
ስለአድዋ አከባበር ሳስብ፣ በዚህ አከባበር የሚበሽቅ ሰው ወይም የሚናደዱ ስብስቦች ባይኖሩ እንዴት ነበር የሚከበረው ብዬ አስባለሁ? ወይም በዓሉ የይገባኛል ክርክር ባይኖርበት እንዴት ነበር ስለበዓሉ የሚኖረኝ እይታ የሚቀየረው?
ሰዎች ስንባል ስነልቦናችን ድል የሚያሰባስበን፣ ከዛ ደግሞ አሸናፊነትን ለኛ ለማድረግ የምንሮጥ ነን። ማንም ሽንፈትን ወይም ተሸናፊነትን ከራሱ ጋር ማያያዝ አይፈልግም። የሆነ ሰው ሀብታም ወይም ታዋቂ ሲሆን ዘመዴ ነው፣ ጓደኛዬ ነው፣ አውቀዋለሁ ብሎ ለመናገር እና ራሳችንን ከዛ ሰው ጋር ለማያያዝ የምንጥር ነን። አሸናፊው ደግሞ ድልን በራሱ ጥረት ብቻ እንዳገኘ፣ ጉብዝናው እና ብልሃቱ ለዛ እንዳደረሰው በመናገር ከሌሎች እሱ ልዩ የሆነበትን ነገር ለማሳየት ይጥራል። እነዚህ ወደ ማህበረሰብ ሲወርዱ ትርክት ይፈጥራሉ። ሰው ደግሞ በትርክት (story) የሚያስብ ፍጥረት ነው። ይሄ ትርክት ማንነትን ይፈጥራል። ከዚያ በዚህ ማንነት ዙሪያ እነሰባሰባለን። እንጋጫለን። ለዚህ ማንነት ብዙ ዘፈኖች፣ ወረቦች፣ ዲስኩሮች በማውረድ ፥ ከዚህ ማንነት ጋር ሁለመናችንን እናሳስራለን። አድዋ አንዱ የማንነት መገንቢያ፣ የመሰባሰቢያ እና እርስ በእርስ የመጋጫ ትርክት ነው። የድል አድራጊነት ታሪክ ስለሆነ ማንነትን በዚህ ላይ መገንባት የሰው ልጅ ዝንባሌ ነው።
ሽንፈትን ቤትውስጥ እንዳለ ቆሻሻ ከእይታ እንሰውረዋለን፣ የህሊና ሰላምም ስለሌለው ወደማይታይበት መዛግብት እንከተዋለን። ምንም እንኳን ሽንፈት የሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ከድል በላይ በዝቶ የሚገኝ ክስተት ቢሆንም ለማንነት ግንባታ ትርክት ግን አይመችም። ከድል በላይ እውነት (reality) ሽንፈት ነው። ሽንፈት ሰዎች መሸሽ የሚፈልጉትን እና የሚሸሹትን ሕመም እንዲጋፈጡ የሚያደርግ ነው። ድል ብዙ ውሸትን በውስጡ አዝሏል። ድል ከእውነት በላይ ፍላጎት ነው፤ ሽንፈት ግን የፍላጎት መነጽር የጎደለው ለእውነት የቀረበ ነው።
በየዕለት ሕይወታችን ብዙ ማንነት አለን። ከአርሴናል ደጋፊዎች ጋር መድፈኞች ነን፣ ከኦሮቶዶክስ ክርስቲያኖች ጋር ኦርቶዶክሳዊ ነን፣ እንደ ኢኮኖሚ መደባችን የመንግስት ሠራተኞች ወይም ባለሀብቶች ወይም ዲያስፖሮች ነን፣ ከገዢዎች ጋር የገዢው ደጋፊ ነን፣ ከአማጺ ኃይሎች ጋር አማጺያን ነን፣ ቀነኒሳ ወይም የዲባባ ልጆች ሲሮጡ ኢትዮጵያዊ ነን፣ ከሌላው ዓለም ጋር በሚደረግ ትግል አፍሪካዊ ነን፣ በጥቁሮች ላይ በሚደርሰው በደል ጥቁር ከሆነው ሁሉም ሕዝብ ጋር እንቆማለን፣ በምዕራባውያን ሀገር ስንኖር ደግሞ ከኮኬዥያን ውጪ ካለው ጋር የቀለም (color) ሰዎች ብለን ራሳችንን እንመድባለን፣ ስለሰው ልጆች ውድቀት ስናወራ ደግሞ ራሳችንን ከሰው ዘር ጋር ሁሉ መድበን መላዕክት እንዳልሆንን እና መሳሳት የኛ ባህሪ መሆኑን እንናገራለን። ይሄ ሁሉ ማንነት ግን በሆኑ አጋጣሚዎች ወደ ደቃቅ ማንነቶች ወርደው የትግል እና እርስ በእርስ የመገዳደል ምክንያት ይሆናል። አንድ ሰው በአንድ ጊዜ የብዙ ማንነቶች ባለቤት ቢሆንም፣ ግጭት ውስጥ የሚያወርደው ግን የብዙ ማንነቶች ባለቤት መሆኑ እና በጠላትነት ከፈረጀው ጋር ካለው ልዩነት ይልቅ አንድ የሚያደርገው እንደሚበዛ መርሳቱ እና ያን ማሰብ አለመፍቀዱ ነው።
