- Mulualem Getachew

- 15 hours ago
- 3 min read

ምንም ነገር ስትጀምሩ ከማይቀረው እና የግድ ከሚሆነው መጀመር በብዙ የሚጠቅም ሆኖ አይቼዋለሁ። ይሄም ማለት ከመጨረሻው ወደ መጀመሪያ ወይም አሁን ወዳላችሁበት መጥቶ ማሰብ እጅግ ጠቃሚ ነው። ማናችንም ጋር የማይቀር አንድ ክስተት አለ። ሞታችን። አሁን በዚህ ሰዓት ጨምሮ በጥቂት ቀናት እና ዓመታት ውስጥ የምንሞት አለን። መቼ እንደ ሆነ አናውቅም እንጂ ሁላችንም የዚህ ፍጻሜ ደራሽ ነን።
ቀጥሎ የሚመጣው ጥያቄ “ቀሪው ሕይወታችሁን እንዴት ነው ማሳለፍ የምትፈልጉት? የሚል ነው። ብዙ ምርጫዎች አሉን። በሁለት ምሰሶዎች ግን ልንከፍላቸው እንችላለን። አንዱ ሁሉ እንደሚሆነው ሆኖ መሞት። ሌላኛው ደግሞ የታሰበበት ሕይወት መኖር።
የመጀመሪያው ቀላል ነው። ብዙ የአዕምሮ ሥራ አያስፈልገውም። ማመዛዘን አያሻውም። ብዙኋኑን መከተል ነው። ስሜት እና ሙዳችንን እያደመጡ ብቻ መንጎድ ነው።
ሁለተኛው ግን መቆም ያስፈልጋል። መጠየቅ፣ መመርመር፣ ግራ ቀኙን ማድመጥ እንዲህም ሆኖ መሳሳት እንዳለ ማመን እና ዘወትር አስተሳሰባችንን እየመዘኑ ለመጓዝ መወሰን ይጠይቃል።
ትላንት “ኦርዌል 2+2=5” የተባለ ግሩም ፊልም እያየው ነበር። ከግማሽ ክፍለ ዘመን በፊት የኖረ ግለሰብ የዛሬን የሰው ሁኔታ በደንብ ገልጾ መጻፉ አስደናቂ ነበር። ግን ተንብዮ እንዳይመስላችሁ። ከሱ በፊት እና በሱ ዘመን እየሆነ ያለውን በማየት እና በማስተዋል ነበር የጻፈው። እንደ ዘወትር የመጣልኝ ሀሳብ “የሰው ልጅ መቼም አይቀየርም” የሚል ነበር። ልክ እንዳልሆንኩኝ የገባኝ ዛሬ ያለንበት ዓለም ከመቶ እና ከዛ በላይ በፊት ከነበረው ዓለም በነጻነትም ሆነ በመብት መከበር እጅግ የተሻለ እንደሆነ ካስተዋልኩኝ በኋላ ነበር። የኦርዌልን ፊልም ሳየው ተስፋ ነበር ያስቆረጠኝ። ይሄ ዓለም በማፍያ ፖለቲከኞች እና በስግብግብ ሀብታሞች ብቻ የሚበዘበዝ እና 99 ፐርሰንቱ ማህበረሰብ ተጠቂ እንደሆነ ብቻ እንዲሁም ጎስቋል መሆኑ የማያቆም እና መቆሚያ የሌለው አድርጌ ነበር የሳልኩት። ያ ግን ፈጽሞ ልክ አይደለም።
አዎ ጨለማ ዙሪያችንን ከቦ ሊሆን ይችላል። መጥፎ ሰዎች ሲያብቡ እና እንዳበቡም ሲሞቱ እያየን ይሆናል። ክፉ እና አስመሳይ ሰዎች በደጋጎች ላይ ሲነግሱ ተመልክተን ይሆናል። እንደ ኢዮብ በንጽህናቸው የሚቀጡ እና ጉስቁልናቸው ማለቂያ የሌለውን ግለሰቦች እና ማህበረሰቦች እያየን ይሆናል።
