top of page
Search
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Jun 1
  • 3 min read




በሕይወቴ ታደልኩት ከምለው ነገር በምርጥ ጓደኞች መከበቤን ነው። እኔን ለማድመጥ ከማይሰንፉ፣ ለነቀፋ ሳይሆን ለማገዝ በፈቀዱ እና ሙላት እንዲሰማኝ በሚያደርጉ ጓደኞች ነው ተከብቤ የኖርኩት። እንዲህ የሚባል አባባል አለ። አንተ የአምስት በዙሪያ ያሉ ሰዎች አቭሬጅ ነህ። የሰው ልጅ መቀየር ከፈለገ ማድረግ ያለበት ጓደኞቹን መለወጥ ነው። ሁልጊዜ የጓደኞቹ አቭሬጅ ስለሚሆን። በዓለም ላይ የድንቅ ለውጦች እና ተቋማት ውጤት የምርጥ ጓደኞች ጥምረት ነው። ዋረን በፌት እና ቻርሊ መንገር፣ ዳንኤል ኮነመን እና አሞጽ ትሮቪስኪ፣ ተፈሪ መኮንን እና ራስ ካሳ፣ መኮንን ሀብተወልድ እና ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ፣ መዝሙረኛው ዳዊት እና ዮናታን እና መሰል ጥምረቶችን ማንሳት ይቻላል። ከስኬታማ ሰው ጀርባ ጠንካራ ሚስት አለች የሚባለው እውነት ቢሆንም ሁልጊዜ ግን አይደለም። ሁልጊዜ እውነት የሆነው ከማንኛውም ስኬት በስተጀርባ ጠንካራ ጥምረቶች እና ወዳጅነቶች ያሉ መሆኑ ነው። ብዙ ስኬታማ ወንዶች ክፉ ሚስት ኖሯቸው ያውቃል። የትኛውም ስኬታማ ሰው ግን ምርጥ ጓደኛ የሌለው የለም።



ብዙዎቻችን ይሄን ምርጥ ጓደኛ ለመፈለግ እንኳትር ይሆናል። በሚገርም ሁኔታ ግን እኛ መልካም ሰው ሳንሆን ፈጽሞ እነዚህን ጥምረቶች ከመጀመሪያውም መፍጠር አንችልም። የምርጥ ጓደኛ አንዱ ብቃት ራሱን ከመጥፎ ሰዎች ማራቅ ነው። ስለዚህ እኛ ልበ ጠማማ እና መሰሪ ከሆንን እነዚህን አስገራሚ ጥምረቶች አናገኛቸውም። ለመልካም ጓደኝነት የሚያስፈልግ ዘር በውስጣችን አስቀድሞ ከሌለ ምርጥ ጓደኞችን ማፍራት አንችልም።



ምንድናቸው እነዚህ ዘሮች?



1) ጓደኛ እንዲሆኑ የምትመርጣቸው ሰዎች ከአንተ ጋር ሁልጊዜ በሀሳብ የሚስማሙ መሆን የለባቸውም። ያንተን blindspot (ግርዶሽ) የሚያሳዩ ሰዎች ነው የሚያስፈልጉ። በራሳቸው ቆመው ማሰብ የሚችሉ ሰዎች ካልሆኑ ጥሩ ጓደኞች አይሆኑህም። ለዚህ ደግሞ አንተ ውስጥ አንድ ዘር ያስፈልጋል። ትችትን በደስታ እና በሳቅ የምትቀበል፣ ፉገራን የምትችል እና ጓደኞችህ ካንተ ጋር ነጻ ሆነው ማውራት እንደሚችሉ የሚሰማቸው ሰው መሆን አለብህ። ካለዛ መስማት የምትወደውን የሚነግሩህ የገደል ማሚቱዎች እንጂ ጓደኛ አይኖርህም።



