top of page



በራሴ ላይም ሆነ በሌሎች ከምታዘበው አንዱ ነገር ድንበራችንን አለማወቅ እና ለማወቅም አለመፈለግ ነው። ዘወትር ዓለምን ለማየት የምንጥረው በፍላጎታችን መነጽር ስለሆነ፣ አዕምሮአችን በሚፈጥርልን ፊልሞች እንወሰዳለን። ከዚህም የተነሳ ምኞት ብዙ አቅማችንን ይወስደዋል።



በኛ ሕይወት ውስጥ ውስንነት አለ። የጊዜ፣ የጤና፣ የሪሶርስ፣ የስልጣን እና የእውቀት ውስንነቶች ሁልጊዜ አሉ። ወሰን አልባነትም አለ። የሰው ልጅ በማሰብ ወሰን አልባ ነው። ፈጽሞ አሁን ላይ የሌሉ ነገሮችን እና ፈጽሞ ያላያቸውን ነገሮች ያስባል። ደንበኛ ትርክት በነዛ ላይ ይፈጥራል። ሌሎችንም ያሳምናል። ከዛ በዛ ላይ ተመስርቶ ግዙፍ ሥራዎችን ይሰራል።



እነዚህን ውስንነቶችን እና ወሰን አልባነትን ያገናዘበ እና ሚዛን ያደረገ ሕይወት ምን አልባት ብዙዎች ስኬት የሚሉት ደረጃ ላይ ሊያስደርሰው ይችላል።



የመጀመሪያው የራስን ውስንነት፣ የሌሎችን ፍላጎት እና የአካባቢያችንን (ከኛ ውጪ ያለውን የተፈጥሮ) ሕግ ማወቅ እና መተዳደሪያቸውን መገንዘብ ያስፈልጋል። ከውስንነት ጋር መጣላት እና መጋጨት እምብዛም ጥቅም የለውም። ከእውነታ ጋር መከራከር አያሻም። ሁልጊዜ ያሸንፋልና። ይሄ ማለት ግን ሰው ውስንነቱን ዝም ብሎ መቀበል አለበት ማለት አይደለም።



ለምሳሌ የሰው ልጅ መብረር አልችልም ብሎ ቢቀመጥ ዛሬ ላይ በራሪ አውሮፕላኖችን ባልፈጠረ ነበር።



ለዚህ ነው ውስንነትን ከወሰን አልባነት ጋር ማጣጣም የሚያስፈልገው። ያም ምኞት እና ሀሳባችን ነው። ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በፍጥነት መሄድ ምኞት ነው። ሌላ አህጉር ካሉት ጋር ፊት ለፊት አሁኑኑ ተገናኝቶ ማውራት ምኞት ነበር። ግን አካላዊ ውስንነት ነበር። ሁሉ ቦታ የምንገኝ አይደለንም። የተፈጥሮ ድንበሮች ይገድቡናል። በዚህ ገደብ ውስጥ ምኞት (ገደብ አልባው) ሲገባ በሁለቱ መኃል ያለ አስታራቂ ቁሶችን እና መላዎችን መፍጠር ተቻለ። ክንፍ ማውጣት ባንችል ክንፍ ካላቸው ተምረን ክንፍ ባለው ነገር መሄድ ጀመርን።



ሃይማኖት የተፈጥሮ ድንበርን ተሻግረን ከሌላው ዓለም ካለ ሰው ጋር የመገናኘትን ሕልም ሲያድለን፤ ስልክን፣ ፌስታይምን እና ተመሳሳይ ግኝቶችን አመጣን። ወሰን አልባ በሆነው የማሰብ አቅማችን የፈጠርናቸው ትርክቶች የውስንነታችንን ድንበር ለጠጡት። ማለትም ሁለት ተቃራኒ ኃይሎች ሲላተሙ መኃከለኛው የተሻለ ዓለም ሆነ።



ለዚህ ነው ቻርልስ ዳርዊን የIQ መጠኑ ዝቅ ያለ እንደሆነ ቢያውቅም፤ አንድ ነገር ግን ግልጽ ሆነለት። ውስንነቱ እና ያን ውስንነት በወሰን አልባነት የማስፊያ መንገድ። ስለዚህ ስለአንድ ነገር እርግጠኛ እውቀት ሲኖረው፣ የሚያደርገው በፍጥነት ከርሱ በፍጹም ተቃራኒ እውቀት እና አስተሳሰብ ካለው ሰው ጋር መወያየት እና የእርሱን ንደፈ ሀሳብ (theory) ውድቅ እንዲያደርግበት መወያየት ነበር።



