top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 2 days ago
  • 3 min read
ree


የጠቢበኛው የጥበብ መዝሙር ላይ እንዲህ ይላል “ወይናችን አብቦአልና የወይናችንን ቦታ የሚያጠፉትን ቀበሮች፥ ጥቃቅኑን ቀበሮች አጥምዳችሁ ያዙልን።” መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 2፥15።



ለመውደቅም ለመነሳትም የጥቃቅን ሕግ ወሳኝ ነው። የጥቃቅን ሕግን የሚያውቅ ሰው፣ በአግባቡ የገባው ሰው በዚህ ምድር ብዙ ርቀት ይጓዛል። የጥቃቅን ሕግ የሰው ልጅን ተፈጥሮ የስንፍናም ሆነ የውንብድና፣ የጉብዝናም ሆነ የዝናን ተፈጥሮ ያገናዘበ ነው።



ሰው ትንሣኤውም ሆነ ሞቱ በጥቃቅን ሕግ ነው።



ስናድግ በወላጆቻችን የሚነገረን ተረት ነበር። በሬ ሰሮቆ የተያዘው ልጅ። ያ ልጅ በበሬ ስርቆትን አልጀመረም ነበር። አንድ ቀን መርፌ ሰርቆ መጣ። ዝም አለችው እናቱ። ከዛ ዳቦ፣ ከዛ የሆኑ ተራ እቃዎችን፣ ከዛ እያደገ ሄደ። በበሬ ግን ተያዘ። ያኔ ወደ እናቱ ዞሮ “በመርፌ ብታቆሚኝ!” አላት። የጥቃቅን ሕግ ማለት ይሄ ነው።



አንዳንድ ጊዜ በመንገድ ስሄድ ቤት አልባ የሆኑ እና በሱስ የወደቁ ሰዎችን አያለሁ። እነዚህ ሰዎች መንገድ ላይ ከሆነ ጊዜ በኋላ ነው የወጡት። እዛው አልተፈጠሩም። ግን የትኛው ሱስ ነበር ለዚህ ያደረሳቸው? የመጀመሪያ ቀን የሳቡት፣ ሁለተኛው ቀን የሳቡት ወይስ ከሳምንት በኋላ የሳቡት ሲሻ ወይም ኮኬን ነው እዚህ ላይ ያደረሳቸው? አላውቅም። የማውቀው ግን ያን መሳብ የጀመሩ ቀን ዛሬ እዚህ ላይ እንደሚድርሱ ማናቸውም አልገመቱም ነበር።



አባት ልጁን ሌላ ከተማ ወዳለሁ እርሻው ላከው። የላከው እርሻውን እንዲያርም ነው። ልጅ ወደ እርሻው ሲደርስ ፥ የእርሻው ግዙፍነት እና መላው እርሻው በአረም መዋጡ የሥራ ቅስሙን ሰበረው። ስለዚህ ማረሙን ትቶ ተኛ። አባት ከሆነ ጊዜ በኋላ ሲመጣ ልጅ ተኝቷል። ለምን እንዳላረመ ሲጠይቀው፤ ይሄን ሁሉ እርሻ ብቻውን ማረም ከአቅሙ በላይ እንደሆነ ነገረው። የጥቃቅን ሕግ የገባው አባት ነበርና፤ ልጁን ሳይቆጣ እንዲህ አለው። “በየቀኑ በቁመትህ ልክ ብቻ አርም። ከዛ ተኛ።” ልጅ እያንገራገረ ጀመረ። ቀስ እያለ ማረሙን ወደደው፣ ከቁመቱ በላይ፣ ሁለት እና ሦስት እጥፍ ማረም ጀመረ። በጥቂት ጊዜያት ውስጥ እርሻውን ሁሉ አርሞ ጨረሰ። የጥቃቅን ሕግ በሬ ብቻ አይደለም የሚያሰርቀው። ጋሻ የሚያክልን እርሻም ያሳርማል። የርግማን ብቻ ሳይሆን የበረከትም ሕግ ነው።