2) ጓደኛ እንዲሆኑ ለምትፈልጋቸው ሰዎች ስኬት ከልብ መጨነቅ መቻል። ይሄ በጣም ከባድ ነው። ቅናት የሰው ልጅ ጥንታዊ ማንነቱ ነው። ከልጅነት ጀምሮ በቅናትም ነው ተኮትኩተን ያደግነው። “ጌታ ሆይ እኔ ራሴን ከጠላቴ እጠብቃለሁ። አንተ ግን ከወዳጄ ጠብቀኝ” የሚባለው የቅናትን ኃያልነት ለመግለጽ ነው። የሚቀናብህ እና በቅናት የሚያጠቃ ደግሞ አጠገብህ ያለው ወዳጅህ ነው። ለዚህ ነው ጥሩ ጓደኛን ለማግኘት የቅናትን ሥሮች ከውስጣችን ነቃቅለን ማቃጠል ያለብን። እንዴት? ለጓደኛ ምክር ከመስጠታችሁ በፊት ራሳችሁን ጠይቁ። “ይሄን ምክር ለራሴ ቢሆን እሰጠዋለሁ? ይሄ ምክር የጓደኛዬን ስኬት በማሰብ የተሰጠ ወይስ የርሱ ስኬት ለእኔ በሆነ መጠን የስሜት ጉድለት ስለሚያመጣ የቀረበ ምክረ ሃሳብ ነው?



አንዱ የምንቀናው ያ ሰው ቢሳካለት እናጣዋለን፣ ከጎናችን አይሆንም ብለን ነው። ለዚህ ነው ከልብ የዛን ሰው ጥቅም ለማሰብ መለማመድ ያለብን።



በዚህ ምድር ምርጥ ጓደኛ የማግኛው ትልቁ ቁልፍ ለዛ ሰው ፍጹም የሆነ ስኬት እና ደስታን መመኘት ነው። ስኬታማ እንዲሆን ደግሞ መደገፍ። ነገር ግን በጎ የምንመኝለት ሰው ቅናተኛ ከሆነ ይሄ ባህሪያችን ብዙም ላይለውጠው ይችላል።



3) ክፉ ካደረገብን በላይ ክፉ እንዲሰማን ያደረገብን ሰውን እናስታውሳለን። በተቃራኒው መልካም ስሜት እንዲሰማን ያደረገንን ሰው እንወደዋለን። ጓደኛ እንዲሆኑን የምንፈልጋቸው ሰዎች በጎ ስሜት ስለራሳቸው እንዲያድርባቸው ማድረግ አለብን። እነርሱን ዝቅ የሚያደርግ እና ጎዶሎ እንደሆኑ እንዲሰማቸው ማድረግ ምርጥ ጓደኛን የማጫ ዋነኛው መንገድ ነው። በጎ ስሜት እንዲሰማቸው ወዳጅ እንዲሆኑን ለምንፈልጋቸው ሰዎች እናድርግ። ስለ ስሜታቸው እንጨነቅ። ሰው የሚያስብ እንስሳ አይደለም። የሚሰማው እንስሳ ግን ለማሰብ የሚጥር ነው። ስለ ሌሎች ስሜት መጨነቅ ሌሎችን የማትረፊያ መጀመሪያ ነው።



4) ዓላማችሁ የሚያስቡ ወዳጆች ማግኘት ነው። ስለዚህ ኮንቨርሴሽን (conversation) የምትወዱ ካልሆናችሁ ጥሩ ጓደኞችን ማግኘት ከባድ ነው። በርግጥ በቡድን ውስጥ ማውራት ምቾት የሚሰጠው (extrovert) እንዳለ ሁሉ የራሱ ምቹ ሁኔታ (comfort zone) እስኪፈጠር የሚጠብቅ (introvert) ተፈጥሮ ያለው ሰውም አለ። የማውራት ተፈጥሮአችን ይለያይ እንጂ ሰው የሚያወራ እና ሀሳብ የሚለዋወጥ ፍጥረት ነው። የምትፈልጉት ወዳጅ ሀሳብ ያለው መሆን አለበት። ሀሳብ ማፈልቅ የሚችል እና የሚያስብ። ከእናንተ ስሜት ጋር የሚነጉድ ሳይሆን ያላያችሁትን የሚያሳያችሁ መሆን አለበት። ለዚህ ደግሞ ቁልፉ እናንተ ናችሁ።


እነዚህን አራት ነጥቦች በጥልቀት ብታዮቸው ካለ ባላንስ እርስ በርስ ይጋጫሉ። ጥበብ ማለት ሊጋጩ የሚችሉ ነገር መቀመሚያ ነው። ብዙ ወለፈንዲዎችን (paradox) አቻችሉ እና አስማምቶ የሚሄድ ሰው ነው ጥበበኛ የምንለው።