ብዙዎቻችን ለራሳችን ባለ ስሱ እና egoistic አመለካከት ምክንያት ከተቃራኒ እይታ ልናተርፍ የምንችለውን እጅግ ድንቅ ጥቅሞች እናጣለን። ስለዚህ የሚቃረንን ጠላት ማድረግ ወይም መሸሽ ነው ስራችን። እኛ ያከበርነውን ሃይማኖት፣ ፖለቲካ፣ ግለሰብ የሚያቀልብን ሁሉ ጠላታችን ነው። ለዳርዊን ግን እንደዚህ ዓይነቱ ሰዎች ነበሩ ወዳጆቹ። ምክንያቱም የሰው ልጅ የአቅም ውስንነት የሚሻሻለው በተቃራኒው ኃይል ስበት ነው። የኛን አመለካከት የሚደግፉ (ኮንፎርም ከሚያደርጉ) እምብዛም የምናገኘው ጥቅሞች የሉም፤ ስሱ ሆነን የራስ መተማመናችንን በእነዚህ ድጋፎች መገንባት ካልፈለግን በቀር።



ዳርዊን ከታች ማንነት ተነስቶ ዌስት ሚኒስቴር ፍጻሜው የሆነው ውስን ስላልሆነ ሳይሆን፤ ናፍቆቱ እውነትን ማግኘት ስለነበረ ነበር። እውነትን ለማግኘት የሚጥር ሰው ስህተቱ በቶሎ እንዲገለጥ ነው የሚሻው። የአስተሳሰብም ሆነ የእምነት ስህተቱን ለፀሐይ (ለትችት) በማጋለጥ ፈውስን ያገኛል። የፀሐይ ብርሃን ትልቁ ኢንፌክሽን ማከሚያ ነው ይባላል። (sunshine is the best disinfectant)።



ለዚህ ነው መቀየር የማትችሉትን ነገር መቀበል ሲባል፤ መቀየረ የማንችለውን ነገር አሁን ባለው ውስንነታችን ማየት እና ወሰን አልባነታችንን ተጠቅመን ግን ድንበሮችን መግፋት ያሻል ማለት ነው።



ለምሳሌ ሰው ከሞተ በኋላ ለምን ሞተ ብሎ ማማረር ደካማነት ነው። የሞተን ሰው ምንም ማድረግ አንችልም። ያ ሕይወት ቢያንስ ከኛ ጋር ባለው ሕብረት አብቅቶለታል። ያን ሞት ወደ ሕይወት ማምጣት አንችልም። ግን አንድ ነገር ግን እንችላለን። ስለ ሞቱ ምክንያት ማጥናት፣ ያ የሞት ምክንያት ሌሎቹ ላይ ወደፊት እንዳይደገም እና ሕይወትን በቶሎ እንዳይቀጭ ማድረግ እንችላለን። በዚህም ከውስንነታችን በመማር የሌሎችን ሕይወት (ወሰን) ግድቡን ከፍ እናደርጋለን። ሞትን ባናስቀር እንኳ እናዘገየዋለን። ሞትን ዝም ብለን ብንቀበል ግን የማዘግየትን ዕድል እናጣለን።



በአዕምሮአችን ውስጥ ሁለት ትግሎች አሉ። ሕይወታችን በጊዜ የተገደበ መሆኑ። ሌላኛው ዘላለማዊ የመሆን ምኞት። (ምኞት ወሰን አልባ ነው)። ስለዚህ ሰው በሞት ሲቀጭ ከምኞታችን ጋር ይላተማል። በሞት እንዳይቀጭ እና ዘላለማዊ የመሆን ፍላጎት ጋር ማለት ነው። ስለዚህ ምኞታችን ስለሞት ያጠናል፣ ያን የሰው ሕይወት ለዘላለም ቅርብ ለማድረግ ይታገላል። በዚህም ምኞታችን ዘላለማዊ ጋር መድረስ ባንችል እንኳ የዕድሜን ገደብ ከፍ እናደርጋለን። ለዚህ ምኞታችን ሃይማኖት ጥሩ ትርክት ሆኖ አገልግሎናል። የሰው ልጅ ፈጽሞ አይቶት ስለማያውቀው ግን ተችሎ ነበር ስለሚለው የዘጠኝ መቶ ዓመቱ ማቱሳላ በእምነት እንድናይ ያደርገናል። ያ እምነታችን ወሰናችንን ያሰፋዋል።