በሕይወታችሁ ተኝታችሁ ካላችሁ እና ሰማይ ምድሩ በላያችሁ ላይ የተጫነ ከመሰላችሁ፤ ሰማዩን ከላያችሁ ለማንሳት ከመታገል ፥ ማንሳት ከምትችሉት ቀላል ነገር ጀምሩ። ምንም ስፖርት ከማይሰራ ሰው ይልቅ አራት ፑሽ አፕ ብቻ በየቀኑ ሰራለሁ ብሎ የተነሳ ሰው በዓመቱ መጨረሻ የተሻለ ጤነኛ ሆኖ ራሱን ያገኘዋል። ብዙ ሰው ስለቢዝነስ፣ ስለ ስኬት እና ስለሥራ ሲያስብ ዓይኑ ላይ ድቅን የሚለው የትልልቅ ሕግ እንጂ የጥቃቅን ሕግ አይደለም።



የሆነ ነገር ሥራ የምትሉት አብዛኛው ሰው ትልቅ ብር ይጠራላችዋል። ወይም ይሄን ያህል ገንዘብ ያስፈልጋል ይላል። ግን ትልልቅ ብር ያላቸው ሰዎች ሁሉ ከዛ አልጀመሩም። ይልቁንስ በእጃቸው የነበሩ ጥቂቶችን ዘሩ። ከዛ ያጨዱትን መልሰው እየዘሩ ፥ ዛሬ ጋሻው የእነሱ ሆነ። ከትንሽ ለመጀመር ያልፈቀደ ሰው ትልቅ ሆኖ መቀጠል አይችልም።



ብዙ ሰው ስለ ስርቆት፣ ሌብነት፣ ማጭበርበር ሲያስብ ፥ የሚያስበው ስለ ሳንቲሞች እና መርፌዎች አይደለም። ግን የጥቃቅን ሕግ የሚነግረን ወደ ገሀነም የሚወስደው መንገድ በቅን ልቦና የተጠረገ መሆኑን ነው። “ምንም አይደል” ብለን ዛሬ የሰበርናት ትንሽዬ ሕግ ነገ ገሀነም ላይ ታደርሰናለች።



አብይ አህመድ በአንድ ቀን አንባገነን አልሆነም። ደራሲ ሀዲስ አለማየው ስለ መንግስቱ ኃይለማርያም መለወጥ ለቪኦኤ በተናገሩበት ወቅት እንዲህ ነበር ያሉት። መንግስቱን እዚህ አውሬነት ላይ ያደረሱት ዙሪያው ያሉ ጓዶቹ ናቸው። “አንተ እኮ ነብር ነህ” አሉት። መጀመሪያ “ጓዶች እኔ እንደናንተው ነኝ” አላቸው። ግን ደገመቱ። “ነብር ነህ” አሉት አሁንም። ተቃወመ። በትህትና “እንደናንተው ነኝ” አላቸው። ቀስ እያለ ግን እርሱም ተቃውሞውን ቀነሰ። በመጨረሻ ነብር ሳልሆን አልቀርም ብሎ መጠራጠር ጀመር። በመጨረሻ ጭራሽ ነብር ነህ ካላሉት መግደል ጀመረ። ከዛ ነብር ሆኖ ፈጃቸው። ኢትዮጵያ ትቅደም ያለምንም ደም ብሎ የተጀመረ አብዮት፣ በአንዱ ሰው ጄኔራል አማን አንዶም መገደል ቀስ እያለ ስልሳዎችን ፈጀ። ከዛ ስልሳ ሺ ሕዝብ ፈጀ። አብይ አህመድም ዛሬ ላይ ለመድረስ የጥቃቅን ሕግን ተከትሏል።



ራሳችሁን በመጥፎ ባህሪ እና በማትፈልጉት አስተሳሰብ ውስጥ ካገኛችሁት፣ የጥቃቅን ሕግን ፍልስፍና ተከተሉ። ችላ ያላችሁት ደካማ ወይም መጥፎ ባህሪ ካላችሁ ፥ ነገ የሞት አፋፍ ላይ ራሳችሁን ከማግኘታችሁ በፊት ዛሬ ንቁ።



