነትህን እና ፍቅርህን መጠየቅ አልሻም። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ውስጥ ሆነህ ፥ ሀገራችንን ለማገልገል መፍቀድህ በራሱ ለእኔ ትልቅ ቁምነገር ነው። ነገር ግን ባለፉት 5 ዓመታት ሁላችንን ብዙ ነገር አስተምሯል ፥ “ኢትዮጵያ ሱስ ናት” ብለው በቃላቸው ፥ በተግባር ግን አንዱን ብሔር ነጥለው የሚመቱ ፥ 3 መቶ አማሮች በየቀኑ ሲረግፉ ፥ መንገድ ዳር ከተከሉት እና ለጠወለገባቸው አበባ ያሳዩትን ብስጭት ለአማሮች ሞት መግለጽ ያልቻሉ መሪዎችን ነው ያየነው። “አዲስ አበባ ውስጥ የኦሮሞ ጥላቻ አለ” ብሎ ጠረጼዛ እየደበደበ የተናገረ ጠቅላይ ሚኒስትር ፥ 3 መቶ አማሮች በቀን ሲታረዱ ግን ድግስ እየደገሰ ሲደሰት ለህዝብ ያሳያል። ወገኔ ላለው ተጠላ ብሎ በፓርላማ ያዙኝ ልቀቁኝ ሲል ፥ ከመጠላት አልፎ ሕጻን አዛውንት ሳይቀር በገፍ ለታረዱበት የአማራ ሕዝብ ግን የውሸት ሐዘናቸውን እንኳ ሊያሳዩት አልፈቀዱም። ጄኔራል አበባው ፥ ንግግር ሰምተን እና አምነን እማ ፥ ዐብይ አህመድን ልባችን እስኪወልቅ ደግፈነው ፥ ሞቱን ሳይቀር ለመሞት መርጠን ነበር። የዛሬ 5 ዓመት ለዐብይ አህመድ የድጋፍ ሠልፍ ሲወጣበት የነበረው የአማራ ከተሞች እና መንደሮች ነበሩ።ለምን?



 (የዛኔ ከጥቂት የኦሮሚያ ከተሞች በቀር ለዐብይ የተደረገ ሠልፍ አላስታውስም።ከ5 ዓመት በኋላ ቃሉን ሳይሆን ተግባሩን ያዩ ሰዎች ለድጋፍ የወጡት በኦሮሚያ ነው።)

 አማራ ዐብይ አህመድ “መደመር ይሻለናል ፥ አንድነት ይሻለናል” ስላለ እንጂ ፥ ዐብይ ኦህዴድ መሆኑ ጠፍቶት አልነበረም የደገፈው። አማራንም ጠቅማለው ስላለው አልነበረም። ይልቁስ ጄኔራል ፥ ዐብይ አህመድ ያለን ዛሬ ልክ አንተ ያልከንን ነበር። “አንድነት ይሻላለና ፥ ስንደመር ነው ኃያል የምንሆነው” ነበር ያለን። ዛሬ እሱን የሚያምነው ስለሌለ አንተ እነዚህን ቃላቶች እንድትናገር ላከክ። አንተም የዛሬ 5 ዓመት እሱ የተናገረውን ሳትቀንስ እና ሳትደምር ፥ “በጋራ አድርገን አንድ ጠንካራ ኃይል ልንገነባ ነው” አልከን። ጄኔራል አንተ ሰው አማኝ ምንአልባትም እንዳልከው ፖለቲካ ብዙ የማትወድ ትሆናለህ። እኔም ብችል እንዳንተ ብሆን እና ለዚህ ሕዝብ የተደገሰለት ግፍ ባይገባኝ እመርጥ ነበር። ግን ትምህርቴ እና የሥራ ልምዴ ዓይኖቼን ከፍቶታል። ማኪያቬሌ እንዳለው ፥ ሕይወት ሰዎች የሚናገሩትን ሳይሆን የሚሰሩትን እንድመለከት አስተምራኛለች።