ለዚህ ነው ስለምንቃወመው ነገር መጠንቀቅ ያለብን። ብዙ ሰዎች ሃይማኖት እርባና ቢስ እና ተራ የስሜት ምቾት ሰጪ ብቻ ያደርጉታል። ሃይማኖት ግን የማይቻለው ነገር ድንበር ሰባሪ ነው። ይሄ ማለት ሃይማኖት ሁልጊዜ ጥሩ ነው እያልኩ አይደለም። ብዙ ጎታች ሃይማኖቶች አሉ። እያልኩኝ ያለውት እንደ ጄ ኬ ቼስተርተን ነው። የሆነ አጥር ካየ ያ አጥር የቆመበት ምክንያት አለው። ጥራዝ ነጠቅ አዋቂዎች አጥሩን ሲያዩ፤ ምንድነው ይሄ አጥር ፥ ኑ እናፍርሰው ይላሉ። የበሰሉ አዋቂዎች ግን “ያለፈው ማህበረሰብ ዝም ብሎ አጥር አያስቀምጥም። ከማፍረሳችን በፊት ይሄ አጥር የቆመበትን ምክንያት ሁሉ ጠንቅቀን እንወቅ። ሲገባን ብቻ፣ ስናውቅ ብቻ የዛኔ ማፍረስ ካለብንም እናፈርሳለን።” ይላሉ።



ይሄ ጹሁፍ የሚነግረን አንድ ነገር የሆነ ሃሳብ ሲመጣልን ሌላ ሀሳብ በተቃራኒው እስከምናደምጥ እና የራሳችንንም ሆነ የተቃራኒውን ሀሳብ በደንብ እስከምናውቅ ድረስ አቋም ላለመያዝ እንጠንቀቅ እያለን ነው። አቋም በቀላሉ ይያዛል። የመማር እና የማወቅ ክፍተት ግን ከተደፈነ በኋላ መክፈት ከባድ ነው። የሰው ውስንነት በቶሎ የመርካት ዝንባሌ አለው። የማይታወቅ ነገር ስለሚያስፈራን በውሸት እውቀት ፍርሃትን ማሸነፍ እንመርጣለን።

 
 
 


እ.ኤ.አ. በጁላይ 2021 የተጻፈ እና በድጋሚ የተለጠፈ



በመንፈሳዊ ሕይወት ያደኩት በሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ነው። በዕድሜም በብዙ ንባብም መጎልመስ ስጀምር፣ በጉዙዎቼ ከብዙ አገራት ሰዎች ጋር ጥልቅ ውይይቶችን ሳደረግ መንፈሳዊ ብዬ ከተቀበልኩት ነገር ብዙ ለውጬያለው። አንዳንድ ከራሴ ጋር ያደረኩዋቸው ውይይቶች ለራሴ እስከሚያስፈሩኝ ድረስ በሀሳብ ተወስጄባቸዋለው። ካርል ዩንግ እና የሱን ፍልስፍና በስፋት ያስፋፋቱ እንደ አላን ዋትዝ እና ያን ፒያት እንደነገሩን በልጅነታችን ያለንን ስሪት በጣም እጅግ በትንሹ ብቻ ነው መለወጥ የምንችለው። አድካሚ “የኢንቴሌክቿል” ጉዞ ከሄድን መድረስ የምንችለው ራሳችንን ማወቅ ላይ ብቻ ይሆናል። ይሄ በልጅነት እንዴት እንደተሰራን ጥቃቅን ነገሮችን ሳይቀር በማስታወስ የሚደረግ አሰጨናቂ ጉዞ ነው።



ካርል ዩንግ ራሱን ለማወቅ በወንዝ ዳር እንደ ሕጻናት ጭቃ እያቦካ በመጫወት ሕጻን እያለ የተሰሙትን ስሜቶች ከ“unconscious” አዕምሮ ፈልቅቆ ለመረዳት በመጣር የሚሰማውን ስሜት ይመዘግብ ነበር።