ጥሩ ነገሮችን ሁሉ ለማግኘት ከባድ ናቸው። ሕይወት ደግሞ የሚነግረን መልካም ነገሮችን ለመሳብ ማግኔቱ እኛ ጋር እንደሆነ ነው። መልካም ዘር መልካም መሬትን ይፈልጋል። መልካም መሬት ያለ ጥሩ ዘር ዋጋ የለውም። ሁለቱ ሲጣመሩ ነው አስገራሚ ውጤት የምናየው። መልካም መሬት ካልሆንን የዘሩ ጥሩነት ምንም ጥቅም የለውም። መልካም መሬት ካላገኘን ምርጥ ዘር ቢኖረን ጥቅሙ ምንም ነው። ነጮች “it takes two to tango” ይላሉ። ጓደኝነት የጋራ ጉዞ ነው።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • May 18
  • 2 min read




የሰንበት ዕይታ ዓላማ ሳምንታዊ ግምገማ ነው። “ምንድነው በዚህ ሳምንት የተማርኩት?” የሚል ግምገማ። ረጋ ብሎ፣ ዝግ ብሎ፣ ቆም ብሎ፣ ወደ ኋላ በማየት ስለወደፊቱ የማሰብ አቅምን የማግኘት የሪፍሌክሽን ማዕድ ነው። ዝም ብሎ ላለመሮጥ የመወሰን የመንገድ ጉብታ ነው። ይሄ ለጥ ያለ አስፓልት ላይ ሳምንታዊ እብጠት ነው። ፍሬን ተይዞ ፥ “ምን ያህል መጣው እስካሁን ፥ ቀሪውንስ እንዴት ልጓዝ?” የምልበት ማቀዝቀዧዬ ነው።



ፍጹሙ ሰው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሳይቀር ራቅ ብሎ ወደ ተራራ በመውጣት፣ ለአንድ አፍታ ከሰው መንጋ ፥ ከተከታዮች አድናቆት እና ክብር ራቅ ብሎ ፥ እርሱ እና አባቱ ብቻ ወደ ሚነጋገሩበት ርጋታ እና ዝምታ ይሰወር ነበር።



“ምንድነው እያደረኩኝ ያለውት? የት ነው ይሄ የሚያደርሰኝ? ምን አስቤ ነው እዚህ ድረስ የመጣውት? ከዚህስ በኋላ እንዴት ነው ልጓዝ እያሰብኩኝ ያለውት?” የምንልበት የጸጥታ በዓት ያስፈልገናል።



ከተርዕዮ ሱስ ራቅ ብለን ፥ ወደ ውስጥ የምንመለከትበት የርጋታ ጉብታ ላይ መውጣት ያሻል። ለእኔ ያ መጻፍ ነው። ከራሴ ጋር የማወራበት፣ ማደርገውን ነገር በምክንያት የምሞግትበት፣ ከመውቀጥ፣ ከመደለቅ፣ ከመሰልጠቅ ሩቅ ወደ ሆነው የመመሰጥ እና የማሰብ ሀገር የምሄድበት ነው የሰንበት ዕይታ።



“ምንድነው የተማርኩት?” የምልበት። ብሩስ ሊፕተን የእንጀራ አባቱን ሞት ሲገልጽ እንዲህ ይላል። “የእንጀራ አባቴ ለአንድ ሳምንት ኮማ ውስጥ ገብቶ ቆይቶ በመጨረሻ ትንፋሹ ሰዓት ብድግ ብሎ ተነሳ። ከየት አመጣው በሚያስብል በታላቅ አቅም ነበር ብድግ ያለው። ‘በሕይወቴ ሁሉ አንድ ቀን ደስ ብሎኝ አያውቅም’ የሚለውን ቃል ተናግሮ እስከወዲያኛው ጸጥ አለ። ከዛ ቀን ጀምሮ ስሞት እንዲህ ላለማለት ወሰንኩኝ” ይላል ብሩስ ሊፕተን።



ብዙ ሰው በሕይወት ዘግይቶ ይነቃ እና “ለዚህ ነበር!”ይላል። “ከቤተሰቦቼ ጋር ተጋጭቼ የኖርኩት ለዚህ ነበር?” ይላል። “ያንን ሁሉ ሰው ያሳዘንኩት ለዚህ ነበር?” ይላል። “በማይረባውም በሚረባውም ስባዝን እና ስጨነቅ የኖርኩት ለዚህ ነበር?” ይላል። በእስትንፋሱ መጨረሻ ሰዓታት ላይ ይነቃ እና “ለዚህ ነበር!” ይላል።



