top of page
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • 15 hours ago
  • 3 min read



 


“መልካም ስም ከብዙ ባለጠግነት ይሻላል፥ መልካምም ሞገስ ከብርና ከወርቅ ይበልጣል።” ምሳሌ 22፥1



ማህበራዊ ሚዲያ ላይ መንግስትን ደግፋችሁም ይሁን ተቃውማችሁ ወይም የሆነ ግለሰብ ወይም ተቋም ላይ የሀሳብ ልዩነት ስታነሱ መጥተው በነውረኛ ስድብ የሚያጥለቀልቋችሁ ሰዎች ተፈጥረዋል። የሚገርመው ደግሞ የእነዚህ ሰዎችን የፕሮፋይል ፎቶ ስታዩ የክርስቶስ፣ ወይም የማርያም ስዕል ወይም ደግሞ የሃይማኖት ተቋም ምልክት ወይም አላህን ወይም ፈጣሪን የሚጠራ ጥቅስ ያዘለ ሆነው ታገኛላችሁ ሁሉም ባይሆኑም እንኳ አብዛኞቹ እንደዛ ናቸው።



የቅዱሳን ወይም የፈጣሪ ወዳጅ ነን ብለው ፕሮፋይል ፎቶ ቀይረዋል ግን የስድብ አፍ አላቸው። ሰዎችን ከማዋረድ፣ ከመስደብ፣ ከመዝለፍ ውጪ ምንም ጨዋነት የተሞላው ክርክር እና ውይይት አያደርጉም። በሀሳብ ለመሞገት አይችሉም። ግን ጸያፍ የስድብ አፍ አላቸው። በዮሐንስ ራዕይ ላይ “ለአውሬው የስድብ አፍ ተሰጠው” ይላል። መቼስ የሚሳደብ አውሬ እስካሁን አላየንም። አውሬው ልንባል የምንችለው ተሳዳቢዎቹ እኛው ነን።



እኔ በወገኔቼ ላይ የማየው ይሄ አስነዋሪ ምግባር የምር ያሳስበኛል። በመጀመሪያ ከፈጣሪ ጋር ያጣላል እግዚአብሔር እርስ በእርሳችን እንድንከባበር አዞናልና በተጨማሪም ልዩነት ማለትም የሀሳብ ልዩነት የብዙ መልካም ነገሮች ውጤት ነው። የተሰበሰው ህዝብ ሁሉ ንጉሱ ራቁቱን ሆኖ እያየው ከፍርሃት የተነሳ ያልለበሰውን ልብስ “ዋው! እንዴት ያምራል!” ሲል ፥ አንድ ልጅ ናት “ንጉሱኮ ራቆቱን ነው!” ያለችው። ይሄ ምሳሌ የሚነግረን ሀሳብን ማፈን የማህበረሰብን ውድቀት እንደሚያፋጥን ነው።



ስንት ድንቅ እውቀት እና ሀሳብ ያላቸው ሰዎች የአውሬዎችን የስድብ አፍ ተፀይፈው ከሀሳብ መለዋወጫ መድረክ ራቁ?! ይሄ ደግሞ ዋልጌዎች ልጆቻችን ላይ ተጽዕኖ እንዲያሳድሩ ፥ እውቀት አልባ ሰዎች መድረኩን እንዲይዙ ዕድል ይፈጥራል።



ዛሬ አንድ ከምደነቅበት የአዲስ ኪዳን ታሪክ ላጋራቹ። በሉቃስ ወንጌል 16:19 ጀምሮ ያለ ብዙ ትምህርት ያለው ታሪክ ነው። እኔ ግን ከጨዋነት አንጻር ብቻ ለትምህርት ይሆነን ዘንድ ልጥቀስ።



ታሪኩ ስለ አንድ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ደስተኛ ስለነበረ ባለጸጋ እና አልአዛር ስለተባለ ድሃ ነው። ድሃው አልአዛር ሲሞት ወደ አብርሃም እቅፍ በመላእክት ተወሰደ። ሃብታሙ ግን ወደ ሲዖል። ከሲዖል ሆኖ ወደ አብርሃም እየተመለከተ “አብርሃም አባት ሆይ ማረኝ፥” እያለ ምህረት እና ውሃ ለመነ። ለእኔ አስደናቂው የአብርሃም መልስ ነበር። ይሄ በሃጢአቱ ምክንያት ወደ ሲዖል የወረደ፣ ለደሃው አልአዛር ፍርፋሪ ለመስጠት እንቢ ያለ ንፉግ ባለጸጋ አሁን በድፍረት ምህረት እና ውሃ ሲለምን፤ አብርሃም ብዙ ማለት በቻለ ነበር። አብርሐም በደሉን አስታውሶ ሊያሳፍረው ወይም ሊሰድበው አልወደደም ይልቁንስ “ልጄ ሆይ” ብሎ መለሰለት እንጂ። ይሄን የተፈረደበት ኃጢአተኛ ልጄ ለማለት አብርሐም አልተጠየፈም።