አንድ ነገር ዘወትር አሰላስላለው። ቅዱስ ገብርኤል በእኔ ባህሪ ላይ ያለው ተጽዕኖ። በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ገብርኤል የጽናት ምሳሌ ነው። “ንቁም በበህላዌነ ፥ ባለንበት ጸንተን እንቁም” ብሎ ዓለም በአምላክ ቃል ከጸናች በኋላ ከፈጣሪ ቀጥሎ ጽናትን ያወጀ መላክ ነው። ከእሱ እና ከሌሎች ቅዱሳን በኃይሉ የገዘፈው የሳጥናኤል ግርማ ሳይረታው አምላኩን እስከሚያይ የጸና ፥ ያጸና መላዕክ ነው። ያዳናቸው ቅዱሳን ሁሉ የሱ ባህሪ አለባቸው። ፊት ለፊታቸው የገጠማቸው ጠላት ታይቶ የማይታወቅ ግዙፍ፣ ብዙዎች የተርበደበዱበት እነሱ ግን የመዳን ተስፋ እንኳ ርቋቸው ለእምነታቸው መከራውን ለመቀበል የተዘጋጁ ሰዎችን ነው በቅዱስ ገብርኤል አመታዊ በዓላት የሚዘከሩት።



በሌላ አነጋገር ከልጅነቴ ጀምሮ እምነት እና አሸናፊነት ተለያይቶ ነው ስሰበክ የነበረው። ለሆነ ነገር ዋጋ የምትከፍለው እንደምታሸነፍ ስለምታምን ሳይሆን ያ ነገር “አንተነትህን” ስለሚወስን ነው። ሠልስቱ ደቂቅም ሆኑ ሕጻን ቂርቆስ እንድናለን ብለው ወደ እሳት እና የሚንተከተክ ውሃ ውስጥ አልገቡም። ለእምነታችን መሞት ነው አሸናፊነት ፥ ብንድንም ፥ ባንድንም ለእኛ ግዳችን አይደለም። ለእኛ ዋናው ነገር “እምነታችን” ነው ያሉ ቅዱሳን ናቸው። ከዓመት ዓመት ያለመስልቸት የምንሰበከው እነዚህ ታሪኮችን ነው። በጽናት ስለቆመው መላዕክ እና ባንድንም ለማናምንበት ነገር አንበረከክም ስላሉ ቅዱሳን። እኔ ያደኩበት ቤተክርስቲያን መምህሩ (ፓስተሩ) አፈር ለአፈር እያንከባለለን አላደግንም። ስለመቆም እና ጥብአት እያስተማረን እንጂ። ውጤቱን አስልቼ (መዝኜ) አይደለም ለመሠረታዊ እሴቶቼ የምቆመው። እምነቴ ውጤቱን ያመጣው ይሆናል እንጂ ውጤቱ እምነቴን አይሸርፈውም። በኦሮቶዶክስ በተለይ በኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን ምሰሶ የሚባለው አትናቲዎስ የሚታወቀው “ዓለሙ ሁሉ ጠልቶሃል” ብሎ ሰይጣን ሲነግርው ፥ “እኔ ቀድሜ ዓለሙን ሁሉ ጠልቼዋለው” ብሎ በተናገረው ንግግሩ ነው። ይሄ እምነትን በውጤት አለመመዘን ቤተክርስቲያኒቷን በተረዱ ሰዎች ላይ የሚታይ ባህሪ ነው።



ወደ ንባብ ዓለም ስገባ የአምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ “I stand alone” መጽሐፍ እጅግ ይማርከኝ ነበር። አንድም የኃይለሥላሴ ባለስልጣን ደፍሮ ንጉሱ እና ሥርዓታቸው የገቡበትን ንቅዘት ለመናገር ባልፈቀዱ ሰዓት በእንጦጦ ቤተ-ክርስቲያን ያደገው ብርሃኑ ድንቄ ግን አላስቻለውም። ኋላም ጥገኝነት መራራ በሆነበት የነጭ አሜሪካ ተሰዶ ስለእምነቱ ፍጹሙ ስቃይን የተቀበለ ሰው ነው። ደርግም ሲመጣ አሁንም የእምነት ጉዳይ ነውና ደርግን አወገዘ። ኋላ ይሄ እምነቱ በጤናው ጨምሮ በሁሉም ነገር ዋጋ አስከፈለው። እሱ ግን ለእምነቱ የከፈለው ዋጋ ሳይጸጽተው አለፈ። ለእኛም “ብቻዬን ቆምኩኝ” የሚለውን መጽሐፉን አበረከተልን።



የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሲዖል እንደሚገቡ የተነገረላቸው ቅዱሳን ያላት እና "ሲዖል እንኳ ብንገባ የምናመልከው ገነት ወይም ሲዖል ያስገባናል ብለን አይደለም” ያሉ ቅዱሳን የነበራት ናት። ይሄ ነው ትምህርቷ። በዚህ ትምህርት የሚፈጠር የሰው ስነ-ልቦናን አስቡ።



ምንድነው ግቡ ሲዖል እና ገነት ካልሆነ ታዲያ ብሎ ለሚጠይቅ ፥ “ፍቅር” ትላለች ቤተክርስቲያን። መውደድ! በምታገኘው ነገር ሳይሆን በእምነትህ ፥ ለእምነትህ ባለህ ፍቅር ተደሰት። አንተነትህ ሸቀጥ አይደለም። ጸጋዬ ገብረመድህን “ይህችን ነው ኢትዮጵያ የሚላት።”



የቅዱስ ገብርኤል በዓል ተራ ንግስ እና ቅዱስ መላዕክ ማክበር ብቻ የሚመስለው ወይም ለቁስ ስኬት ስዕለት ለማስገባት ሰዎች የሚሯሯጡበት የሚመስለው ይኖራል። ይሄን የሚያደርጉም በዓሉን እና መላዕኩን እየሰደቡ ያሉ ይመስለኛል። በዚህ የቤተክርስቲያን ጥልቅ ፍልስፍና ላይ ቆሞ የሚንጎራደደው መድረክ መሪ የውጤት ተኮር ስዕለቶችን ዝርዝር ሲተርክ ይውላል።



እውነት ለመናገር በዚህ ዘመን ያለችው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን እና የብልጽግና የፕሮቴስታንት ቸርቾች ጋር ያለው የፍልስፍና ልዩነት ግራ ይገባኛል። የብልጽግና ፕሮቴስታንት የኢንዱስትሪያል አውሮፓ ፍጥረት ነው። ፍልፍስናው ሁሉ ኢንዱስትሪ ነው። የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ግን የቁሱ ዓለም ተቃራኒ ናት። ቄሳርን የለየች ነበረች። ዛሬ ያ የለም። እየተፈጠረ ያለው ትውልድም በሽንፈት የሚርድ ፥ በአሸናፊነት ያለ ልክ የሚወጠር ነው። ጦር ሜዳ የሚወስደው እምነቱ እና ክብሩ ሳይሆን ማሸነፍ መቻሉን እርግጠኛ ሲሆን ነው። ምንአልባት የብልጽግና ሃይማኖት ስኬት እየታየ ይሆናል።


አድዋ ላይ የጊዮርጊስን ታቦት ይዞ የዘመተው ሕዝብ እዛ ድረስ የወሰደው ሰውነት ስለሚባል ክብር ነው። ሰማዕት ጴጥሮስ በመድፍ ፊት ሃሳቡን ያለወጠው እና ጣልያንን እያወገዘ የጥይት አረር የተቀበለው ውጤት ተኮር ሃይማኖት ስላነበረው ነው። እንዴት የሰው ልጅ ማንነት በምንአልባት በሚወሰን የወደፊት ውጤት ይሰፈራል። ቅዱስ ገብርኤል የገባቸው አባቶቻችን ኢትዮጵያን የወደዷት ከዚህ እምነት በመነሳት ነበር። ኢትዮጵያ “ባያድነን እንኳ (ባይደላኝ፣ ብራብብሽ፣ ብሰቃይብሽ፣ ወዝ እና አቅም ባይኖርሽ) ፥ ለጠላቶቻችችን ውርደት አንገዛም” የሚለው እምነት ሃውልት ነበረች። ይሄን እምነት ነው አባቶቻችን ኢትዮጵያ የሚሉት።


 
 
 
  • Writer: Mulualem Getachew
    Mulualem Getachew
  • Dec 21, 2025
  • 3 min read