ለዚህ ነው ውድ ጄኔራል አበባው ፥ የምትናገረው ነገር ከሚሰራው ጋር ፈጽሞ አይገናኝም የምልህ። በርግጥ አንተም የምትናገረውን ብዙ ያመንክበት አይመስልም ፥ ምክንያቱም ባንድ በኩል ትልቅ አቅም እንደተገነባ እየፎከርክ ታወራለህ በሌላ በኩል ደግሞ “ዛሬ ባለችው ኢትዮጵያ አይደለም ሰው በነጻነት ሰላም ተሰምቶት ከክልል ክልል ሊሄድ ከቤቱ ወጥቶ ማምሸት እንደማይችል” ትገልጻለህ። ደግሞ መልሰህ ትፎክራለህ። አንድ አባት በአንድ ወቅት ሲናገሩ እንደሰማውት የተሸነፈ ሠራዊት ፉከራ ያበዛል ፥ አንተም አቅማችን ኃይል ነው ብለህ ሳትጨርስ ሰው ከቤቱ ወጥቶ ማምሸት የማይችልበት ኢትዮጵያ እንደተፈጠረች ትነግረናለህ።



የሕዝብ አመጽን ማፈን የሚችል ኃይል ተገንብቷል ፥ ማንም ምንም የማምጣት አቅም የለውም በተደጋጋሚ ትላለህ። ጄኔራል ፥ አንተ የውጭ ፖለቲካ አትከታተል ይሆናል። አይደለም ኢትዮጵያ ውስጥ ፥ አሜሪካ ውስጥ ራሱ የእርስ በእርስ ጦርነት ሊነሳ ይችላል አይችልም የሚሉ ክርክሮች በስፋት በሙሁሩ ዘንድ እየተካሄደ ነው። ይሄ ማለት በኃይል ስልጣን ሊይዝ የሚያስብ አለ ማለት ነው። የማይቻል ነገር ደግሞ አይታሰብም። በአሜሪካ እንኳ ሊሞከር የሚችልን ነገር ነው እርሶ ገና እየተገነባ ያለ ሠራዊትን ይዘው እንዲህ የሚፎክሩት።



 እሱ ብቻ ግን አይደለም ፥ አንት እንዳልከው ኃይል ስልጣን የመያዣ መንገድ ብቻ ሳይሆን ፥ በስልጣን ላይ ያለን የማስገደጃም ነው። ለምሳሌ በሕዝብ ከተመረጠ የወራት ዕድሜ ያለው የቢቢ ናታኒሆን (የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር) መንግስት ፥ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን የመወሰን እና ህገ-መንግስታዊ ጉዳዮችን የማየት አቅም የሚያሽመደምድ ረቂቅ ሕግ ለፓራላማው አቅርቦ ሊያጸድቅ ነበር። እስራኤሎች ግን ገና ከመረጡት ወራት ባስቆጠረው ጠቅላይ ሚኒስትራቸው ላይ ሕዝባዊ አመጽ ጠሩ። ምክንያቱም የእስራኤል ብቸኛ ነጻ ተቋም ፍርድ ቤቱ ነበር። ይሄን አጡት ማለት ዲሞክራሲ በእስራኤል አበቃለት ማለት ነው። ቢቢ ናታኒሆን እስራኤልን በመውደድ አቻ የሚገኝለት ሰው አይደለም። ግን ፖለቲከኛ ነው። ፖለቲከኛ ስልጣንን ከምንም ነገር በላይ ይወዳለ። እሱ ብቻ ግን አይደለም። ፖለቲከኛ ብዙ ጊዜ እጁ ቆሻሻ ነው ፥ ስለዚህ ተጠያቂነትን ማስቀረት ይሻል። ለዚህ ነው ከራስ በላይ ንፋስ ብሎ ፥ በእስራኤል የዲሞክራሲ ምሰሶ ላይ የዘመተው። ሕዝብ ግን አደባባዩን አጥለቀለቀው። መንገዶችን ዘጋ። ቢቢ ናታኒሆን በቅርብ ተመርጬ ይሄ እንዴት ተደርጎ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ አላለም። ምክንያቱም ምርጫ ማለት ኮንትራት ነው። ኮንትራት ማለት ውል ነው። ከአንድ ድርጅት ጋር ለ5 ዓመት ውል ገባህ ማለት ፥ ድርጅቱ ሊጠግንልህ የቀጠርከውን ቤትህን ሲያፈርስ የ5 ዓመት ውሉ እስከሚያልቅ ዝም ብለህ ታየዋለህ ማለት አይደለም። ከውል ውጪ እየፈጸመ ብቻ ሳይሆን ፥ ውሉ ያስፈለገበትን ዋነኛ መሠረት እየናደ ስለሆነ ውሉን የመሰረዝ መብት የትኛውም የአራዊት ሕግ የሌለበት ሀገር ሕግ ይፈቅዳል። የሕግ ባለሙያ ስለሆንኩ የምናገረውን አውቃለው።