ብዙ ትዳሮች ፍጹም በሆነ ፍቅር ይጀምራሉ። ልነጠፍልሽ ያልተባባሉ፣ በሕልምም በቁምም ያልተነፋፈቁ ፍቅረኛሞችን ማግኘት ከባድ ነው። ከዛ ከዓመታት በኋላ ወደ ዛ ትዳር ተመለሱ። የጥቃቅን ሕግ ወይ ፍቺ ላይ አድርሷቸዋል ወይም ፍቅር የሞተበት ቤት አስታቅፎአቸዋል። መቼ ነው ግን እንደዚህ መሆን የጀመሩት? አንድ ቀን!!! ያ ችላ ያሏት አለመግባባት፣ በቶሎ ያልፈቱት ልዩነት፣ ያዳፈኑት እና ከውይይት አርቀው የቀበሩት ያ አጀንዳ ነው የጥቃቅን ሕግን ተከትሎ የትዳራቸው ካንሰር ወደ መሆን ያደገው።



ወይናችሁ እንዲያብብ የምትፈልጉ ሰዎች ፥ ጥቃቅን ነገር ማድረግ ጀምሩ። ወይናችሁ ያበበም ሰዎች ወይናችሁ እንዳይጠፋ ጥቃቅን ነገሮችን በቶሎ ፈልጋችሁ ፥ እነሱን ነቅላችሁ አሶግዱ። ትልልቁን ነገር ችላ ብትሉት ይሻላል፤ ጥቃቅኑን ችላ ከምትሉ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 26
  • 3 min read

ree


የአዕምሮ ጅምላስቲክ ሕጻናት ጋር የተለመደ ነው። ምንም ነገር ያስባሉ። ምንም ነገር ለመሆን ፈቃደኛ ናቸው። ምንም ነገር ከመጣላቸው ይጠይቃሉ። እንደ ወፍ ለመብረር፣ እንደ ጉንዳን ለመዳህ፣ እንደ ጉዑዝ ነገር ለመድረቅ ፈቃደኛ ናቸው። ማሰሪያ የሌለው የሀሳብ ዋና ውስጥ ራሳቸውን ያስገባሉ።



አዋቂዎች ጋር ይሄ የተለመደ አይደለም። እንሸማቀቃለን። ትላንት የተናገርነውን ላለመቃረን ዛሬ ስህተት መድገም ይቀለናል። ብዙ ልጓሞች አሉብን። እንዲህ ሆኜ እንዴት እንደዚህ ሆናለሁ ብለን ራሳችንን ከፈጠራ እንገድባለን።



በዚህ ሳምንት ከአንድ ወዳጄ ጋር ስናወራ፤ እንዲህ ተባባልን። ብዙ አፍሪካኖች ወደ አሜሪካ መምጣት ይፈልጋሉ። ምንአልባትም በአንዳንድ ሀገሮች ሁሉም ሰዎች ከዛ ተነስተው ኢዚህ መግባት ይሻሉ። ለምሳሌ ይሄ ሀሳብ መጣልን። አሜሪካኖች እና አውሮፓኖች ለሁሉም አፍሪካኖች “እሺ ወደ ሀገራችን መምጣት ትፈልጋላችሁ። ሁላችሁም ኑ። እንደውም እናንተ የኛን ሀገር ውሰዱ። አሁን እንዳለው። ምንም ነገር ሳንቀንስ እንስጣችሁ። እናንተም የናንተን አፍሪካ ስጡን። ማለትም አሁን ባለንበት ሁኔታ ሙሉ ለሙሉ ቦታ እንቀያየር።”



ይሄ አይሆንም። ግን ቢሆን ምን የሚመስል ይመስላችዋል? በእኔ ግምት አሜሪካውያን እና አውሮፓውያን አፍሪካን ልክ ለቀው እንደሄዱበት ሀገራት በጥቂት ዓመታት ውስጥ ያደርጉታል። በተቃራኒው አፍሪካውያን አሜሪካንን እና አውሮፓን ያወድሙታል። የመጡበት አፍሪካን ያስመስሉታል።