ከዛ የሚጠብቀን የመንገድ ጉብታ ፥ አስገድዶን ፍሬን የሚያሲዘን እና ቆም ብለን በጥልቀት እንድናስብ የሚያደርገን የማሰላሰያ አዋሻዊ የርጋታ የዝምታ ጉብታ ያስፈልገናል።



እንደ ማርከስ አርሊየስ እያሰብ ከእውነታ ጋር የምንጋፈጥበት ጉብታ። በቅርብ ሁሉን ነገር ትረሳለህ። በቅርብ በሁሉ ትረሳለህ። በዚህ እውነታ ውስጥ ነው ያለነው። በቅርብ የግርግዳ ፎቶ ትሆናለህ። ከዛም ከምንም ነገር ላይ ትወርዳለህ። በዚህ ሳይክል ውስጥ ነው ያለኸው። ስለዚህ ምን እያደረክ ነው?



እየተካሰስክ ነው ወይስ ቢያንስ የአንድ ሰውን ሕይወት በጎ ለማድረግ ጥረት እያደረክ ነው? በዚህ ክፋት በሞላበት ዓለም ፊት ውበትን የማየት አቅም አጥተን ይሆናል። ስለዚህ እንቁም። ጉድለት በበዛበት ሕይወት ውስጥ ያለንን ብዙ ነገሮች ረስተን ይሆናል። ስለዚህ ፍሬን እንያዝ። “ምንድነው ግን የተማርኩት?” እንበል። “ምንድነው በሕይወቴ መድገም የማልፈልገው እና ብደግመው የማፍርበት ነገር? ምንድነው በሕይወቴ እየሰራ ያለ ጥሩ ነገር እና አብዝቼ መቀጠል ያለብኝ? ማቋረጥ የምሻው እና ያላቆምኩት ነገር ምንድነው?” እንበል።



በዚህ ሕይወት በጣም የምፈልገው ነገር ምንድነው? ያን ባገኝ ምንድነው የሚሆነው? ምን ላደርግበት ነው ያን ነገር የምፈልገው? ሳላገኘውስ ይሄ ሕይወት ቢያበቃ እንዴት ነው ሕይወቴን መኖር ያለብኝ?



መቀበል የቸገረኝ ነገር ምንድነው? ለምንድነው የከበደኝ?



ምንድናቸው ዓይኖቼ የታወሩባቸው ነገሮች? ማየት የተሳኑኝ?



ዛሬ ትላንት የጓጓህለት ወይም የፈራኸው ነገ ነው። ትላንት የተደሰትክበት ወይም ያዘንክበት ዛሬ ነበር። ነገም ዛሬ ይሆናል። ከዛ ትላንት። ለዚህ ነው ዘይትህን ቆም ብለህ ለመፈተሽ ወይም ለመቀየር መወሰን ያለብህ። ካለዛ አንድ ቀን ኢንጅነህ ተበላሽቶ ትነቃለህ። ኢንጅንህ እስከወዲያኛው ላለመስራት ሆኖ ትደርሳለህ። ብትረግጠው፣ ብትገፋው፣ ብታስገፋው - Too Late! ይልሃል።





 
 
 




በሥራዬ ምክንያት በአሜሪካ ዙሪያ ያሉ ብዙ የኢትዮጵያ ቢዝነሶችን በሕግ ዙሪያ የማማከር ዕድሉን አግኝቻለሁ። ብዙዎቹንም የሕግ ጉዳይ እና ችግር ገጥሞአቸው ረድቻቸዋለሁ። ወይም ከሚረዷቸው ሰዎች ጋር አገናኝቻለሁ። የዚህ ጹሁፍ ዓላማ ግን እርሱ አይደለም። የማገኛቸው ብዙ የኢትዮጵያ ቢዝነስ ሰዎች የሚነግሩኝ ነገር ፥ ከሚረዷቸው ኢትዮጵያኖች ባልተናነሰ ብዙ ምቀኛ እና ተንኮለኛ ኢትዮጵያዊ አለባቸው። የሆነ ችግር ሲገጥማቸው ምሳር የሚያበዙባቸው እንጂ የሚበዙት፤ አዲስ ቢዝነስ ሲከፍቱ መደገፍ ወይም ማገዝ እና እንዳይወድቁ የሚረባረቡ ኢትዮጵያኖች አይደለም በብዛት ያሉት።