በዚህ ባለጸጋ የተበደለው ህያው ምስክር ሆኖ በአብርሃም እቅፍ መኖሩ ፥ ለአብርሃም ያልተገባ ንግግር ለመናገር ምክንያትም ሆነ ሰበብ ሊሆን አልቻለም ፥ ይልቁንስ ለሚጠይቀው ጥያቄ ሁሉ ሳይሰለች በአክብሮት መለሰለት እንጂ። ድሃውን አልአዛርን ለማየት ያልፈቀደ ይሄ ባለጸጋ ፥ የአብርሃምን የክብር መልስ ግን አገኘ። በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር ቢፈረድበት እንኳ አብርሃም ግን ልጄ ብሎ በክብር ጠርቶት ምህረት እንደማይደረግለት ነገረው።



ክፉ ዜና ለመንገር እንኳ አንደበቱን ማቆሸሽ አላስፈለገውም። ያንን በክብር ነገረው እንጂ። የመልካምነት ማማ አብርሃም ፥ ከሲዖል ለሚያናግሩት እንደዚህ ካለ ፥ እኛ ገና በዚህ ምድር የመጨረሻ ፍርድ ሳይቀበሉ ላሉት የምናሳየው ርህራሔ ምንኛ መተለቅ ነበረበት።



የአብርሃምን አሉታዊ የሆነ መልስ የሰማው ባለጸጋውም ፥ ከዚህ በኋላ ምን ሊቀርብኝ ብሎ አንደበቱን አላጎደፈም። እስከመጨረሻው “አባት ሆይ” እያለ ነበር አብርሃምን ያናገረው። ወደ ገነት የመግባት ምንም ተስፋ እንደሌለው ቢነገረውም አሁን ግን ከሞት በኋላ ባየው ነገር ይሁን ወይም ያለፈው ዘመኑ ሕይወት ከንቱነት ገብቶት ተስፋ የለህም ሲባል እንኳ አንደበቱ ጨዋነት አልተለየውም ነበር።



ወገኖቼ ቅዱስ ጳውሎስ የሚለን ነገር አለው። “እግዚአብሔር አይዘበትበትም። ሰው ሁሉ የዘራውን ያጭዳል።” ስድብን የሚዘራ ነውርን ያጭዳል። ጨዋነትን የሚዘራ ክብርን ያጭዳል።



መልካም ስም፣ መልካም አንደበት ከምንም ሃብት በላይ ነው። ብዙ እውቀት የማያስከፍተውን በሮች መልካም ምግባር ያስከፍታል። አንደበታችንን፣ አዕምሮአችንን መግራት ያስፈልጋል። ለሰዎች በክብር ለመመለስ እንጣር። እኛ መከበርን እንደምንፈልግ ሁሉ ሌሎችን እናክብር።



ስድቡን ኪቦርድ ላይ ስንፅፈው ሄዶ የሚያርፈው ሰው ልብ ላይ መሆኑን እናስታውስ፥ ተጎጂዎቹና ጉዳቱ ሩቅ ሆኖ ካልታየን እኛ ላይ ሲደርስ ያለውን ህመም እናስታውስ:: ማዋረድ የሰይጣን ባህሪ ነው፥ ዳይብሎስ ነው አዋራጅ:: እኛ ግን በክብር ጌታ ምሳሌ የተፈጠርን ነን እና ለምንናገረው እንጠንቀቅ።



አንደበታችንን መግራት የማንፈልግ ተናዳጅ እና ቁጡ፣ ተሳዳቢ ለመሆን ከወሰንን ደግሞ ቢያንስ የፈጣሪን፣ የቅዱሳንን ስዕል እና ጥቅስ ከፕሮፋይል ፎቶ እንቀይር። ይሄ ሌላ በደል ይሆንብናልና።

 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • May 31
  • 4 min read


በየቀኑ ስለ መጪው ግምት እንሰጣለን። በተለይ ሙያተኛ ስትሆኑ ደግሞ ሰዎችም ስለ መጪው ይጠይቋችዋል። አላውቅም ካላችሁ ወይ እየዋሻቹ ነው የሚመስላቸው ወይም እውቀት የሌላቹ። ግን ደግሞ ሁላችንም ስለ መጪው ገምተን ውሳኔ እንሰጣለን።



ሕይወቴ እንዲሰምር ማንን ላግባ?