የብዙ ሰው ግምት ይሄ የሚሆን ይመስለኛል። ለምን እንደዚህ አሰብኩኝ? ምክንያቱም አፍሪካ በዓየር ጸባይ እና በመልካ ምድር ምቹነት ከብዙ የአውሮፓ ሀገራት እና የአሜሪካ ስቴቶች የተሻለች ነች። ግን በዛ ምድር የምንኖር ሰዎች አመለካከታችን፣ ባህላችን እና የትምህርት ደረጃችን በጣም ዝቅ ያለ ነው። ሰጥቶ መቀበል የሚባለው ባህል፣ ስትራቴጂክ ሆኖ ማሰብ፣ የፖለቲካ ባህላችን እና መሰል ለሰው ልጆች በሰላም እና በብልጽግና የመኖር ዋስትና የሆኑ ከአዕምሮ የሚነሱ ሀብቶች ላይ በጣም ዝቀተኛ ነን።



ይሄ ለምን እንደሆነ በርግጠኝነት እኔ መናገር አልችልም። ብዙ ጥናት የሚሻው ይመስለኛል። የማውቀው አንድ ነገር ጥቁሮች ዝቅተኛ IQ ስላለን እንዳልሆነ ነው። ምክንያቱም በአውሮፓ እና አሜሪካ መጥተን እንደ ነጮች በእነሱ ዘርፍ ጥሩ የሆኑ ብዙ ስላሉ። በተለይ ጥሩ ትምህርት ገና በልጅነታቸው ያገኙ ሰዎች በብቃት ደረጃ ምንም አይተናነሱም።



ይሄ ዓይነት የሀሳብ ጨዋታ የሚጠቁመን ብዙ ነገሮች አሉ። አንደኛው የጎደሉንን ነገሮች ቆም ብለን እንድናስብ እና ችግሮቻችንን በተለየ መነጽር እንድናይ ያደርገናል።



ለምሳሌ በአሜሪካ ውስጥ ሁለት በጣም ሀብታም ስቴቶች አሉ። ኒው ዮርክ እና ካሊፎርኒያ። በአሜሪካ ውስጥ ሁለት በጣም ቅይጥ (diverse) የሆኑ እና ከነጩ ይልቅ ሌላው ማህበረሰብ በቁጥር የሚበልጥበት ስቴቶች አሉ። ኒው ዮርክ እና ካሊፎርኒያ። በደቡቡ የአሜሪካ ስቴቶች ውስጥ በጣም ሀብታሙ ከተማ አትላንታ ነው። በጣም ቅይጡ (diverse) ከተማም አትላንታ ነው። የአትላንታ ሀብት ብቻ በደቡቡ ካሉት ስቴቶች ሁሉ ይበልጣል። ደቡቡ እንደ ሚሲሲፒ፣ አላባማ፣ ሚዙሪ፣ አርካንሳ፣ ሉዊዚያና የመሰሉ ስቴቶች ከ90% በላይ ነጭ ሲሆን፤ እጅግ ደሃ ስቴቶች ናቸው።



ከዚህ ምን እንማራለን?



ለምሳሌ ወደ ሀገራችን እንሂድ። ሐዋሳ የዛሬ አስር ዓመት ኢትዮጵያ ውስጥ በፍጥነት እያደጉ ከነበሩ ከተሞች አንዷ ነበረች። ብዙ ሀብታሞች መፈጠር እና ሆቴሎች፣ ንግዶች መስፋፋት ጀመሩ። የመሬት ዋጋ ሰማይ መንካት ጀመረ። ሐዋሳ የዛሬ አስር ዓመት የነበራት ቅይጥነት አስገራሚ ነበር። የመንግስት መስሪያ ቤቶች ያሉ የስልጣን ቦታዋች በብዙ ብሔሮች የተያዙ ነበሩ። አንድ ዓይነት ነገር የለም። ማንም ቤቱ የሚመስለው ከተማ ሐዋሳ ነበር።