ምንም ነገር ስትጀምሩ ከማይቀረው እና የግድ ከሚሆነው መጀመር በብዙ የሚጠቅም ሆኖ አይቼዋለሁ። ይሄም ማለት ከመጨረሻው ወደ መጀመሪያ ወይም አሁን ወዳላችሁበት መጥቶ ማሰብ እጅግ ጠቃሚ ነው። ማናችንም ጋር የማይቀር አንድ ክስተት አለ። ሞታችን። አሁን በዚህ ሰዓት ጨምሮ በጥቂት ቀናት እና ዓመታት ውስጥ የምንሞት አለን። መቼ እንደ ሆነ አናውቅም እንጂ ሁላችንም የዚህ ፍጻሜ ደራሽ ነን።



ጥሎ የሚመጣው ጥያቄ “ቀሪው ሕይወታችሁን እንዴት ነው ማሳለፍ የምትፈልጉት? የሚል ነው። ብዙ ምርጫዎች አሉን። በሁለት ምሰሶዎች ግን ልንከፍላቸው እንችላለን። አንዱ ሁሉ እንደሚሆነው ሆኖ መሞት። ሌላኛው ደግሞ የታሰበበት ሕይወት መኖር።


የመጀመሪያው ቀላል ነው። ብዙ የአዕምሮ ሥራ አያስፈልገውም። ማመዛዘን አያሻውም። ብዙኋኑን መከተል ነው። ስሜት እና ሙዳችንን እያደመጡ ብቻ መንጎድ ነው።



ሁለተኛው ግን መቆም ያስፈልጋል። መጠየቅ፣ መመርመር፣ ግራ ቀኙን ማድመጥ እንዲህም ሆኖ መሳሳት እንዳለ ማመን እና ዘወትር አስተሳሰባችንን እየመዘኑ ለመጓዝ መወሰን ይጠይቃል።



ትላንት “ኦርዌል 2+2=5” የተባለ ግሩም ፊልም እያየው ነበር። ከግማሽ ክፍለ ዘመን በፊት የኖረ ግለሰብ የዛሬን የሰው ሁኔታ በደንብ ገልጾ መጻፉ አስደናቂ ነበር። ግን ተንብዮ እንዳይመስላችሁ። ከሱ በፊት እና በሱ ዘመን እየሆነ ያለውን በማየት እና በማስተዋል ነበር የጻፈው። እንደ ዘወትር የመጣልኝ ሀሳብ “የሰው ልጅ መቼም አይቀየርም” የሚል ነበር። ልክ እንዳልሆንኩኝ የገባኝ ዛሬ ያለንበት ዓለም ከመቶ እና ከዛ በላይ በፊት ከነበረው ዓለም በነጻነትም ሆነ በመብት መከበር እጅግ የተሻለ እንደሆነ ካስተዋልኩኝ በኋላ ነበር። የኦርዌልን ፊልም ሳየው ተስፋ ነበር ያስቆረጠኝ። ይሄ ዓለም በማፍያ ፖለቲከኞች እና በስግብግብ ሀብታሞች ብቻ የሚበዘበዝ እና 99 ፐርሰንቱ ማህበረሰብ ተጠቂ እንደሆነ ብቻ እንዲሁም ጎስቋል መሆኑ የማያቆም እና መቆሚያ የሌለው አድርጌ ነበር የሳልኩት። ያ ግን ፈጽሞ ልክ አይደለም።



አዎ ጨለማ ዙሪያችንን ከቦ ሊሆን ይችላል። መጥፎ ሰዎች ሲያብቡ እና እንዳበቡም ሲሞቱ እያየን ይሆናል። ክፉ እና አስመሳይ ሰዎች በደጋጎች ላይ ሲነግሱ ተመልክተን ይሆናል። እንደ ኢዮብ በንጽህናቸው የሚቀጡ እና ጉስቁልናቸው ማለቂያ የሌለውን ግለሰቦች እና ማህበረሰቦች እያየን ይሆናል።



ይሄ ሁኔታ ከዚህ በፊትም የነበረ እና ያለ እንዲሁም የሚኖር ነው። ግን የዚህ ዓለም ጨለማ ድሮ ከነበረው በብዙ እጥፍ ቀንሷል። ይሄ ዓለም ከሺዎች ዓመት በፊት የፈሪሳውያንን ሕግ አላከበርክም ብላ አንድ ፍጹም እና ንጹሁ የሆነን ሰው የሰቀለች ነበረች። የእርሱ ተከታይ ናችሁ ብላ ሌሎችን ደግሞ ቆዳ እስከመግፈፍ የደረሰች ነበረች። ይሄ ዓለም ለጆሮ ዘግናኝ የሆኑ ግፎችን ያስተናገደች ናት። አሁን ያ በጥቂት ቦታዎች እናይ ይሆናል እንጂ በብዙ ቀንሷል። ለብዙዎቻችን ዛሬ ከመቶ ዓመት በፊት ከነበረው በብዙ የተሻለ ነው።