ይሄ ሁኔታ ከዚህ በፊትም የነበረ እና ያለ እንዲሁም የሚኖር ነው። ግን የዚህ ዓለም ጨለማ ድሮ ከነበረው በብዙ እጥፍ ቀንሷል። ይሄ ዓለም ከሺዎች ዓመት በፊት የፈሪሳውያንን ሕግ አላከበርክም ብላ አንድ ፍጹም እና ንጹሁ የሆነን ሰው የሰቀለች ነበረች። የእርሱ ተከታይ ናችሁ ብላ ሌሎችን ደግሞ ቆዳ እስከመግፈፍ የደረሰች ነበረች። ይሄ ዓለም ለጆሮ ዘግናኝ የሆኑ ግፎችን ያስተናገደች ናት። አሁን ያ በጥቂት ቦታዎች እናይ ይሆናል እንጂ በብዙ ቀንሷል። ለብዙዎቻችን ዛሬ ከመቶ ዓመት በፊት ከነበረው በብዙ የተሻለ ነው።
ለዚህም ዋነኛው የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዓይነት ግለሰቦች ነበሩ። “ጨለማን ከማውገዝ ሻማ ማብራት የተሻለ ነው” ያሉ ሰዎች ናቸው ይሄን ዓለም ወደ ተሻለ መንገድ የመሩት። እዚህ ያደረሱት። አንዲት ቅድስት በዘመኗ ክፋት በዝቶ ሰዎች ተስፋ ሊያስቆርጧት ሲመጡ፤ ያለችው “የኔ ተልዕኮ ክፋትን ማሸነፍ አይደለም። የእኔ ድርሻ ክፋትን መዋጋት ነው” ነበር።
ኢትዮጵያውያን እኔም የምጋብዛቹ ይሄን ነው። በዚህ ዘመን እንደኔው ብዙ ግራ ገብቷቹ ሊሆን ይችላል። አዋቂው ሕጻን የሆነበት ዘመን ላይ እንዳላችሁ ሊሰማችሁ ይችላል። መላ ቅጡ የጠፋበት እና አዋቂነት ያሽቆለቆለበት ዘመን ላይ ልንሆን እንችላለን። ግድ የላችሁም። ይሄን ጨለማ በማውገዝ ጊዜ አታጥፉ። እናንተ ጋር ያለው መልካምነት እና በጎ መንፈስ ግን እንዳይጨልም አደራ። መልካም እና ደግ ከመሆን አትገደቡ። ምንም ቢጨልም የእናንተ ሻማ የሚገፈው ጨለማ እንዳለ እመኑ።
ዮሐንስ አፈወርቅ ብቻውን የቆመ ቢመስለውም የእርሱን የእምነት ሻማ ግን ለማጥፋት አልፈቀደም ነበር። ኢትዮጵያኖች በዚህ የተርዕዮ ዘመን፣ ሰዎች ዋጋቸውን ከሰዎች በሚገኝ ሙገሳ እና አድናቆት ለማግኘት በሚሮጡበት ዘመን፣ የመልካምነትን ደረጃ (ስታንዳርድ) ዝቅ ላለማድረግ እንጠንቀቅ። በጥቃቅን ነገሮች ሳይቀር ክብርን መጠበቅ፣ የምግባራችንን ደረጃ ከፍ ማድረግ፣ “የእኔ የስነምግባር ማማ ይሄ ነው" ማለት አናቁም። ሁሉም በሰከሩበት ሰዓት ላይ ብንኖር እንኳ የባህሪ ማማ ላይ ለመቆም እንቁረጥ።
ጨለማን በማውገዝ ያሸነፈ የትም የለም። አይኖርምም። በብርሃን፣ በሻማቸው ያሳወሩት ግን አሉ። እኛ ጨለማን በብርሃኑ ብዛት ካሳወረው ነን። ምንም ከባድ ቢሆን ፥ ለማሸነፍ ብቻ አይደለም እዚህ ያለነው። ምክንያቱም ማሸነፍ ብንፈልግ እንኳን ሞት አንድ ቀን ይረታናል። ማንም በመሸነፋችን አይታዘበንም። ሳንዋጋ እጅ በመስጠታችን እንጂ። በማይቀረው ሞታችን መኃል የሆኑ ሰዎችን ሕይወት፣ የሆኑ ግለሰቦችን ሕመም ፈውሰን፣ ጨለማ የነበረውን ሕይወታቸውን አብረተን ካለፍን ፥ የዛኔ ሞት የማይረታው ትንሣኤ በሌሎች ሕይወት ውስጥ ጥለን እንሄዳለን። ሻማ፣ አዎ ሻማ እናብራ በዚህ ጨለማ መኃል።