ከዛ ምን ሆነ? የክልል ጥያቄን ያነሱት ሰዎች ብዙ ስህተት ሰሩ። የክልል ጥያቄን መጠየቃቸው አይመስለኝም ስህተቱ። ይልቁንስ የከተማዋን የእድገት ምስጢር ፈጽሞ አለመረዳታቸው ነበር። ዛሬ የመሬት ዋጋ ወድቋል። ማውቃቸው ትልልቅ ባለሀብቶች ሁሉም ለቀው አዲስ አበባ ገብተዋል። ለመመለስም ፈጽሞ አያስቡም። ያሉትም መውጣት ይሻሉ። ለምን? መልሱ ግልጽ ይመስለኛል።



ኦሃዮ፣ ስፕሪንግ ፊልድ የዛሬ ስምንት እና ሰባት ዓመት የጎስት ከተማ እየመሰለ ነበር። የከተማው ባቡር ቆመ። ባዶ የሆኑ ቤቶችን መመልከት የተለመደ ሆነ። ፋብሪካዎች ተዘጉ። ከዛ ዲሞክራት ሲመጡ ከተማዋን ለማነሳሳት ከሄቲ የመጡ ስደተኞችን በገፍ ወደ ስፕሪግ ፊልድ ወሰዷቸው። ከተማዋ መነሳሳት ጀመረች። የከተማው ባቡር መንቀሳቀስ ጀመረ። የቤቶች ዋጋ ከፍ ማለት ጀመረ። ለምን? መልሱ ግልጹ ነበር። ከተማዋ በአዲስ መጤዎች ጉልበት እና የፈጠራ አቅም መነሳሳት መጀመሯ ነበር።



አንድ ብልህ መሪ ምንድነው የሚያደርገው? ከዚህ በፊት በሌሎች ቦታዋች የሰሩ ሙከራዎችን በርሱም ግዛት መሞከር ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ የትም ቦታ ብትሔዱ ከነባሩ ሕዝብ በላይ ለዛ አከባቢ መጤ የሆነው ማህበረሰብ ንግድ ውስጥ አለ። የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን የካቢኔ ስብሰባዎች የጻፈው አምባሳደር ዘውዴ ረታ የኢትዮጵያን የንግድ አውታሮች ተቆጣጥረው ይዘውት ስለነበሩ አረቦች ጽፏል። መጤዎች ነበሩ ኢትዮጵያ ውስጥ በንግድ የተሳካላቸው። የአረቦች መብዛት ያስፈራው የንጉሱ ካቢኔ ሀሳብ ዘየደ። ይሄን ሀሳብ ለንግድ ሚኒስትሩ መኮንን ሀብተወልድ የነገረው አንድ የተማረ ጉራጌ ነበር። ጉራጌዎች የንግድ ክህሎት አላቸው። አረቦችን ሊተኩ የሚችሉት እነርሱ ናቸው። ስለዚህ አረቦችን ገፍትረን ከምናሶጣ ጉራጌዎችን አምጥተን ብድር እንስጣቸው። ከዛ ጎን ለጎን ሱቅ ይክፈቱ። በዓመቱ አረቦቹ ሲከስሩ በራሳቸው ለቀው ይወጣሉ አለው። የሀብተወልድ ልጅ ይሄን ሀሳብ ተቀበለ። መንግስት ጉራጌዎችን በገፍ አምጥቶ መርካቶ ላይ በማስፈር ብድር በመስጠት ንግድ እንዲሰሩ አደረገ። በዓመቱ አረቦች ከስረው በራሳቸው ጊዜ ለቀው ወጡ። መርካቶ ከአፍሪካ ትልቁ የገበያ ማዕከል ሆነ።