ምን ባጠና ይሻላል?


ምን ሙያ ልምረጥ ወደፊት የሚያበላ?


ብሰደድ ወይስ ሀገሬ ብቀር?


ዓብይ አህመድ ለሚቀጥሉት ዓምስት አመታት ይቀጥላል ወይስ ይወድቃል?


ዲሞክራቶች ይመረጣሉ ወይስ የአሁኑ አስተዳደር ይቀጥላል?



የመሳሰሉት መጪው ጊዜ ላይ ያተኮሩ ትንበያዎችን በየቀኑ እንሰጣለን። ያን ተመስርተን ሕይወታችንን በዛ መንገድ እንመራለን።



ግን ከዚህ በፊት ያደረግናቸውን ትንበያዎች ብንመለከት ብዙዎቹ አሰቃቂ ናቸው። በአንድ ወቅት የDepartment of Homeland Security ምክትል የነበረ አንድ የሕግ ፕሮፌሰር ነበረኝ። ፕሬዝዳንት ትረምፕ ሲመረጥ ትረምፕ የሚሰራቸውን ታሪኮች፣ ስለሚገነባው አዲስ የፌዴራል ከተማ፣ ስለሚቀነሱ በጀቶች እና የአሜሪካ የበጀት ጉድለትን እንዴት እንደሚፈታ በማብራራት በኢሜል ያልጻፈልኝ ጉድ የለም። እኔም የእርሱን እምነት ሳይ ትረምፕ ሊያደርገው ይችላል ብዬ አስቤ ነበር።



ከሁለት ዓመት በኋላስ ምን ሆነ? በቅርብ ኢሜል አደረኩለት። ትረምፕ ክዶናል አለኝ። ጦርነት ጀመረ። የፌዴራል በጀት ጉድለት በጥቂት ወራት ውስጥ 39 ትሪሊዮን ዶላር ደረሰ። አሜሪካ በዓመት ከምትሰበስበው በላይ ለዕዳ የምትከፍለው በለጠ። የተገነባ የፌዴራል ከተማ የለም። ትረምፕ በብዙ ሙስና እየታማ ነው። ያ ሁሉ ግምት ውሃ በላው። ያ ሁሉ ትንበያ (በጣም አዋቂ በሚባል ሰው የተሰጠ) የተገላቢጦሽ ሆነ።




ዛሬ ከአጎቴ ጋር ስናወራ፣ ስለ ኢትዮጵያ ምርጫ አነሳን። ከዛ ዓብይ አህመድ ወደ ስልጣን ሲመጣ የተናገራቸውን ንግግሮች፣ ስለዲሞክራሲ የገባቸውን ቃሎች፣ ስለ ፖለቲካ ምህዳሩ የገለጸልን ተስፋዎችን እና እኛ ደግሞ በምን ደረጃ አምነን ኢትዮጵያችን ተቀየረች ፥ ትንሣኤዋ ደረሰ ብለን ተቀብለን እንደነበረ ራሳችንን ገመገምን። ከስምንት ዓመት በኋላ ከአዲስ አበባ ልዩ ማማር በቀር ሀገራችን እንዳልነበረች ሆና አገኘናት። የቱንም አልገመትንም ነበር። የቱም አልታየንም ነበር። የኢትዮጵያ ሕዝብ ነገ ለምርጫ የቀረበለትን ዓብይ አህመድን ብቻ ሊመርጥ እየወጣ ነው። ይሄን ማየት አልቻልንም ነበር።



ነገስ? ከዛሬ ስምንት ዓመት በኋላስ ምን ይሆናል? ከዛሬ ሁለት ዓመት በኋላስ? AI በሁሉም ቦታ እየመጣ ነው። ምንድነው የሚሆነው ነገር?






አላውቅም።






ግን ስለ አንድ መሳጭ ታሪክ ልንገራቹ። ዓለምን ስለወረሰ ሰው። እንዲሁም ለዓለም ጥፋት ምሳሌ ስለሆነ ሰው።



ዘፍጥረት ምክራፍ 13 ላይ ነው ያለው።




የወንድማማች ጦርነት። የታላቅ እና የታናሽ ወንድሞች ጥል።




የአብርሃም እና የሎጥ የእረኛ ሠራዊት በግጦሽ መሬቶች ተጣሉ። ጥንታዊ ጦርነትም ሆነ ዘመናዊ ጦርነት በሪሶርስ መቆጣጠር ላይ ያለ ነው።