በሚገርማችሁ አሜሪካ ውስጥ አንድ የኢትዮጵያ ሞል አታገኙም። በዋሽንግተን ዲሲ እና አከባቢው (ቨርጂኒያ እና ሲልቨር ስፕሪንግን ጨምሮ) እስከ 250 ሺ ኢትዮጵያዊ አለ። ሚኒሶታ ትልቁ የሶማሌ ኮሚኒቲ ያለበት ስቴት ነው። ቁጥራቸው ግን ወደ 60 ሺ ብቻ ነው። ይሄ ከኢትዮጵያኖች ጋር ሲነጻጸር በብዙ እጥፍ ያንሳል። ነገር ግን ከአንድም ሁለት ትልልቅ የሶማሌ ሞል በሚኒሶታ አለ። የዚህን ምስጢር ብዙ የሶማሌ ደንበኞቼን ስጠይቃቸው የሚሉኝ “ሶማሌ ከሌላ ሶማሌ ሱቅ ይገዛል። ልብስ ከፈለገ የነጭ ሱቅ ሳይሆን የሚሄደው እዛው አጠገቡ ያለውን የሶማሌ ቢዝነስ ነው የሚደግፈው። ከዛው በመግዛት።” ይሄ በኢትዮጵያኖች ዘንድ እምብዛም አልተለመደም። ብዙ ኢትዮጵያኖች ወገናቸው ከስሮ ፥ ስለክስረቱ ማውራት ያስደስታቸዋል ፥ ያን ሰው ተሯርጠው ደግፈው እንዲሳካለት ከማድረግ ይልቅ።



ስለብዙ ነገር ሳስብ ፥ ወደ መሠረቱ ሄጄ ለመረዳት እሞክራለሁ። ስለ ኢትዮጵያኖችም ይሄ አስገራሚ ራስን የሚጎዳ ባህሪ ሳስብ ፥ ወደ መሠረቱ ሄጀ ለማሰብ ሞክሬያለሁ። ኢትዮጵያኖች የተለየን ሆነን አይደለም እንደዚህ አስገራሚ ባህሪ የምናሳየው። ማለት በጣም ጥልቅ የሆነ የምቀኝነት ባህል እና ባህሪ (ጠልፎ የመጣል ባህል) የኖረን ፥ እጅግ ኋላ ቀር የሆነ የአስተሳሰብ ተሸካሚ ማህበረሰብ ስለሆንን ነው።



ልክ የኢትዮጵያኖች ዓይነት በጣም ኋላ ቀር የምቀኝነት ባህል እጅግ ደሃ የሆኑ ማህበረሰቦች ሁሉ አላቸው። ታላቁ የቲዎሎጂ ሊቅ ሲ ኤስ ሉዊስ “የሰይጣን ትልቁ ተልዕኮ ሰው እንስሳነቱን እንዲረሳ ማድረግ ነው” ይላል።