ለዚህም ዋነኛው የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዓይነት ግለሰቦች ነበሩ። “ጨለማን ከማውገዝ ሻማ ማብራት የተሻለ ነው” ያሉ ሰዎች ናቸው ይሄን ዓለም ወደ ተሻለ መንገድ የመሩት። እዚህ ያደረሱት። አንዲት ቅድስት በዘመኗ ክፋት በዝቶ ሰዎች ተስፋ ሊያስቆርጧት ሲመጡ፤ ያለችው “የኔ ተልዕኮ ክፋትን ማሸነፍ አይደለም። የእኔ ድርሻ ክፋትን መዋጋት ነው” ነበር።



ኢትዮጵያውያን እኔም የምጋብዛቹ ይሄን ነው። በዚህ ዘመን እንደኔው ብዙ ግራ ገብቷቹ ሊሆን ይችላል። አዋቂው ሕጻን የሆነበት ዘመን ላይ እንዳላችሁ ሊሰማችሁ ይችላል። መላ ቅጡ የጠፋበት እና አዋቂነት ያሽቆለቆለበት ዘመን ላይ ልንሆን እንችላለን። ግድ የላችሁም። ይሄን ጨለማ በማውገዝ ጊዜ አታጥፉ። እናንተ ጋር ያለው መልካምነት እና በጎ መንፈስ ግን እንዳይጨልም አደራ። መልካም እና ደግ ከመሆን አትገደቡ። ምንም ቢጨልም የእናንተ ሻማ የሚገፈው ጨለማ እንዳለ እመኑ።


ዮሐንስ አፈወርቅ ብቻውን የቆመ ቢመስለውም የእርሱን የእምነት ሻማ ግን ለማጥፋት አልፈቀደም ነበር። ኢትዮጵያኖች በዚህ የተርዕዮ ዘመን፣ ሰዎች ዋጋቸውን ከሰዎች በሚገኝ ሙገሳ እና አድናቆት ለማግኘት በሚሮጡበት ዘመን፣ የመልካምነትን ደረጃ (ስታንዳርድ) ዝቅ ላለማድረግ እንጠንቀቅ። በጥቃቅን ነገሮች ሳይቀር ክብርን መጠበቅ፣ የምግባራችንን ደረጃ ከፍ ማድረግ፣ “የእኔ የስነምግባር ማማ ይሄ ነው" ማለት አናቁም። ሁሉም በሰከሩበት ሰዓት ላይ ብንኖር እንኳ የባህሪ ማማ ላይ ለመቆም እንቁረጥ።


ጨለማን በማውገዝ ያሸነፈ የትም የለም። አይኖርምም። በብርሃን፣ በሻማቸው ያሳወሩት ግን አሉ። እኛ ጨለማን በብርሃኑ ብዛት ካሳወረው ነን። ምንም ከባድ ቢሆን ፥ ለማሸነፍ ብቻ አይደለም እዚህ ያለነው። ምክንያቱም ማሸነፍ ብንፈልግ እንኳን ሞት አንድ ቀን ይረታናል። ማንም በመሸነፋችን አይታዘበንም። ሳንዋጋ እጅ በመስጠታችን እንጂ። በማይቀረው ሞታችን መኃል የሆኑ ሰዎችን ሕይወት፣ የሆኑ ግለሰቦችን ሕመም ፈውሰን፣ ጨለማ የነበረውን ሕይወታቸውን አብረተን ካለፍን ፥ የዛኔ ሞት የማይረታው ትንሣኤ በሌሎች ሕይወት ውስጥ ጥለን እንሄዳለን። ሻማ፣ አዎ ሻማ እናብራ በዚህ ጨለማ መኃል።

 
 
 

Contact the author

  • Facebook
  • Twitter
  • LinkedIn
  • Instagram

Thanks for submitting!

  • Facebook
  • X
  • Instagram

© 2024   by Mulualem's Sixth Sense

Designed and built by Abel

bottom of page