በተመሳሳይ የዐብይ አስተዳደር አንድነትን የመፍጠር ቃልኪዳኑ ቀርቶብን እንደ ድሮ ተከፋፍለን እንኳ መኖር እንዳንችል እያደረገን ነው። ክቡር ጄኔራል አንተ ለኢትዮጵያዊ የምታዝን ከሆንክ ፥ በአዲስ አበባ ዙሪያ ከ10 ዓመት በላይ ከኖሩበት ቤት ኢትዮጵያኖች ሲፈናቀሉ ፥ ምን አደረክህ? እውነት ነው ያደረከውን ነገር በአደባባይ ትነግረኛለህ ብዬ ጠብቄ አይደለም ፥ ግን ኢትዮጵያኖች ቤታቸው በላያቸው መፍረሱ ሊቆም ይቅርና ፥ ራሳቸው አፍርሰው ጣሪያና በራቸውን እንኳ መውሰድ አትችሉም ነው የተባሉት። አንተ በውስጥ ስለዚህ ጉዳይ ተናግረሃል ብለን እንመን። አንተ ጄኔራሉ ማስቆም ያቀተህን የዛሬ ግፍ ፥ አማራው ነገ ስለተደገሰለት መከራ ግድ የላችሁም እኔን እመኑኝ ስትል ትንሽ ለህሊናዎ አይከብዶትም።


ጄኔራል ከስልጣን ተባሮ መኖር እንደሚቻል እኮ እርሶ በተግባር ያውቁታል። ግፍ እና ውንብድና ሰርቶ ግን መኖር ቀላል እንዳልሆነ ፥ እርሶም ከቀድሞ የትግል አጋሮቾ ለምን አይማሩም? (በቃለመጠይቁ "ከትግራይ ጦርነት ተማሩ" የሚለውን በብዛት ስለተጠቀሙ ነው። እርሶም ከቀድሞ ጓዶቾ የሚማሩት ብዙ አለ የሚለውን ለማስታወስ ነው።)

ልጠይቆትማ ጄኔራል። ከአማራ ልዩ ኃይል አባላት ጋር አብረን ጎን ለጎን ተዋግተናል። ቆስለናል ፥ ደምተናል አሉን ልበል። እንግዲያውስ ይሄን ይመልሱ። ሕወኃት ቆቦን ስትይዝ ፥ ለምናቹ የጠራችሁት ጄኔራል ፥ በዚህም ምክንያት ከ 10 በላይ ጥይቶችን በእግሩ ውስጥ የተሸከመን ባለውለታ ፥ ለአስቸኳይ ሕክምና ከአገር አትወጣም ብላችሁት እየተሰቃየ ነው። ሲሆን ሲሆን ወጪውን ችላችሁ ማሳከም ሲገባ ፥ ይሄን ምስኪን ጄኔራል ቀስ እያለ እንዲሞት ፈረዳችሁበት። ከጎንህ ሲዋጋ ለቆሰለው ፥ ለሀገሩ ዋጋ ለከፈለው ጄኔራል ተፈራ ያልቆምከውን አንተ ፥ ለሱ መሆን ያልቻልከውን አንተ ፥ በሚሊዮን ሕዝብ ደህንነት ጉዳይ እመኑኝ ነው የምትለን? ክቡር ጄኔራል ፥ እኔ በመጽሐፉ ቅዱስ አምናለው። በመጽሐፉ ቅዱስ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶ ፥ አደራ የሰጠውን ባለሟሉን ጠርቶ ያለው እንዲህ ነው ፥ “አንተ በጥቂት ታምነሃል እና በብዙ ትሾማለህ ፥ ያልታመነውን ደግሞ ያለው “አንተ በጥቂት አልታመንክም እና ያለህም ይወሰድብሃል።” ስለዚህ ክቡር ጄኔራል ፥ አይደለም በብዙ ሚሊዮን ምስኪን የአማራ ወገኔ ጉዳይ ላምንህ ይቅርና ፥ ከዛ ባነሱ ጉዳዮች ሳይቀር እምነቴ መሉ አይደለም።