አብርሃም ይሄ የእረኞች ጥል ወደ እርሱ እና ወንድሙ ሎጥ ጋር መምጣቱ እንደማይቀር አወቀ። ስለዚህ ወደ ሎጥ ሄዶ እንዲህ አለው። "እኛ ወንድማማች ነንና በእኔና በአንተ በእረኞቼና በእረኞችህ መካከል ጠብ እንዳይሆን እለምንሃለሁ። ምድር ሁሉ በፊት ህ አይደለችምን፧ ከእኔ ትለይ ዘንድ እለምንሃለሁ፤ አንተ ግራውን ብትወስድ እኔ ወደ ቀኝ እሄዳለሁ፤ አንተም ቀኙን ብትወስድ እኔ ወደ ግራ እሄዳለሁ።" ዘፍ ምዕ 13፥8።



አብርሃም ምን ያህል የወደፊቱን መገመት የሚችል ሰው መሆኑን እወቁ። ሁሉን ነገር ግን አይደለም። የሰውን ባህሪ ነው የገመተው። ሰው ይጣላል። ጻድቅ ነን ስለዚህ ከጥል ነጻ ነን አላለም። ሁለት ሰዎች ተመሳሳይ ነገር የሚፈልጉ ከሆነ መጣላታቸው አይቀርም። አንዳች በመኃላቸው ይሄን የሚያስቆም ጠንካራ ሥርዓት ከሌለ በቀር። አቻዎች ይጣላሉ። አብርሃም ታላቅ ቢሆንም ሎጥን ግን በትህትና እና በልመና ቀረበው። እንለያይ ብሎ ለመነው። አሁንም ታላቅ ቢሆንም የመምረጥን ቅድሚያ ለሎጥ ሰጠው። አንተ ምረጥ እኔ እከተላለሁ አለው።



ሎጥ የእርሱ እና የአብርሃም እረኞች ጥል ሰላም እንደነሳው የሚገልጽ ምንም ነገር የለም። ምንአልባትም ሁልጊዜ አሁን ያለው የወንድማማች ፍቅር ይቀጥላል የሚል የዋህ እይታ አለው ማለት ነው። ምክንያቱም ይሄ ነገር አሳስቦት የመጣው አብርሃም እንጂ ሎጥ አይደለም። አብርሃም ጠብን ከሩቅ አይቶ መጪውን ተነበያ። ለዛም መጠበቂያ ሊያደርግ ተነሳ።



መጠበቂያውንም ሲዘረጋ የእኔ የሚለውን እና የራሱን ጥቅም ለማስጠበቅ ቅድሚያ አልሰጠም። ግን መልካም የሆነውን ለወንድሙ፣ ለታናሽ ወንድሙ በማስቀደም አንተ ምረጥ አለው። በስግብግብነት የሚጸና ዘላቂ ሰላም እንደሌለ አውቋልና። ሎጥ አሁንም "አንተ ታላቅ ነህ። አንተን መከተል ነው ያለብኝ" አላለውም።



እሺ ብሎ የወደፊቱን መኖሪያውን ለመምረጥ ተነሳ። የምርጫ መስፈርቱንም ዓይኑን አደረገ። መጽሐፉ ቅዱስ ሎጥ ዓይኑን አነሳ። ለዓይኑም እንደ እግዚአብሔር ገነት የምትመስለውን፣ በግብጽ አምሳያ የተሰራችውን ሰዶምን መረጠ ይለናል። ውበት። እርሱም የዓይን ውበት ነበር መለኪያው።



የወደፊቱን ተነበየ። በትንበያውም መሰረት መረጠ። የዛ ትንበያ ፎርሙላ የዓይን ውበት ነበር። ሳየው ደስ ይለኛል። ሳየው ያምራል። የሚል።



አብርሃም ወደ ምርጫ እና የወደፊቱን መኖሪያ ለመምረጥ አልተጣደፈም። ተረጋጋ። ሎጥ ግን በፍጥነት ተለየው። ይልቁንስ አብርሃም እግዚአብሔር መጥቶ ዓይኑን እስኪያበራለት ድረስ ታገሰ። በመጨረሻም የመረጠው ቦታ ድንጋያማውን ኬብሮን ነበር። ግን ጸሎት እንዳደረገ እና በእምነትም በመደገፍ ያን ምርጫ እንዳደረገ እናነባለን። ግን የዓይን ውበት አልነበረውም ፥ ቤተሰብ ለመመስረት፣ ተረጋግቶ ለመኖር፣ አምላኩን ለማምለክ የሚያስችል ስፍራ ግን ነበር።