ስለሀገሩ ትልቅነት የሚያስብ ሰው በሀሳብ ይጫወታል። የሰዎችን ዝቅተኛ የዘረኝነት እና የጎሳነት ስሜት በመጫር ሳይሆን ከእውነት ጋር ማህበረሰብ እንዲጋፈጥ ያደርጋል። መጽሐፉ ቅዱስ የስደት ታሪክ የተከተበበት መጽሐፍ ነው። ሰዎች ከእናት አባታቸው ተለይተው ታላቅ የሆኑበትን ታሪክ የምናነብበት መጽሐፍ ነው። በሀገራችንም ከቀዬ ውጣ ከምንል ይልቅ ወደ ቀያችን እና መንደራችን አዳዲስ ማህበረሰቦች እንዲመጡ፣ በመንግስትም ሆነ በግሉ ዘርፉ ላይ ገብተው እንዲወከሉ ብናደርግ ተዓምር መስራት እንችል ነበር።



ከኢትዮጵያ ብቻ አይደለም፣ ከጎረቤት ሀገራት ጭምር እየመጡ በነጻነት እንደ ዜጋው ንግድ ውስጥ እንዲገቡ፣ የራሳቸውን ባህል እና ማንነት እንዲያጎለብቱ ብንፈቅድላቸው ተዓምራዊ ለውጥ ማየት እንችል ነበር። ከቦታ ቦታ ሰዎች እንደልብ ተዟዝረው መስራት እና ሀብት ማፍራት ቢፈቀድላቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ከተሞች ተዓምር መስራት ይችላሉ።



ዛሬ በስደተኞች ታላቅ የሆነችው ሀገረ አሜሪካ የታላቅነቷ መሠረት የሆነው ስደት ላይ በሯን እየቆለፈች ነው። የዛሬ ዓመት የነበረው የኢኮኖሚ መነቃቃት ዛሬ የለም። በሁሉም ከተሞች ድብታ እየሰፈነ ነው። ኢኮኖሚው በጣም ተቀዛቅዟል። እስከዛሬ የነበረው የአሜሪካ ብልሃት ነገሮች እንዲህ ሲከፉ መንገዳቸውን (course) ቶሎ ማቃናት ይችላሉ። አሁንም ሳይረፍድ ዘረኝነት ያነሳሳው እብደት እና ዕውረነት ይሰክናል የሚል እምነት አለኝ።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Oct 19
  • 3 min read
ree

አሸናፊው ስብዕና ነው ደግነት። በዚህ ምድር ላይ ሰውን ወደ ሕይወታችሁ ለማስጠጋት አንድ መለኪያ፣ አንድ ሜቲሪክ፣ አንድ ሚዛን ብቻ ቢኖራችሁ። ያ ደግነት መሆን አለበት። ጥሩ ነገሩ ብዙ መለኪያዎች አሉን። ግን ደግነት የጎደለው ሰው ሁሉ ነገር ቢኖረው እንኳ በፍጹም ወደ ሕይወታችን መግባት የለበትም። ደግነት የሰው ልጅ የመልካምነቱ ውሃ ልክ ነው። ምንም እውቀት ቢኖረው ሰው ደግ ካልሆነ በዚህ ዓለም ላይ እዳ እንጂ ትሩፋት አይደለም። ምንም ገንዘብ እና ጠቃሚ ምግባሮች ቢኖሩት ደግነት የሌለው ሰው ይሄን ዓለም የመረዳት አቅም የለውም።

 

ደግነት ሕጻን ሲያይ ይራራል። ደግነት ሰው ሲያይ ያ ሰው ምስኪን እናት እንዳለችው፣ እህት ና ወንድም እንዳሉት፣ ልጆች ሊኖሩት እንደሚችሉ ያስባል። ደግነት የሰው ልጅን የዓለም መጋረጃ ከፍቶ በዛ ሰው ውስጥ ያለውን ውጣ ውረድ ለመመልከት ይችላል። ደግነት የሰውን የውጣ ውረድ ታሪክ ሲሰማ እንባውን ያፈሳል። ሕይወት በሞት አላዝር ፊት እንባውን እንዳፈሰሰ።

 