ሰዎች በትምህርት የጎደልን እና በስሜት የምንመራ ስንሆን እንስሳዊ ባህሪያችን ብቻ ነው የኛ አስተዳዳሪ የሚሆነው። ብዙ ሰው ቅናት እና ምቀኝነት የክፋት ውጤት ይመስለዋል። ይሄ ግን ደካማ ትንታኔ ነው። ቅናትም ሆነ ምቀኝነት እንስሶች ራሳቸውን ለመጠበቅ የሚያመነጩት የሆርሞን መጠበቂያዎች ናቸው። የምንፎካከረው ከኛ በጣም በቅርብ ርቀት ካለ ሰው ጋር ነው። ያ ሰው በሀብት ወይም በማናቸውም ነገሮች ሲበልጠን ፥ እንስሳዊ ባህሪያችን ዕድል (opportunity) አይደለም የሚታየው። ይልቁንስ መሸነፍ፣ ዝቅተኛ መሆን፣ በሌሎች ተፈላጊ አለመሆን እና ብቸኛ መሆን ነው የሚታየው። ስለዚህ ራሱን የሚከላከለው የሚበልጠውን በማጥፋት ነው። ምክንያቱም ሰው ፍጹም የሆነ ሚዛን (objective truth or standard) የለውም። የሚያስበው ሁሌ በአንጻራዊ ሁኔታ ነው። በምሳሌ ላስረዳ። የአሪዞናው ዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር ካልዲኒ አንድ የሰራው አስገራሚ ጥናት አለ። በዚህ ጥናት አምስት ሰዎችን በጣም ቀዝቃዝ የሆነ ክፍል ውስጥ አስገባቸው። ሌሎች አምስት ሰዎችን ደግሞ በጣም የጋለ ሙቀት ያለበት ክፍል ውስጥ ለተወሰነ ደቂቃ አስገባቸው። ከዛ ሁለቱንም ከየክፍላቸው አውጥቶ ወደ ሩም ቴምፕሬቸር (ዓየሩ ወደ ተስተካከል) ክፍል ውስጥ ከተታቸው። በጣም ቀዝቃዛ ከሆነ ክፍል ውስጥ ለመጡ ይሄ ክፍል ሲሞቃቸው፤ በጣም ሙቅ ከሆነ ክፍል ውስጥ ለመጡት ደግሞ ይሄ ክፍል ቀዘቀዛቸው። ይሄ የሚያሳየን የሰው ልጅ የተስተካከል ሚዛን (objective truth/scale) የሌለው መሆኑን ነው። ሁልጊዜ የሚያስበው በንጽጽር ሁኔታ ነው።



ኢለን መስክ በብዙ እጥፍ በሀብት እየበለጠን በርሱ ሳይሆን የምንቀናው፤ የምንቀናው በምናውቀው እና አብሮ አደግ በሆነ ጓደኛችን ነው። ምክንያቱም የዝቅተኛ ስሜት እና የመሸነፍ እና ያለመፈለግ ስሜት በውስጣችን የሚጭረው ያ የምናውቀው አብሮ አደግ ጓደኛችን ሲበልጠን ነው። ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ "ሰው ሀዘን የሚሰማው እንደሚያሸንፈው የሚያስበው ሰው ሲበልጠው ነው።" ይላል። ያ Primordial በሆነው እንስሳዊ ዓለም ውስጥ ፥ በአቻው የተበለጠ እንስሳ የመኖር ተስፋው እና በተቃራኒ ጾታ ተፈላጊነቱ እጅግ ዝቅ ስለሚል ፥ ራሱን በሌላ ዘር የመተካት አቅሙ ሳይቀር ነው የሚቀንሰው። ለምሳሌ ፒኮኮች ያላቸው ቀለማማ ጸጉር ምንም ጥቅም የለውም። ከአንድ ጥቅም ውጪ። ላባቸው እጅግ ቀለማማ ነው ማለት የሚያባክኑት ከፍተኛ የሆነ አቅም (energy) አላቸው ማለት ነው። ያ ደግሞ ለርቢ በጣም ወሳኙ ዘር መሆናቸውን ለተቀራኒው ጾታቸው ያሳውቃሉ። ስለዚህ ብዙ ቀለማት ያላት ፒኮክ ከሌሎች ፒኮኮች ይልቅ በተቃራኒ ጾታ በጣም ተፈላጊ ትሆናለች። በዚህም ለዘር (ለርቢ) ምርጧ መሆኗን ታሳያለች። ይሄ በጣም ዝቅተኛ አስተሳሰብ ባላቸው ሰዎች ዘንድ በተመሳሳይ አለ። ለምሳሌ የእነዚህ ፒኮኮች ባህሪን ልክ እንደ መንሱር ጀማል ያሉ ሰዎች ላይ ታያላችሁ። ብዙ የሚጨነቁት ለሰዎች እና ለማህበረሰቡ ስለሚያሳዩት የሀብት መገለጫዎች ነው። ያ በጣም ዝቅተኛ የሆነው እንስሳዊ ባህሪ ሲያስተዳድረን የምናሳየው ባህሪ ነው።



እጅግ ስማርት የሆነ ሰው፤ ጓደኛው ሀብታም ቢሆን እርሱም ሀብታም የመሆን ዕድሉ በጓደኛው ሀብታም መሆን ብቻ እንደሚጨምር ነው የሚያውቀው። ቢያንስ ለለቅሶ፣ ለምርቃት ወይም ለሆነ ችግር ጓደኛው ሲመጣ ሀብታም ቢሆን ደሃ ከሚሆን ይልቅ የሚሰጠው ገንዘብ ከፍ ይላል። በጓደኛው ኮኔክሽን እና ኔትወርክ ተጠቅሞ እርሱም ወደ ሀብት ከፍ ሊል ይችላል። ይሄ ሁልጊዜ እውነት ባይሆን እንኳን ጓደኛው ሀብታም በመሆኑ ዕድሉን ያሰፋዋል።