በአብርሃም የወደፊት ትንበያ ውስጥ የምንማራቸው በጣም አስገራሚ እውቀቶች አሉ።



የመጀመሪያው ስግብግብነት የለበትም። ለራሱ ቅድሚያ ያልሰጠ ምርጫ ነበር። ታናሽ ወንድሙን አስቀደመ። ምን አልባት ሌሎችን መስማት፣ ታናሽ ቢሆኑ እንኳን ሌሎችን ለማድመጥ መሞከር ስለ ወደፊቱ ለመገመት ይረዳል። ከሁሉ በላይ ሰው ስግብግብ በሆነበት ነገሮች ላይ ጥራት ያለው እይታ አይኖረውም። የቸኮላችሁበት፣ የተስገበገባችሁበት ነገሮች ላይ ግልጽ እና ጥርት ያለው እይታ የላችሁም። ስለዚህ ተረጋጉ። ሌሎች ሊቀሟቹ ከመሰላቹ ተውሏቸው። ይውሰዱት።



ሁለተኛ አብርሃም ዓይኑን አላመነም። ዓይናችን እውነትን የመግለጥ ተልዕኮ ብቻ የለውም። የመጋረድም እንጂ። ሎጥ መጥፊያውን ከተማ መረጠ። ሚስቱን አጣበት። ልጆቹ አስነወሩት። ሎጥ የብዙ መጥፎ ምስሌ እንዲሆን አደረገው ዓይኑ። ፍጻሜውም ጉስቁልና ሆነ። የእርሱ ንጽህና ነፍሱን ቢታደግለትም ደስታ እና ርካታ ግን አልሰጠውም። ምክንያቱም የወደፊቱን በዓይኑ ብቻ መርጧልና።



አብርሃም በእምነት እና በጸሎት ጭምር ተደገፈ። መሰረታዊ የሆኑ የወደፊት ሕይወታችን ላይ ልዩነት የሚፈጥሩ ጉዳዮች ላይ እንረጋጋ። ጸሎት ማድረግ ከቻልን እናድርግ። የማናምን ካለን ደግሞ ቢያንስ የተረጋጉ እና የሰከኑ፣ ታማኝ ሰዎችን እናውራ። ከዛም በእምነት ይሁን ምርጫችን።



አብርሃም የመሬቱ ውበት ሳይሆን የእምነቱ ጥንካሬን መሠረት አደረገ። ብዙ ሰዎች ነገ የሚያበላው ምንድነው ብለው ሙያ እና ትምህርታቸውን ይመርጣሉ። ከዛ ይልቅ ጠንካራ የሆንበትን፣ ጎበዝ የሆንበትን ነገር የምርጫ መሠረታችን ብናደርግ ስኬት ይቀርበናል።



ሎጥ የምርጫውን አካባቢ እና ሁኔታ ለማጥናት ጊዜ አልወሰደም። ቢወስድም በዛ ያሉት ሕዝቦች ምን እንደሚመስሉ፣ ለልጆቹ እንዴት ያለ አካባቢ መሆኑ፣ ሰው አነዋወሩ እንዴት እንደሆነ ግድ አልሰጠውም። አንድን ነገር ስንመርጥ እና የወደፊቱን ስንተነብይ ይሄ ዓለም ውስብስብ መሆኑን አንርሳ። ምርጫችን እና ትንበያችን በብዙ ዙሪያው ባሉ ጉዳዮች ይጠቃል። በብዙ የተያያዙ ጉዳዮች ተጽዕኖ ውስጥ ይወድቃል። ለምሳሌ ይሄን ግለሰብ አምነዋለሁ ብለን ልንመርጠው እንችላለን። ግን ግለሰቡ ምን ዓይነት ጓደኞች አሉት፣ የት ያዘወትራል፣ አብረው እነማን ይሰራሉ፣ ቤተሰቡ ምን ይመስላል እና የመሰሉ ሁኔታዎች ያ ግለሰብ መልካም ቢሆን እንኳ ሊቀይሩት ይችላሉ። ስለዚህ ብዙ ጉዳዮችን ትንታኔያችን ውስጥ ማስገባት ተገቢ ነው።



በመጨረሻም ለምርጫችን ጊዜ እንስጠው። የሎጥ ምርጫ መጥፎ እንደሆነ የአብርሃም ምርጫ ደግሞ ትክክል እንደነበረ ለማየት ጊዜ አስፈልጎታል።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • May 26
  • 4 min read


በሥጋ ማርያም ተገልጦ፥ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በአይሁድ ምድር ሲመላለስ አምላካቸውን ያዩት ሰዎች እንዴት ታድለዋል የሚል ነገር አንዳንዴ ውል ይልብኛል (ይሄ ዘወትር የምንደነቅበት ነበር መሆን ያለበት)።