በመጨረሻ የመንግስት ትዕዛዝን በሰላም የማትቀበሉ ከሆነ ፥ እንጠርጋችሃለን ብለሃል። አሁን የቀደመው ፥ ማስታወስ የማልሻው ማንነትህ ተገለጠ። ግን ክቡር ጄኔራል አንተ እንዳልከው እኛን የማጥፋት ኃይል ቢኖርህ እንኳ ፥ የሕዝባችንን መጥፋት ዓይናችን እያየ ዝም ከምንል ፥ ሁሉን መሆንን እንመርጣለን። ኔልሰን ማንዴላ እንዳለው “ሁሉም ነገር እስከሚሆን ድረስ የማይቻል ነበር።” እግዚአብሔርን የማመሰግነው ፥ “የምንሸነፍ አይደለንም ፥ ጦርነት ባህላዊ ጫዎታችን ነው” ያሉትን ሕወኃቶች ሳይቀር ፥ በእንብርክክ ይቅርታ ጠይቀው መሸነፍ የተፈጥሮ ግዴታ መሆኑን በዕድሜዬ ማየቴ ነው። የአማራ ሕዝብም እንዲህ ባለህ መታበይ ፥ እንዲገጥማችሁ አልሻም። ምክንያቱም ኃይል የእግዚአብሔር መሆኑን ከአንዴም ብዙ ጊዜ አይቻለው እና። የአማራ ሕዝብ ካሸነፈም የሚያሸንፈው የመገፋቱን መጠን ፥ የደረሰበትን ግፍ እና ስቃይ አምላክ ስለቆጠረለት ነው። አዎ ፥ ለምስኪኖች ተስፋቸው ማነው? ፥ እግዚአብሔር አይደለምን?


በዚህ ጥበዓት የአማራ ሕዝብ ለህልውናው ይቆማል ፥ ዳግም በአፈ ሞላጮች ላይሸወደ በአንድነት ይነሳል። ለራሱ ብቻ ሳይሆን ፥ በኢትዮጵያ ምድር ለሚጎሳቆሉ ሁሉ ፥ ለሚጠሉት ሁሉ ፥ የተመቸች የጋራ ቤት ፥ የእኩልነት ቤት ለማቆም ይሰራል። በመጨረሻ የዐብይ ፖለቲካ ግር ለሚላችሁ ይሄን የማኪያቬሊ ምሳሌያዊ ታሪክ ፥ መርህ ይሁናችሁ።


ማኪያቬሊ ሰውን በዓይንህ በምታየው ሳይሆን በእጁ በሚሰራው ፍረድ የሚለውን አስደናቂ ጥበብ ያገኘው በሱ ዘመን ከነበረ አንድ መጽሐፍ ነው ፥ መጽሐፉ ውስጥ የትልቋ እና የትንሻ ወፍ ወግ ይላል። ታሪኩ እንዲህ ነው። አንድ ሰውዬ ወፎችን ሰብስቦ በብረት ወጥመድ (cage) ውስጥ ያስቀምጣቸዋል። የሆነ ቀን እየጠበቀ ፥ ከወጥመዱ እያወጣ እነዚህን ወፎች አንድ በአንድ ያርዳል። ከሁሉ ሕጻን የሆነችው እና ልምድ የሌላት ወፍ ለትልቋ ወፍ ፥ “ዓይኖቹን ተመልከቺ ፥ ጓደኞቻችንን ሲያርድ እኰ አዝኖ እያለቀሰ ነው” ትላለች። ትልቋ ወፍም “ሰውዬውን በዓይኑ ሳይሆን በእጆቹ በሚሰራው ፍረጂ” አለቻት (“Judge by the hands, not by the eyes”)።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page