በተመሳሳይ ኢትዮጵያኖች በአሜሪካ ውስጥ ያሉ ሌሎች የኢትዮጵያኖችን ቢዝነሶች በስትራቴጂ ቢደግፉ ፥ የመጀመሪያው ለልጆቻቸው እነዚህ ስኬታማ ኢትዮጵያኖች ዓርአያ መሆን ይችላሉ። በአሜሪካ ውስጥ ኢትዮጵያዊ ተኮኖም ሊሳካልን እንደሚችል ማሳያ አገኘን ማለት ነው። የሰው ልጅ ደግሞ በእንስሳዊ ባህሪው ምክንያት የሚቀናው ብቻ ሳይሆን የሚበረታታውም አጠገቡ ባለው ሰው ነው። ለምሳሌ መንገድ ላይ ስትሄዱ ነጭ ብቻ እያለፈ ፥ ድንገት ኢትዮጵያዊ የሚመስል ሰው ሲያልፍ ካያችሁት አንገታችሁን አዙራሁ ሁሉ ታዩታላችሁ። ለምን? ምክንያቱም በሰው ሀገር ሆናችሁ ፥ አንዳች የሆነ የቡድን እና የመኖር (survivial) ጥያቄያችሁን የሚመልስላችሁ ይሄ እናንተን የሚመስለው ሰው ነው። ልጆቻችሁ የነጭ ትልቅ መሆን አይደለም በአስጨናቂ እና ከባድ ወቅት የሚያጀግናቸው እና እስከመጨረሻው ለመዋጋት የሚያጠነክራቸው። ይልቁንስ ሌላ እነሱን የሚመስል ሰው ስኬታማ መሆን መቻሉን ሲመለከቱ ነው የሚበረታቱት።



የአበበ ቢቂላ የማራቶን ድል ለብዙ ኢትዮጵያኖች በር እንደከፈተ፤ እኛን የመሰሉ ሰዎች የበለጠ ሲሳካላቸው ለኛም በር የበለጠ ይከፈታል። ብዙ ስኬታማ የኢትዮጵያ ቢዝነሶች አሉ ማለት ብዙ ኢትዮጵያኖች የሥራ ዕድል ያገኛሉ ማለት ነው። ብዙ ኢትዮጵያኖች የሥራ ዕድል ሲያገኙ ሀገር ቤት ብዙ ሰው ይታገዛል ማለት ነው። እርሱ ብቻ ሳይሆን ቢዝነሶች በባህሪያቸው ሌሎች ግብአቶችን ይፈልጋሉ። ለምሳሌ የሬስቶራንት ቢዝነስ ስጋ የሚያቀብለው ይፈልጋል። የጥራጥሬ እና የስፓይስ ግብአት ይፈልጋል። የማስታወቂያ ድጋፍ ይፈልጋል። ስለዚህ ስኬታማ የኢትዮጵያ ሬስቶራንት አለ ማለት እነዚህን ግብአቶች ከሌሎች ኢትዮጵያኖች መግዛት ይችላል። ለሌሎች ብዙ ሰዎች የቢዝነስ ዕድል ፈጠረ ማለት ነው። አንድ የማውቀው ኢትዮጵያዊ የሪል ስቴት ባለሀብት አለ። ቢሞት የነጭ ሪሌተር አይቀጥርም። ሁልጊዜ ቤት ሊገዛ ሲፈልግ ብዙ በእውቀት እና በዋጋ የተሻሉ ነጭ ሪሌተሮች እያሉ እርሱ ግን ኢትዮጵያዊ ሪሌተር ነው የሚጠቀመው። ይሄ ለኢትዮጵያኖች አዝኖ ብቻ እንዳይመስላችሁ። ኢትዮጵያዊ ሀብታም በብዛት ቢኖር የመጀመሪያው ተጠቃሚ እርሱ እንደሆነ ስለገባው ነው።