ተመልከቱ ቅዱስ ሉቃስ “እንደልማዱ በሰንበት ወደ ሙኩራብ ገባ” ይለናል። (ሉቃ 4፥26)። በዕለተ ሰንበት ስትሄዱ መጽሐፉን ገልጦ የሚያነበው ዓለምን በቃሉ የፈጠረው ፥ በእጆቹ የፈጠረን አምላክ ነው።


ግን እኔስ በዛ ዘመን ብኖር ከአይሁድ የተለየ ለጌታዬ ቦታ እሰጠው ነበር? ለዛውም ዘወትር በሰንበት ወደ መቅደሱ የማልሄድ ከሆነ ፈጽሞ አላየውም።


በቤተሳይዳ የጸበሉ ስፍራ ስትሄዱ 38 ዓመት አልጋ ታቅፎ የኖረን ሰው አንድ በሠላሳዎቹ መጀመሪያ ያለ ወጣት እያናገረው ነው፤ ከዛ በሚደንቅ ተአምር አልጋህን ይዘ ተነስ ሲለው ታያላችሁ፤ ያያችሁትን ማመን ቢከብዳችሁም ያን ሰው ግን፣ ያ አጃቢ ያላስከተለውን፣ የወየበ ልብስ የለበሰን ሰው፣ ያ በለሰለሰ ድምጽ የሚናገርን ሰው እንዴት አምላክ ብላችሁ ትወስዱታላችሁ? በዛ ላይ በኑሮ ወጥመድ ተወጥራችሁ፣ እከሌ ዓየን ዓላየን፣ ማን ነው መጀመሪያ ጸበል ውስጥ ዘሎ የገባው የሚለው ወሬ አካባቢውን ወጥሮት እንዴት ይሄን ሰው ዓይኖቻችን ይየው?


ስለአምላክ ያላችሁ፣ ስለሚመጣው መሲህ የሰማችሁት ትንታኔ እና የተወሩ ወሬዎች ሁሉ ዓይናችን ሥር ሆኖ ምስኪኑን መጻጉ የሚያናግረውን አምላክ የሚያገል ነበር።



ያ ዘመን ዛሬ ቢሆን እኔ ከአገለሉት፣ ሲገደል ከተደሰቱት ወይም ግድ ካልሰጣቸው ሰዎች ተርታ የምመደብ እንደምሆን እራሴን እጠረጥራለሁ።



እስቲ በዚሁ ወደ ሰማርያ እንለፍ። ወደ ዩሐንስ ወንጌል ምዕራፍ አራት። “ወደ ሰማርያ ሊያልፍ ግድ ሆነበት” ይለናል ዩሐንስ። ብዙም ሳይዘገይ “በውሃ ጉድጓድ አጠገብ ተቀመጠ” ይለናል። ለምን በሰማርያ ሊያልፍ ግድ እንደሆነበት ሲነግረን።


ከዛ አንዲት በኃጢአት የደከመች፣ በሃይማኖቷ ግን “ክርስቶስ የሚባል መሲሕ ይመጣል የዛኔ እሱ ሁሉን ይነግረኛል” ብላ በልቧ የምትጠብቅ ምስኪን ሴት የውሃ እንስራዋን አዝላ ከነመቅጃዋ መጣች።


ውሃ ስጪኝ አላት ያ የማይጠማው ከሷ ኃጢአት የተነሳ ግን ደክሞት የተጠማው ሰው። የተሰመረን መስመር መሲሒው መጥቶ ምክንያቱን እስኪነግራት የምታከብረው ያቺ ሴት ግን አይሁዳዊ ሲሆን ከሳምራዊት ሴት ውሃ ስጪኝ ማለቱን አልወደደችም። እሱ ግን አላት “የሚጠይቅሽን ብታውቂ አንቺ ነበር ውሃ የምትጠይቂው።” ግራ ገባት። በአንድ በኩል የሚቀልድ መሰላት፣ ስለዚህም በምክንያት እና በማሾፍ ሞገተችው “የታለ መቅጃኸ?” አለችው፣ በሌላ በኩል ይሄ ሰው ሥርዓት አለው፣ እንደሌሎች የምታውቃቸው አይሁድ አልመስላት አላት፣ አይሁድ ሆኖ ሳለ ከሳምራዊት ሴት ጋር ማውራቱ ሳያንስ አነጋገሩ በሥልጣን ነበር። ቸል ብለው የማያልፉት ነበር። ይሄም ከቃሉ የተነሳ ብቻ አልነበረም። ከሁኔታው፣ ከመልኩ፣ ከሞገሱ፣ ዓይን ብቻ የሚገባው ቃላት የማይገልጸው የእውነት ውበት በማየቷ ጭምር እንጂ፣