ፋኖ እና ሸኔ ሆኖ እየተዋጉት ላሉት “ሁለቱም ኢትዮጵያዊ እንደሆኑ ወይም ሁለቱም እልም ያለ ድህነት ያደቀቀው ሀገር አባል መሆናቸው እና ሁለቱም ያለምንም የተረጋጋ ሕይወት ይሄን ዓለም በቅርብ የሚሰናበቱ ሰዎች ስብስብ አባል ናችሁ” ብትሏቸው ከመጣላት ቆም ብለው ማሰብ አይችሉም። ምክንያቱም ማንነትን ማሰብ እና ማሰላሰል ረቶት አያውቅም። (ፋኖን ያስነሳው በደል እና ግፍ ሸኔ ጋር አለ ብዬ አላምንም። ሁለቱ በብዙ ነገር የተለያዩ ናቸው)።
አንድም ብዙዎቻችን በጥቁር እና ነጭ (binary) ነው የምናስበው። ጥሩ እና መጥፎ ሰዎች አሉ፣ ደግ እና የዋህ የሆኑ እንዲሁም አረመኔ እና ርህራሄ አልባ የሆኑ ሰዎች አሉ ብለን እንጂ ማሰብ የምንፈልገው፤ በጎ ነገር ለመስራት የሚጥሩ ግን ደግሞ ፍላጎታቸው እያስቸገራቸው መጥፎ ሥራም የሚሰሩ ግራጫ ሰዎች ብቻ ናቸው ያሉት ብሎ ለመቀበል ይቸግረናል። ሁልጊዜ ወጥነት ያለን (consistent) ሰዎች እንድንሆን ስለምንፈልግ ሌሎችንም የምንረዳው እንደዛው ነው። ፍላጎት ደግሞ እውነት ሆኖ አያውቅም።
በቅርብ አንድ ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የተሰደደ እና የሕግ አገልግሎት ለማግኘት ወደ ቢሮአችን የመጣ ኢትዮጵያዊ ሶማሌ፣ ዘሬን ጠየቀኝ። “ቅይጥ ነኝ” አልኩት። “አታጭበርብር፣ ዋናው አባትህ ነው። አባትህ የምን ዘር ነው? አለኝ። ይሄን ሲሰማ የነበረ እዚህ የተወለደ እና ያደገ ሌላ ባለሙያ ደንቆት፣ “ቆይ የእናቱ አይቆጠረም ማለት ነው?” አለው። “አዎ! ዋናው አባት ነው” አለው። ይሄን ሰው እንደምሳሌ አቀረብኩት እንጂ በየቀን ውሎአችን ሰውን በሳጥን ውስጥ ከተን ለመረዳት የምናደርገው ጥረት ሁሉ አንዱን ጥሎ ሌላውን ማንሳት ነው። የሰው ልጅ እንዴት ያለ ውስብስብ የሆነ ፍጥረት እንደሆነ ለመገንዘብ አንፈቅድም። አሌክሳንደር ሶልዦቪስኪ እንዳለው “በጽድቅ በተሞላው የጻዲቁ ልብ ውስጥ የክፋት ጥግ አለ። በክፋት በተሞላው የአረመኔው ሰው ልብ ውስጥ የጽድቅ ድልድይ አለ።” ያን መቀበል ግን ለኛ ፈራጆቹ ከባድ ነው።
ከሶማሌ ክልል የመጣሁ ይሄው የሀገሬ ልጅ፣ ቀጥሎ እንዲህ ብዬ ጠየኩት። “ዘመድ አለህ እዚህ፣ ማነው እየረዳህ ያለው?” መለሰ። “እኛ ሶማሌዎች የኛ ጎሳ ካለ ይበቃናል፣ በጎሳ እንረዳዳለን። እናንተ ሀበሾች ግን የተቸገረ ሰው ስታዩ ከንፈራችሁን በመምጠት፣ እጃችሁን ጭንቅላታችሁ ላይ በማድረግ ምስኪን፣ ሲያሳዝን ብላችሁ አልፋችሁ ትሄዳላችሁ” አለኝ። ነገሩ እንደቀልድም እንደ ጥሩ እይታም ቢያስቀኝም፣ ይሄ በእርስ በእርስ ጦርነት ለ30 ዓመታት እርስ በእርስ ሲገዳደሉ ከኖሩ ማንነቶች ጋር ራሱን በጎሳ የሚያዛምድ ሰው ነው የመሀል ሀገሩን ሰው፣ በሱ አጠራር ሀበሾች የሚላቸውን በአስመሳይነት የከሰሰው። እውነት ነው የሶማሌ ማህበረሰብ እርስ በእርስ የመረዳዳት ባህል አለው። እርስ በእርስ የመገዳደልም ሰዋዊ ባህል ግን አለው። ያን የክፋት ጥግ ግን ሁልጊዜ እንደቆሻሻ ጠርገን ከሰው እይታ እንሰውረዋለን፣ ከህሊና ግንዛቤ እናርቀዋለን። ምክንያቱም ለማንነት ግንባታ አይመችም።
ከመቶ ዓመት በፊት አድዋ ላይ ድል ያደረጉ የአርበኞች ልጆች ነን። ነገር ግን መቶ ዓመት ሙሉ በረሀብ የምናልቅ፣ በስደት የምንረግፍ፣ በሕግ የሚመራ ሀገር መመስረት ያልቻልል፣ ሀገራችን ድረስ መጥተው ሊገዙን ወደ መጡት ነጮች ሀገር መሄድ እና መኖር ከልጅነት ጀምሮ ህልማችን የሆንን ዜጎች እና በክላሺንኮቭ መሳሪያ ወንድም ወንድሙን እየጣለ የሚኖርባት ሀገርም ፈጣሪዎች ነን። የመጀመሪያው ለዘፈን ይመቻል፣ ሁለተኛው ግን የየቀን ሕይወታችን እውነት ነው።