ሁላችሁን እስቲ ወደ ጋዛ ልውሰዳችሁ። የዋህ እና ደግ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእነዛ ሕጻናት መካከል በእግሩ ቢራመድ ምን የሚል ይመስላችዋል? እናንተ ሙስሊሞች፣ እናንተ የነገ ሀማሶች፣ እናንተ የእፉኝት ልጆች የሚል ወይስ እነዛ ያለ አባት፣ እናት፣ ወንድም እና ቤት ከቀሩ ልጆች ጋር የሚያነባ ይመስላችዋል? ደግነት የሚያደርገው ያቺን ሳምራዊት ሴት ያሳያትን ደግነት ነው ለእነዚህ የጋዛ ሕጻናት የሚያሳየው። አብሮ ቁጭ ብሎ ያነባል። አብሮ መከራቸውን ይጋራል።

 

ደግነት ፍርሃቱ እንዲያሸንፈው አይፈቅድም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሥጋ ፍርሃት ራሱን አሳልፎ የሰጠ ቢሆን ምን ሊሆን እንደሚችል አስቡት። በቀራጩ ቤት ምሳ አይበላም። በዛች በዘማዊት ሽቱ ለመዳሰስ እና ለመታጠብ አይፈቅድም ነበር። ምክንያቱም ሰው ምን ይለኛል፣ ባህሉ እና የተዘረጋው መዋቅር ምን ይፈርድብኛል ብሎ ከፈሪሳውያን ጋር ይቆም ነበር።

 

ደግነት ግን ድንጋይ በእጃቸው ጨብጠው አንዲት ምስኪን ሴትን ለመውገር በተሰበሰቡ ሰዎች ፊት አጎነበሰ። ያቺን ሴት ሊያድን መሬቱን ፋቀ። ደግነት ድንጋይ (መሳሪያ) ከያዙ ሰዎች ጋር አይተባበረም። ደግነት የክፋትን ሠራዊት ይበትናል እንጂ። ዘማዊቷን ለማዳን ደግነት ምንም አይሸማቀቅም። የሌሎች ክፋት ለእነርሱ በችግራቸው ጊዜ ለመድረስ የእርሱን ርህራሔ አያጎድለውም። ልቤ ሆይ ደግነትን በየቀኑ ተማር።

 

ደግነት ፊት ለፊቱ ላለው የሰው ልጅ የውጣ ውረድ ሕይወት ቦታ ይሰጣል። ከፍርሃት ጋር አይቆምም። ቡዙዎቻችን በሚገባ ፍቅር እና የሰው ልጅ ደግነት መካከል ያደግን አይደለንም። ዛሬም በሕግ ማስከበር ሰበብ ከሀገራችን ኢትዮጵያ እስከ አለንበት የስደት ቦታ ድረስ የምናየው የክፋትን ጥግ ነው።


በቤተመንግስት ውስጥ ሆኖ ስለ አትክልቱ እና በእግሩ ስለሚራመድበት የውበት ኮሊደር የሚጨነቅ መሪ እንጂ በእርሱ ወታደሮች እና ድሮኖች ስለሚናጋው የቤተሰብ ሕይወት እምብዛም የማይገደው የጭካኔ መሪን ነው የምናየው። ግን ይሄው መሪ ጩጬ ምስኪን ወንድ ልጅ አለው። ወንድ ልጁን ይወዳል። ሌሎችም እንደርሱ የሚወዱት ልጆቻቸው እየተገደሉባቸው እንደሆነ ግን ማሰብ አይፈቅድም። ልቡን ለደግነት አልከፈተውም። ነጻ አውጪ ነን ያሉትም ነጻ እናወጣዋለን ያሉትን ሕዝብ በግፍ ቀንበር ይገርፉታል።

 

ተሰደን በመጣንበትም ሀገር ማስክ ያጠለቁ ሰዎች የጭካኔ እና የዘረኝነት ክፋታቸውን በኢሚግሬሽን ሰበብ በምስኪን ሰዎች ላይ ያዘንቡበታል።