ይሄ ግን አካላዊ ውበት እንዳይመስላችሁ፤ ከኃጢአት ድካም ማረፍን የናፈቀች ነፍስ ብቻ የምታውቀው፣ ስታየው ግን የማታልፈው ልዩ ውበት እንጂ። ። በመኃልየ መኃልይ ጠቢበኛው ሰሎሞን የገለጻት ነፍስ ስታየው የምታውቀው ፥ ውዷን ከመፈለጓ የተነሳ የደከመችው ያቺ ሴት ስታየው የምታውቀው ውበት ያለው ነበር እንጂ። ለዚህ ነው “ነቢይ እንደ ሆንህ አያለሁ” ያለችው። ንግግሩ ብቻ ስላልሆነ ነው “አያለው” ያለችው።



አምስት ባሎች የነበሯት አሁን አብራው ካለችው ጋር ባልተቀደሰ ጥምረት የተሳሰረችው ያቺ ሴት ግን ክርስቶስን ግድ ያስባለ የሃይማኖት ውበት ነበራት። ያም ተስፋ ነበር። “አንተ ከአባቶቻችን ትበልጣለህ፣ አንተ ከያዕቆብ ትበልጣለህ፣ ደግሞ ይመጣል ያ መሲሒ፣ ይመጣል ክርስቶስ ሊነግረን ሁሉን” ትለው ነበር ለራሱ ለክርስቶስ።


በኃጢአት ብዛት ቀጥና በአባቶቿ እምነት ተስፋ ግን ሳትሰበር ያለችው ያቺ ጌታን ግድ ያሰኘች ነፍስ።



ሲ ኤስ ሉዊስ እንዲህ ይላል “በዚህ ምድር ላይ ተራ ሰዎች የሉም። ከሟች ሰው ጋር በሕይወታችሁ አውርታችሁ አታውቁም።” ተፈጥሮ፣ ሀገራት፣ ባህሎች፣ ጥበቦች፣ ስልጣኔዎች እነዚህ ናቸው ሟቾች። እነዚህ ናቸው አርጀተው የሚጠፉት። የእነዚህ ሕይወት ነው ለእኛ ጥቅም፣ ለእኛ እንደ ትንኝ መሆን ያለባቸው። የምናወራው፣ የምንቀልደው፣ የምንሰራው፣ የምንጋባው፣ የምንበዘብዘው፣ የምናሰቃየው፣ የምንጨቁነው ግን ዘላለማዊን ነው። ከዘላለማዊው ጋር ነው የምንጋፋው። የምንተቃቀፈው።



ጌታችን ያን ሁሉ ሰዓት በውሃ ጉድጓድ ዳር ተቀምጦ የጠበቃት፣ በእኛ ዓይን ብትሆን ባል የማይበረክትላት ተብላ የተገፋች፣ በማንኛውም ሰው ዓይን መሙላት የማትችለው ያቺ ዘላለማዊ ነፍስ ያላት አንዲት ሳምራዊት ነበረች። አንዲት ሳምራዊት። የምታየውን ወንድምህን ካልወደድክ እግዚአብሔርን ወዳለው ማለት ውሸት ነው ይለናል ሐዋርያው ዩሐንስ በመልዕክቱ፣ ምክንያቱም እግዚአብሔርን አላየኸውምና። (1ዮሐ 4፥20)።


ይሄ ማለት አጠገብኽ ያለው ዘላለማዊው ወንድምኽ ነው ያላየኸው አምላክ መገለጫ። እሱን ውደደው፣ ግድ በለው፣ ለምነው ውሃ ላጠጣ ብለህ፣ የሚያስፈልገውን ለምኖ አይደለም ለምነኽ ስጠው እያለን ነው። ዘላለማዊውን ወንድማችንን ስንረዳ ዘላለማዊው ውሃ፣ የፍቅር ውሃ፣ የዚህን ዓለም ውሃ የማያስጠማው ውሃ ፥ የሕይወት ምንጭ መፍለቅ ይጀምራል ከውስጣችን። ክርስቶስ ግድ የተሰኘባትን ነፍስ ያልናቅን ለታ፣ ያን ጊዜ ነው ጌታችንን መውደድ የምንጀምረው። ያቺ ነፍስ በኃጢአት የደከመች ቢሆን እንኳ፣ ያቺ ነፍስ እኛን የሚያበሳጭ እና የሚያናድ ነገር ከመሥራት የማትቦዝን ቢሆን እንኳ፣ ያቺ ነፍስ ቀን በቀን ብታቆስለን እንኳ ከጌታችን ሥጋና ደም ቀጥሎ በዚህ ምድር ላይ ያቺን ነፍስ ነው ልናከብረው የሚገባው። ይሄ ነው የክርስቶስ ፍቅር።