ኢትዮጵያኖች ግን ገና ስትጠይቋቸው የነጭን ሰርቪስ እንደሚጠቀሙ በኩራት እና በጀግንነት ነው የሚነግሯችሁ። “እኔ ኢትዮጵያዊ አልቀጥርም ወይም እኔ ኢትዮጵያዊ ጋር አልሄድም” በማለት ልክ ጽድቅ እንደሰሩ በኩራት ነው የሚናገሩት። በእኔ የሕግ ሥራ ውስጥ ያሉ ብዙ የነጭ ጠበቆች አንዱ በጣም የሚያስገርማቸው ነገር አብዛኛው ስደተኛ ፕሬዝዳንት ትረምፕን መምረጡ ነው። ይሄን ደግሞ በኩራት ነው ብዙ ኢትዮጵያኖች ጭምር የሚያወሩት። ተመልከቱ ፖለቲካ የጥቅም መድረክ ነው። “ማነው የእኔን እና የወገኔን ጥቅም በተሻለ የሚያስጠብቅልኝ” ብለህ አስበ ነው የምትመርጠው። በምን ተዓምር ነው አንደ በነጭ የበላይነት የሚያምን ነጭ እና ኢትዮጵያዊ አንድን የፖለቲካ ተመራጭ በተመሳሳይ ሊመርጡ የሚችሉት?


ለብዙ ኢትዮጵያኖች ሌሎች ኢትዮጵያዊ ስደተኞች ባይመጡ እና ሀገሩ የነጭ ብቻ ሆኖ እነርሱ ግን በሰላም ቢኖሩ ደስ ይላቸዋል። ከዚህ በላይ primordial and lowest thinking (በጣም ዝቅተኛው የእንስሳዊ አስተሳሰብ ማሳያ) ወዴት ይገኝ ይሆን?



በርዕሴ እንደገለጽኩት አይሁዶች ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የተማሩት አንድ እውነት መተባበር እና በሕብረት ተደጋግፎ መሥራት ብቻ በዚህ ዓለም እንደሚያስከብር ማወቃቸው ነበር። የዛሬ ሁለት ዓመት ከራሺያ የመጣ አንድ አይሁድ ቤቴ ከሚስቱ ጋር ጋብዤው ማውራት ጀመርን። ከዛ “አይሁዳች በጣም አዋቂ እና ጂኒየስ ናችሁ” አልኩት። ስቆ፦ “እንደዛ እንኳን አይመስለኝም። እኛ በሁሉም ቦታ ተበትነን ያለን እና በሄድንበት ሁሉ አናሳ የሆንን ነን። በዚህ ደግሞ ለተከታታይ ጥቃቶች ተጋልጠናል። ስለዚህ መተባበር ብቻ የመኖር ሕልውና ማስከበሪያችን መሆኑን አወቅን አለኝ። ለምሳሌ ልንገርህ። እኔ እዚህ ስመጣ የማላውቃቸው አይሁዶች እየጠሩኝ በተከታታይ ግብዣ ያደርጉልኝ ነበር። በማንኛውም ጊዜ ቢቸግርህ አለን ከጎንህ ይሉኛል። ይሄ የአይሁድ እምነት ልከተል ወይም በፖለቲካ እምነቴ የግራ ዘመም ወይም ቀኝ ዘመም ልሁን ምንም ሳይገዳቸው ነው። ይሄ በየቦታው ባህል ተደርጓል። አይሁዳዊ መሆኑ ብቻ በቂ ነው። ያን ሰው መርዳት እና መደገፍ እና ስኬታማ እንዲሆን አስፈላጊውን ዕድል መፍጠር የሁላችንም ግዴታ ነው። ስለዚህ ይሄ ስሜታዊ ትስስር ስላለ ጥቂትም ብንሆን ትብብሩ ስላለ በቀላሉ ብዙ ቁልፍ ቦታዎችን መቆጣጠር እና ስኬታማ መሆን ችለናል።” አለኝ።



ኢትዮጵያኖች ከዚህ ብዙ መማር ይኖርብናል። እውነት ነው ይሄ ካለ እውቀት እና ቆም ብሎ Reflect ካለማድረግ አይመጣም። ግን ይሄን የምታነቡ ሰዎች ቢያንስ ለመለወጥ አስቡ። ጥቂት ለውጦች እየተጠራቀሙ መጨረሻ ላይ ጠንካራ ባህል ይሆናል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page