ዛሬ ያለን የነገ አፈሮች ነን። ነገ በታሪክ መጻፍ ውስጥ እንኳ የማንገባ ኢምንቶች ነን። ይሄ እድሜያችን በሚገርም ፍጥነት ይበራል። ከዛም ያልቃል። በሞት ወደ ምንምነት እንቀየራለን። እንግዲህ ለዚህ ሕይወት ነው ሰው ጎድተን፣ በሌሎች ላይ ጥቅም ይዘን፣ ተቆሳስለን የምናልፈው። ከልጅነት ጀምሮ በጭቆና ያደግንበትን በሌሎች ላይ ድጋሚ ያን ክፋት እና ጭቆና አንጸባርቀን እናልፋለን። የተጎዳ እና ያልታከመ ልብ ፥ ሌሎችንም ጎድቶ እና አቁስሎ ያልፋል።

 

ደግነት የሌለው ሰው ሌላው ሁልጊዜ ያስፈራዋል። ደግነት የጎደለው ሕይወት ሌላው ጥቅም እንደሚይዝበት፣ የእርሱ. የሆነውን ነገር ሊነጥቀው እንደሚፈልግ ነው ሁልጊዜ የሚያስበው። ደግነት አልቦ ሰው በቁስ ማጠራቀም ሕይወቱን ያፍናታል። ከሰው ጋር ነጻ ሆኖ መደሰት አይችልም። በትንንሽ ነገሮች መሳቅ አይችልም። ነጻ ያልሆነ፣ ያልተላቀቀ፣ የሚከብድ ስብዕና ነው ያለው። ሁልጊዜ ያስመስላል። ከፍ ያለ ቦታ ላይ ሲሆን ደግሞ ይጨቁናል። እድሉን ሲያገኝ ያሰቃያል።

 

በየቀኑ በጉዞአችን፣ በየቀኑ በሥራችን፣ በየቀኑ በመንገዳችን የተጎዱ ሰዎች ይገጥሙናል። ደግነትን ሆን ብለን ካልተለማመድን ፍርሃት ነው ባህሪያችንን የሚቆጣጠረው። ያን ጊዜ እነዚህን ሰዎች መልሰን እንጎዳለን። ለዚህ ነው የበራችን መቀነት ላይ፣ የየቀን መንገዳንች ላይ “ልቤ ሆይ ደግ ሁን!!!” ማለት ያለብን። ቢያንስ ባንደበታችን ሰው ላለመጉዳት መጠንቀቅ ይኖርብናል። ክፉ ከመናገር እና ሰውን ከማቁሰል ራሳችንን መገደብ ይኖርብናል። “ልቤ ሆይ ደግ ሁን” ልንለው ይገባል። ለሰዎች ብለን ብቻ እንዳይመስላችሁ። ደግነት የራሳችንን የልጅነት እና የአዋቂነት የመንፈስ ትሮማ (ስቃይ) እና የውስጥ ቁስል መፈወሻ ብቸኛው መድኃኒት ስለሆነም ጭምር እንጂ። የደግነት እንባ የውስጥ ቁስል ፈዋሽ ፋፋቴ ነው። ከመፍረድ ያዘገያል ደግነት። የማናውቀውን የሰው ልጅ ሕይወት መጋረጃ ከፍቶ ያሳየናል።


ለጊዜያዊው ለዚህ ሕይወት ውበቱ እና ክብሩ ደግነት ነው። ደግ የሆነ ሰው ትንሿን ዘመኑን ያከብራታል።


በሞቱ አልጋ ላይ የመጨረሻ ዓይኖቹን ሲጨፍን ለዚህ ነበር ብሎ አይዘጋውም። ይሄ ሕይወት አጭር እንደነበረ ገና ድሮ እንደገባው ግን ደግሞ የሌሎችን ቁስል ፈውሶበት ያሳለፈው መሆኑን በማየት እየሳቀ ዓይኖቹን ይጨፍናል።

 

ልቤ ሆይ ደግ ሁን።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page