የሱ ፍቅር ያለ ቅድመ ሁኔታ አይደለም። ምክንያቱም “የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል ወደ እርሱም እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን” (ዮሐ 14፥23) ብሎናልና።


የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቅ፣ እወድኸለው ስላልከኝ ብቻ አልመጣም እያለን ነው፣ ቃሌን የሚጠብቅ ግን ይወደኛል፣ እኔም አባቴም እንመጣለን። እንመጣለን በሱ ውስጥ መኖሪያ ልናደርግ። በቁመተ ሥጋ ተወስኖ በአይሁድ ምድር ሲመላለስ በእጆቹ የመዳሰስ፣ ቀሚሱን የመንካት፣ እንደ ዮሐንስ ደረቱ ላይ የመተኛት ዕድሉን ላላገኘን ሁሉ በእውነት ግን ይሄን ዕድል ለምንመኝ፣ በእናንተ ውስጥ ከአባቴ ጋር መኖሪያዬን ላደርግ እመጣለሁ አለን። ቃሌን ከጠበቃችሁ።



ለሰማሪያዊቷ ሴት እንዳላት የዘላለም የውሃ ምንጭ በውስጣችን ሊያፈልቅ ይመጣል። ያ የውሃ ምንጭ በውስጡ የፈለቀለት ቅዱስ ጳውሎስ ይሄን አለን “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ... ሞት ቢሆን፥ ሕይወትም ቢሆን፥ መላእክትም ቢሆኑ፥ ግዛትም ቢሆን፥ ያለውም ቢሆን፥ የሚመጣውም ቢሆን፥ ኃይላትም ቢሆኑ፥ ... ከጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ።” (ሮሜ 8፥ 35-39)።


“መቅጃ የለህም” በማለት እንስራ እና መቅጃ ስላላት ውሃ መጠጣት፣ በመጠጣትም መርካት የምትችል የመሰላት ያቺ ምስኪን ሴት፣ አሁን መቅጃዋን አይደለም እንስራዋን ሳይቀር ትታ ወደ ከተማ ሄደች።


ሌሎች ለዘላለም መንግስቱ እንዲሆኑ “ኑ ፥ ያን አንዲት ምስኪን ሴትን ለማዳን የደከመውን እዩ” ብላ ከከተማው ሰዎችን ጠራች። አገኘውት እያለች በንዳድ ፀሐይ የደከመች ዋላ ውሃ ስታገኝ እንደምትዘለው እየዘለለች ወደ ከተማ ገባች። አገኘውት ውዴን እያለች። ኑ እዩት ውዴ እንደ በረዶ ንጹሁ ነው ፥ ኑ እዩት ውዴ ስለእኛ በደም ተለውሶ ቀይ ነው። ኑ እዩት አፉ እጅግ ጣፋጭ ነው ይነግራችኋል ከሁሉ የተሰወረውን ታሪካችሁን፣ መልኩም ለነፍሴ ያማረ ነው። ኑ ሳምራውያን ሆይ ፥ ውዴ ይህ ነው ፥ ይመጣል ያልነው ክርስቶስ ይህ ነው ፥ ባልንጀራዬም ይህ ነው። (መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 5፥ 10-16)።



በዚህ ምድር ላይ የሚገጥመን ሰው ሁሉ ጌታችን በመስቀል ላይ ደሙን ያፈሰሰለት ነው። ያለእሱ ፈቃድ በዚህ ምድር ሊመላለስ ይቅርና ከጸጉሩ አንድ እንኳ ያለአምላካችን ፈቃድ አትነቀልም። ያ ሰው ክርስቲያን ሲሆን ደግሞ ክብሩ ልዩ ነው። በዚህ ምድር ላይ ባልጀራችን ነው አምላካችንን የመውደዳችን መገለጫ። ለእኛ በጣም ቅርቡ እርሱ ነው።


በሰማርያ ለአንዲት ኃጢአተኛ ያን ሁሉ የደከመ ጌታችን፣ በጎልጎቷ የመስቀልን መራራ ሞት የተጎነጨላትን ያቺን ነፍስ እናክብራት።


ስልጣኔ እንጂ ሟች ፥ የሰው ልጅ አይደለም።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page